ሰሞኑን የጎጃም ፋኖ የክልሉ መንግስት ከሚለው በተቃራኒ እያጠቃ፣ እየማረከና ድል እየተቀዳጀ እንደሆነ ቢያስታውቅም፣ የባሕርዳር ከተማ አስተዳድር ከዚህ በፊት ጥሏቸው የነበሩ ገደቦችን አነሳ። የሰዓት እላፊ ገደቡ መነሳቱን ተከትሎ ከፋኖ ወገን የተሰማ ነገር የለም።
በቅርቡ ክልሉ “አማራ ክልልን ወደ ተሟላ ሰላም ለመመለስ ከሕግ ማስከበር ባለፈ የሰላም አማራጭ ተዘርግቶ እየተሠራ ነው” ተብሎ ነበር። ሰፊ የፖሊስ፣ አድማ ብተናና፣ ሚሊሻ በማስለጠን ከመከላከያ ጋር በመሆን ሰፊ ስራ እየተሰራ መሆኑን ገልጾ ነበር። ከፋኖ በኩል መረጃው ተራ ፕሮፓጋንዳ እንጂ በመሬት ላይ የሌለ ሽንፈት የወለደው ዜና እንደሆነ በመግለጽ ሲያጣጥሉ ነበር የከረመት።
የአማራ ክልል ሰላም እና ጸጥታ ቢሮ ኀላፊ ዶ/ር እሸቱ የሱፍ ሰሞኑን በሰጡት ሰፊ ቃለ ምልልስ “ፋኖ እንደ ኳስ የሚነጥርበት ስፍራ የለውም” ሲሉ በየስርቻው ተበትኖ እንደሚገኝ ማመልከታቸው አይዘነጋም።
ኃላፊው አክለውም ” ክልሉን ወደ ተሟላ ሰላም ለመመለስ ከሕግ ማስከበር ባለፈ የሰላም አማራጭ ተዘርግቶ እየተሠራ ይገኛል። በዚህም በርካታ የታጠቀ ቡድን በሰላም ወደ ማኅበረሰቡ እንዲቀላቀል ተደርጓል” ብለው ነበር፡፡
ዶክተር እሸቱ ይህን ባሉ በሳምንት ጊዜ ውስጥ ነው የክልሉ የጸጥታ ምክር ቤት “የከተማችንን የጸጥታ ሁኔታ መነሻ በማድረግ የኅብረተሰቡን ደህንንነት ከማስጠበቅ አኳያ ልዩ ልዩ ክልከላዎችን” አንስተናል ሲል ያስታወቀው።
የፋኖን ዜናዎች በቀጥታ ስልክ በመደወልና በማነጋጋር እየዘገቡ ያሉት በውጭ የሚገኙ የዩቲዩብና የማህበራዊ ሚዲያ አውዶች በሰበር ሳይቀር ፋኖ አንጸባራቂ ድል ማስመዘገቡን ዕለት ዕለት ሲዘግቡ መክረማቸው አይዘነጋም። እነዝህ ሚዲያዎች ከፍተኛ ቁጥር ያለው የመንግስት ኃይል መማረኩን፣ ሙትና ቁስለኛ መሆኑን እንዲሁም ለማጥቃት ሞክሮ ሳይሳካለት መሳሪያውን እንዳስረከበ በተከታታይ ይዘገቡ ነበር።
የአማራ ክልል ሰላም እና ጸጥታ ቢሮ ኀላፊ ዶ/ር እሸቱ የሱፍ ለፋኖ ምላሽ ለመስጠት በውስን ቦታዎች ሳይሆን በአጠቃላይ የክልሉን ሁኔታ ሲያስረዱ ” ተላላኪ፣ ጉዳይ አስፈጻሚ” ያሉት ፋኖ አሁን ላይ እዚህ ግባ የሚባል ኃይል እንዳልሆነ ዝርዝር መረጃ አንስተዋ አስታውቀው ነበር።
ዛሬ ይፋ የሆነው መረጃ “አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ በባሕርዳር ከተማ አስተዳድር በተከታታይ በተሠራው ጠንካራ የሕግ ማስከበር ሥራ እና በኅብረተሰቡ የላቀ ተሳትፎ የከተማዋ የሰላምና የጸጥታ ኹኔታ በከፍተኛ ኹኔታ እየተሻሻለ መምጣቱን ምክር ቤቱ ገምግሟል” ያላል።
የከተማው ፀጥታ ምክር ቤት ሌላው አፅዕኖት ሰጦ የተመለከተው የከተማው ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ኹኔታ በጥሩ እንቅስቃሴ ላይ የሚገኝ መሆኑንና ይህንኑ በላቀ ኹኔታ ለማሳለጥና የከተማዋን የቱሪዝም እና የልማት ተግባራት የበለጠ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ለማድረግ ሲባል ከዚህ ቀደም ተጥለው የነበሩ ገደቦች መነሳታቸውን ይፋ አድርጓል። በከፊል ገደባቸው ሙሉ በመሉ የተነሳባቸው
- ማንኛውም የንግድ እንቅስቃሴ ያለገደብ 24 ሰዓት ክፍት በማድረግ እንዲሠሩ ተወስኗል፣
- ከባጃጅ እና ከሞተር ሳይክል ውጭ ሁሉም ተሽከርካሪዎች ያለገደብ እንዲንቀሳቀሱ ተወስኗል፣
- ማንኛውም ሰው ያለምንም የሰዓት ገደብ እንዲንቀሳቀስ ተፈቅዷል፣
በሌላ በኩል ማሻሻያ ያልተደረገባቸውና አሁንም የተጣሉ ግዴታዎችን አስመልክቶ ምክር ቤቱ፣ - ማንኛውም ተሽከርካሪ በሚንቀሳቀስበት ጊዜ የፊት ለፊትና የኋላ ሰሌዳ አሟልቶ መንቀሳቀስ አለበት ይህንን ሳያደርግ ተገኝቶ በጸጥታ ሀይሉ ለሚወሰደው ማንኛውም ሕጋዊ እርምጃ ኅላፊነቱን ራሱ ይወስዳል፣
- ማንኛውም እግረኛ ሲንቀሳቀስ ማንነቱን የሚገልጽ የቀበሌ የነዋሪነት መታወቂያ ይዞ መገኘት አለበት፣
- የጸጥታ ሀይሉ እና በሚኖሩበት ቀበሌ ወይም ቀጠና ወይም ብሎክ ብቻ መሳሪያ ይዘው እንዲንቀሳቀሱ ከፈቀደላቸው መሳሪያ ፈቃድ ኩፖን ከተሰጣቸው ውጭ የጦር መሳሪያ ይዞ መንቀሳቀስ በፍጹም የተከለከለ ነው፣
- የባጃጅ ተሽከርካሪ ከምሽቱ 12:00 ሰዓት በኋላ ይዞ መንቀሳቀስ ክልክል ነው፣
- ባለ ሁለት እግር ሞተር በማንኛውም ሁኔታ ይዞ መንቀሳቀስ በፍጹም የተከለከለ መኾኑን ከከተማ አስተዳደሩ ኮሙኒኬሽን ገጽ የተገኘ መረጃ ያሳያል።


