ከአዘነ ጋር የሚያዝኑት፣ እናት የሌላቸውን ሕጻናት አጥብተው የሚያሳድጉት፣ የጎረቤት ልጅ እንደ ራስ ልጅ የሚቀጡት፣ ሕግና ሥርዓት የሚያስተምሩት፣ ከልጅ ልጅ ቢለዩ ዓመትም አይቆዩ እያሉ የሚናገሩት የት ገቡ? ለሕጻናት የሚያዝኑ አንጀቶች፣ ለሕጻናት የሚንሰፈሰፉ ሆዶች፣ ለሕጻናት የሚራሩ ልቦች ምን አስቆረጣቸው ? ምንስ አስጨከናቸው?
የት እየሄድን ነው? በሕጻናት ላይ መጨከን እንደምን ያለ ጭካኔ ነው? ሕጻናትን መግደልስ እንደምን ያለ አገዳደል ነው? እንባቸው አያሳዝንምን? ዋይታቸው አያንሰፈስፍምን? ለቅሷቸው አንጀት አይበላምን? ኮልታፋ አንደበታቸው የጨካኝን ልብ አያራራምን? ፍቅራቸው ጥላቻን አያርቅምን? የልጅነት ወዛቸው ከክፋት አይመልስምን? ያልጠናው ገላቸው ልብ አይነካምን? ስለ ምን ተጨከነባቸው? ስለ ምንስ ተቆረጠባቸው?
ዓይን እንዳይበዛቸው ሸፍኗቸው፣ በሰው ፊት አትግለጧቸው፣ በምሽት ከቤት አታውጧቸው እየተባሉ ጥንቃቄ የሚበዛላቸውን፣ አብዝቶ የሚሳሳላቸውን ሕጻናትን ለመግደል እንደምን ተቻላችሁ? እንደምንስ ኾነላችሁ? ጭካኔውንስ ከየት አገኛችሁት?
ኢትዮጵያውያን እንደዚህ አስተምረዋልን? ኢትዮጵያን እንኳን ለሰው ልጅ ለአዕዋፋት ልጆች የሚያዝኑ፣ እናት የሞተችባትን የፍየል ግልገል ወተት አጠጥተው የሚያሳድጉ አይደሉምን? ከየት መጣችሁ? ማንስ ይሄን የጭካኔ ሀሳብ በልባችሁ ጻፈላችሁ? የአጨካከንም ልክ አለው፤ የአገዳደልም ወግ አለው እኮ።
በማሕጸኗ የተሸከመች፣ አምጣ የወለደች፣ በጀርባዋ ያዘለች፣ እየተራበች ያጎረሰች፣ እየተጠማች ያጠጣች፣ እየታረዘች ያለበሰች፣ እንቅልፍ አጥታ ለልጇ የኖረች እናት አታሳዝንምን? ለልጆቹ ሲል በችግር የሚኖር፣ ሀዘኑን በልጆቹ ደስታ የሚረሳ፣ ለእነርሱ ሲል ዓለሙን የተወ አባትስ አያሳስብምን? አምላክ ለዘር እንዲያበቃቸው የተማጸኑ ወላጆች አያሳዝኑምን?
እንደዚህ መክፋትስ ለማን ይበጃል? የዘሩትን ማጨድ፣ በሰፈሩት ቁና መሠፈር አይመጣምን? በራስ እንዲኾን ያልፈለጉትን በሰዎች ላይ ማድረግስ የተገባ ነውን ? ከሚደሰቱት ጋር ተደሰቱ፣ ከሚያዝኑትም ጋር እዘኑ እየተባለ በሚሰበክባት ሀገር፣ ደግነት እንደ ምንጭ ውኃ ሲፈስስባት በኖረች ምድር እንደዚህ ማድረግ ጤነኝነት ነውን ? የግፍ ጎርፍ እኮ ራስንም ይወስዳል። የግፍ እሳት እኮ ራስንም ያቃጥላል። ለሰው የተቆፈረ መቃብር እኮ ለራስም ይኾናል። በግፍ የፈሰሰ ደም እኮ በምድርም በሰማይም ይጮሃል። ለምሕረት የተጠበቀው ሰማይ እኮ ለማዕት የታዘዘ መከራ ያወርዳል።
የሕጻን ሄቨን ለቅሶ እና ሀዘን ሳይጠፋ፣ የፈሰሱ እንባዎች ሳይታበሱ፣ ያጠላው የድንጋጤ ድባብ ሳይገፈፍ ሌላ አሳዛኝ ድርጊት ተፈጽሟል። ለወትሮው ከሀዘን ማግስት ሀዘን የሚያስረሳ ተድላና ደስታ ይሰማ ነበር። ዛሬ ግን ሌላ መከራ፣ ሌላ ሀዘን፣ ሌላ እምባ፣ ሌላ አንጀት የሚቆርጥ መርዶ ተሰምቷል።
ኖላዊት ዘገዬ የተባለች ሕጻን በጎንደር በአጋቾቿ ተገድላ ኑ ሬሳችሁን አንሱ የሚል መርዶ መጥቷል። ከጡት ያልተለየች ሕጻን በአጋቾች ተወስዳ፣ በረሃብ እና በናፍቆት አልቅሳ በመጨረሻም በጨካኝ እጆች ላትመለስ አልፋለች። የወላጆቿን አንጀት ቆርጣ ያለ በደሏ አሸልባለች። ከሀዘኑም የከፋው ሀዘን ደግሞ ሕጻን ኖላዊት ከእገታ እንድትላቀቅ ብር ተጠይቆባት ነበር። ወላጆችም ልጃቸውን ለማስለቀቅ ብሩን ከፍለው ነበር። ዳሩ ግን ልጃቸውን አላገኟትም። በሕይወት አልተመሰለችም። ሬሳቸው ተላከላቸው እንጂ።
ብሩን ተቀብለው ሕጻኗን ገደሏት። ከበደልም የከፋው በደል ተፈጽሟል። ሕጻን እያስለቀሳችሁ ከዚያም ጨክናችሁ ገድላችሁ በተቀበላችሁት ገንዘብ ልታጌጡበት ነውን? ወይንስ ልጅ ልታሰድጉበት ነው? ግፍ አይደርሳበችሁምን?
