የውጭ ባንኮች ከሚቀጥለው ዓመት አጋማሽ ላይ ወደ ኢትዮጵያ በመግባት ኢንዱስትሪውን እንደሚቀላቀሉ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ አቶ ማሞ ምሕረቱ አመልክተዋል።
የውጭ ባንኮችን ሥራ ለማስጀመር በተያዘው ዕቅድ መሠረት የመጀመሪያዎቹ የውጭ አገር ባንኮች በ2025 መጨረሻ ወይም በመጪው በጀት ዓመት አጋማሽ ወደ ሥራ እንደሚገቡና ለዚህም አስፈላጊ የሆኑ ዝግጅቶች መደረጋቸውን አቶ ማሞ ገልጸዋል።
በቀጣዩ ዓመት የውጭ ባንኮች ወደ ኢትዮጵያ መግባት እውን ቢሆንም የትኞቹ የውጭ ባንኮች ሊገቡ እንደሚችሉ ግን የብሔራዊ ባንክ ገዢ አልገለጹም።
የውጭ ባንኮች እንዳይገቡ እንቅፋት ይሆናቸዋል ተብለው ይጠቀሱ የነበሩ አንዳንድ መመሪያዎች የውጭ ባንኮች ይገባሉ ተብሎ ከተጠቀሰው ጊዜ ቀደም ብሎ የሚስተካከሉ መሆኑ ተነግሯል።
የውጭ ባንኮች ቢግቡ አይቀበሏቸውም ተብለው ሲጠቀሱ ከነበሩ መመሪያዎች መካከል በአሁኑ ወቅት ባንኮች በአስገዳጅነት እንዲገዙ የሚገደዱት ቦንዶችና የ18 በመቶው የብድር ገደብ ጣሪያ ይገኙባቸዋል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ እነዚህ መመሪያዎች እንደሚሻሩና ለዚህም ቀነ ገደብ መቀመጡን ይፋ እንዳደረጉ ሪፖርተር ጋዜጣ አስነብቧል።


