በግለሰቦች ላይ ጥናት በማድረግ የዘረፋ ወንጀል ሲፈፅሙ የነበሩ ተጠርጣሪዎችን በቁጥጥር ስር አውሎ ምርመራ እያጣራ መሆኑን የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታወቀ፡፡
ተጠርጣሪዎቹ በቁጥጥር ስር የዋሉት በቦሌ ክፍለ ከተማ ልዩ ልዩ ስፍራዎች ላይ ትኩረት አድርገው የቅሚያ እና የዘረፋ ወንጀል ሊፈፀምባቸው የሚችሉ ግለሰቦችን አስቀድሞ በማጥናት ወንጀሉን ሲፈፅሙ እንደነበር የክፍለ ከተማው ፖሊስ መምሪያ ኃላፊ ረዳት ኮሚሽነር አድማሱ ኢፋ ተናግረዋል፡፡
የቦሌ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ በክፍለ ከተማው ልዩ ልዩ ስፍራዎች የሚፈፀሙ የቅሚያና የዘረፋ ወንጀሎችን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር በጥናት ላይ ተመስርቶ ባደረገው ክትትል ተደራጅተው የቅሚያ እና የዘረፋ ወንጀል ሲፈፅሙ የነበሩ መሰረት ኪዳኔ߹ ሐብቶም ሐይሉ߹ ኬቨን አማኑኤል߹ አብርሀም አፅባ ߹ሙሉጌታ መክት߹ አብርሀም ማናሰበ߹ ሁሴን ዳውድ߹ አማኑኤል ሐይሌ ߹ እዮብ አለማየሁ ߹ በድሉ ደጉ߹ ምስኪ አድማሱ እና ሰለሞን ታደሰ የተባሉ በአጠቃላይ አስራ አራት ግለሰቦችን በቁጥጥር ስር አውሎ የግል ተበዳዮች ፈፃሚዎቹን እንዲለዩ በማድረግ ንብረት ማስመለሱንና ምርመራውን አጠናክሮ መቀጠሉን ኃላፊው ተናግረዋል፡፡
ፖሊስ መምሪያው ወንጀል ፈፃሚዎቹን ለይቶ በቁጥጥር ስር ለማዋል በክትትል ላይ እንዳለ በፖሊስ ሲፈለግ የነበረው አንድ ተጠርጣሪ በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 4 ልዩ ቦታው ጎላጉል ህንፃ አካባቢ ከቀኑ 7 ሰዓት ገደማ ከወይዘሮ ሸሪፋ ኢብራሂም ላይ ግምቱ 33ሺ ብር የሚያወጣ ሞባይል ስልክ ቀምቶ ለማምለጥ ሲሞክር ግለሰቡን ለመያዝ ክትትል ላይ በነበሩት የፖሊስ አባላት እጅ ከፍንጅ መያዙ ታውቋል፡፡
ተጠርጣሪው በቁጥጥር ስር መዋሉን ተከትሎ በተከናወነ ምርመራ የማስፋት ስራ ከዚህ ቀደም በክፍለ ከተማው ወረዳ 3 ቦሌ መድሃኔዓለም እና በወረዳ 2 ቦሌ ፍሬንድሺፕ ߹ደሳለኝ ሆቴል እና ሳፋሪ አዲስ አካባቢ በሌሎች ግለሰቦች ላይ ተመሳሳይ ወንጀል መፈፀሙ ተረጋግጧል፡፡
በሌላ የወንጀል ድርጊት ትኩረታቸውን በቤት ሰብሮ ስርቆት ላይ ያደረጉ ወንጀል ፈፃሚዎችን ለመያዝ በተደረገ ክትትል ቢኒያም አለማየሁ እና ይድነቃቸው ጋረደው የተባሉት ተጠርጣሪዎችን መያዙን መምሪያው ገልፆል፡፡ ወንጀል ፈፃሚዎቹን በቁጥጥር ስር ለማዋል በተደረገ ክትትል በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 3 ልዩ ቦታው ኖህ ሪል ስቴት ህንፃ 11ኛ ፎቅ ላይ በመውጣትና ተመሳሳይ ቁልፍ በመጠቀም የአንድን ግለሰብ መኖሪያ ቤት ከፍተው በመግባት 1ሺህ 688 የአሜሪካ ዶላር፣ 61 የእንግሊዝ ፓውንድ እና 17 ሺህ 250 ሰርቀው ሲወጡ መስከረም 8 ቀን 2017 ዓ/ም እጅ ከፍንጅ እንደተያዙ ተጠቅሷል፡፡
ግለሰቦቹ በፈፀሟቸው ወንጀሎች በአጠቃላይ 4 መዝገቦች ተደራጅቶ እና ክስ ተመስርቶ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ እንደሚገኝ እና የቤት ሰብሮ ስርቆት በፈፀሙት ላይ ምርመራው ተጠናክሮ መቀጠሉን ረዳት ኮሚሽነር አድማሱ ኢፋ ገልፀዋል፡፡
ወንጀል ፈፃሚዎቹ ወንጀሉን የሚፈፅሙት በቦሌ ክፍለ ከተማ ልዩ ልዩ ስፍራዎች በመንቀሳቀስ ግለሰቦችንና መኖሪያ ቤቶችን አስቀድመው በማጥናት ሲሆን በሰው አካል ላይ ጉዳት በማድረስ ጭምር ወንጀሉን ሲፈፅሙ መቆየታቸውን ኃላፊው አስታውሰዋል ። በግለሰቦቹ ላይ ተጨማሪ መረጃዎችን መስጠት የሚፈልግ ወይም ወንጀል ተፈፅሞብኛል ባይ ቦሌ ክ/ከተማ ፖሊስ መምሪያ በአካል በመገኘት እንዲለይ እና ተጨማሪ መረጃ እንዲሰጥ ሀላፊው ጥሪ ያቀረቡ ሲሆን ወንጀል ፈፃሚዎችን በቁጥጥር ስር ማዋል በመቻሉ የአካባቢው የወንጀል ስጋቶችን በከፍተኛ ሁኔታ መቀነስን ገልፀው መረጃ በመስጠት በኩል ህብረተሰቡ የነበረው ተሳትፎ የሚበረታታ ነው ሲሉ አስረድተዋል፡፡