የዚያች ታሪካዊት እና ቀደምት ከተማ ጎንደር ነዋሪዎች፣ ደጋጎቹ አዝነዋል። ከማንነታቸው፣ ባሕላቸው እና ከልካቸው የወጣ ክፉ ድርጊት ተፈጽሞባቸዋልና አንብተዋል። እነርሱ የሚያውቁት ታላቅን ማክበር፣ ታናሽን እየወደዱ ማሳደግ እንጂ እንዲህ አይደለምና። በቀያቸው ተደርጎ የማይታወቅ ነገር ተደርጎባቸዋልና። እነርሱ የሚያውቁት ያዘነን ማጽናናት ነውና እያዘኑ ነው።
እሺ ሕዝብ እትብቱ ከተቀበረበት፣ ተወልዶ ካደገበት፣ አግብቶ ወግ ማዕረግ ካየበት፣ ምድር ርቆ የት ይሂድላችሁ ? ምን ያድርግላችሁ ? ስለ ምን መከራውን ታበዙበታላችሁ ? ስለምንስ ስቃዩን ታጸኑበታላችሁ? ለምን በሰላም እንዲኖር አትተዉትም? ለምን በቆየው በባሕሉና እሴቱ እንዲኖር አትፈቅዱለትም? መከራው በዛ እኮ። ሰቃዩ በረታበት እኮ። መሳቀቅ ይበቃዋል። የጥይት ድምጽ ሰልችቶታል። እያነሱ መቅበር መርሮታል።
በአማራ ክልል በተፈጠረው የጸጥታ ችግር ምክንያት ግፍና በደል እንደቦይ ውኃ እየፈሰሰ ነው። በየቀኑ ንጹሐን ይታገታሉ፣ ለፍቶ አዳሪዎች ይታፈናሉ። በሚሊዮን የሚቆጠር ብር ይጠየቃሉ። መክፈል የሚችሉ ጥሪታቸውን ሰጥተው ይለቀቃሉ። መክፈል የማይችሉ ደግሞ በአጋቾች አፈሙዝ ተበልተው የወገን ጸጸት ኾነው ይቀራሉ። ሕጻን ኖላዊትም የኾነችው እንዲሁ ነው።
ግፍና እንግልቱ ሊገልጹት፣ ሊናገሩት፣ ሊጽፉትና ሊተርኩት ከሚችሉት በላይ ኾኗል። በሕጻን ሄቨን እንዲያቆም የታሰበው ግድያ በሕጻን ኖላዊት ቀጥሏል። እኒያ መልካም እሴቶች ካልተመለሱ፣ ነውር የሚፈጽሙት፣ ግፍን የሚያደርጉት ካልተወገዙ፣ ከሰው ካልተለዩ ነገም ላለመቀጠሉ ዋስትና የለም።
ግን የት እየሄድን ነው? መድረሻችንስ የት ነው? ግባችንስ ምንድን ነው? ስንት ሕጻናት ሲሞቱ ነው የሚቆጨን ? ስንት ንጹሐን ሲያልቁ ነው የሚያንገበግበን ? መቼ ነው በቃ የምንለው ? ዛሬ ከንፈር መጥጠው ቢያሳልፉት ነገ በየቤቱ ይደርሳል። ዛሬ እንደዋዛ ዝም ቢሉት አንዳንድ እያለ ሁሉንም ይወስዳል። ሁሉም ከመወሰዱ፣ ግፈኞች በንጹሐን ላይ ከመሠልጠናቸው አስቀድሞ በአንድነት፣ በኅብረት እና በቁርጠኝነት በቃን ብሎ መነሳት፣ በጋራም ሰላምን መጠበቅ ግድ ይላል። ያ ካልኾነ ግን ከንፈር መምጠጡ ይቀጥላል። ሞቱም እንደዚያው ይኾናል።
አሚኮ


