ከኢሚግሬሽን እና ዜግነት አገልግሎት አሠጣጥ ጋር በተያያዘ ከተገልጋዮች የሚነሱ ተደጋጋሚ ቅሬታዎችን ከመሰረቱ ለመፍታት ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት፣ ከኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ እና ከኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት የተወጣጣ ግብረ-ኃይል ሕገ ወጦችንና ሙሰኞችን በሕግ ተጠያቂ ለማድረግ ለረጅም ጊዜ የተቀናጀ ክትትልና ምርመራ ሲያደርግ ቆይቷል ይላል ጉዳዩን አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙኃን የተላከው መግለጫ።
በመሆኑም ከተቋማቱ የተወጣጣውና ጉዳዩን እየተከታተለ ያለው የጋራ ግብረ-ኃይሉ በመግለጫው እንዳመለከተው፤ ተገልጋዮች በመደበኛ የመንግሥት ስርዓት የሚፈልጉትን የፓስፖርትና መሰል አገልግሎቶችን በአፋጣኝና በአነስተኛ ዋጋ ማግኘት ሲችሉ፤ ተጠርጣሪዎች የፈጠሯቸው የተንዛዙና እና የተወሳሰቡ አሠራሮች ዜጎችን ለከፋ እንግልት ከመዳረግ ባሻገር ላልተገባ ወጪ ሲዳርጉ ነበር፡፡
ተጠርጣሪዎቹ ከፍተኛ ገንዘብ በመጠየቅ በሙስና ተግባር መሰመራታቸውና የግል ጥቅማቸውን ሲያሳድዱ እንደነበር ያመለከተው ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት፣ ከኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ እና ከኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት የተወጣጣው ግብረ-ኃይል ፤ ግለሰቦቹ በአገልግሎት መሥሪያ ቤቱ የተሰጣቸውን ስልጣንና ሐላፊነት ወደ ጎን በመተው ለግል ጥቅማቸው ሲሉ በዜግነት ኢትዮጵያዊ ላልሆኑ የውጭ ሀገራት ዜጎች፣ በወንጀል ተከሰው የጉዞ ሰነዳቸው ለታገደባቸውና ሐሰተኛ የማንነት መገለጫ ላላቸው ሕገወጦች ጭምር የፓስፖርት፣ ሊሴፓሴና ቪዛ አየር በአየር በመሸጥ እና በማስተላለፍ፤ መንገደኞች በሌሉበት ጉዞ እንዳላቸው በማስመሰል እና የጉዞ ሰነድ በማዘጋጀት ወደ ተለያዩ ሀገራት እንደተዘዋወሩ የሚገለፅ ማሕተም በማዘጋጀት ተግባር ተሰማርተው ተገኝተዋል።

በተጨማሪም ከሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ተመልምለው ያለፉ እንደሆኑ በማስመሰል ግለሰቦች ባልተገባ መንገድ ለሥራ ወደ ተለያዩ የዓረብ ሀገራት እንዲወጡ በማድረግ እንዲሁም የሕጋዊ ግለሰብን ፓስፖርት ፎቶግራፍ በመቀየር ከፍተኛ የማጭበርበር ወንጀል ሲፈጽሙ እንደተደረሰባቸው የግብረ-ኃይሉ መግለጫ ጠቁሟል።
እነዚህ ወንጀለኞች ከአዲስ አበባ እስከ ክልሎች የጥቅም ትስስር በመዘርጋት ሙስና ሲፈጽሙ ከመቆየታቸውም ባሻገር፤ ሐሰተኛ የማንነት መታወቂያዎችን በማዘጋጀት ተግባር ላይ ተሰማርተው ከነበሩ የውጭ ሀገር ዜጎች ጋርም ግንኙነት በመፍጠር ወንጀሉን ሲፈፅሙ እንደቆዩ ታውቋል።
ይህን ተከትሎም ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት፣ ከኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ እና ከኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት የተወጣጣው ግብረ-ኃይሉ ባደረገው ክትትል ከ200 በላይ የሚሆኑ በሕገወጥ መንገድ የተዘጋጁ ፓስፖርቶች እንዲመክኑ የተደረገ ሲሆን፤ የወንጀል ድርጊቱም መንግሥትን በሚሊዮን የሚቆጠር የውጭ ምንዛሪ እንዳሳጣው በመግለጫው ተመልክቷል።

በጉዳዩ ላይ ምርመራ ሲያደርግ የቆየው ግብረ -ኃይሉ መግለጫ እንዳመለከተው፤ በአዲስ አበባ ከተማ፤ ኦሮሚያ፣ አማራ፣ ሲዳማ፣ ሶማሌ፣ ጋምቤላ እና ቤንሻንጉል ጉምዝ ክልሎች በወንጀሉ የተሳተፉ በኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ሲያገለግሉ የነበሩ ከከፍተኛ አመራርነት እስከ ባለሙያ ያሉ 42 ተጠርጣሪዎች በሕግ ቁጥጥር ስር ውለዋል፡፡
በዙሁ መሰረትም በወንጀል ድርጊቱ ተሰማርተው ከተገኙና በሕግ ቁጥጥር ስር ከዋሉ ተጠርጣሪዎች መካከልም የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር የነበሩት ታምሩ ግንበቶ አዋልሶን ጨምሮ ዘመድኩን ጌታቸው፣ ከድር ሰዒድ ስሩር፣ አስቻለው እዘዘው፣ አብዱላሂ አሊ መሀመድ (አብዱላሂ ጃርሶ)፣ ቴዎድሮስ ቦጋለ፣ ጌትነት አየለ፣ ጀማል ገዳ፣ ሙላት ደስታ፣ ጅላሎ በድሩ፣ ገነት ኃ/ማርያም፣ ደገፋ ቤኩማ ፣ ወንድይፍራው ሽመልስ ገ/ሰንበት እና ሌሎችም እንደሚገኙበት ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት፣ ከኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ እና ከኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት የተወጣጣው ግብረ-ኃይል አስታውቋል።
በተያዙት ተጠርጣሪዎች ዙሪያ የሚደረገው ምርመራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል በመግለጽም፤ በግለሰቦቹ ዙሪያ ተጨማሪ መረጃ ያላቸው ዜጎች ለፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቢሮ ጥቆማ መስጠት እንደሚችሉም ገልጿል፡፡
በዚህ ኦፕሬሽንም የተለያዩ ፓስፖርቶች፣ የተለያዩ ሀገራት የብር ኖቶች፣ ሐሰተኛ መታወቂያዎች፣ አየር በአየር የወጡ ሊሴ ፓሴዎችና የታተሙ ቪዛ ካርዶች በተጠርጣሪዎቹ መኖሪያ ቤትና የሥራ ቦታ በተደረገ ብርበራ በኢግዝቢትነት መያዛቸወን ግብረ -ኃይሉ አመልክቷል።
ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት፣ ከኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ እና ከኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት የተወጣጣው ግብረ -ኃይል በእንደዚህ አይነት ሕገ ወጥ ተግባር ዙሪያ የሚያካሂደውን ምርመራ፣ ክትትልና ኦፕሬሽን አጠናክሮ እንደሚቀጥል በመግለጽ፤ ለኦፕሬሽኑ መሳካት ማኅበረሰቡ ላሳየው የተለመደና ቀና ትብብር ምስጋናውን አቅርቧል፡፡
- ONLF Rejects Claims of Affiliation With Armed GroupsVOA NEWS – The Ogaden National Liberation Front (ONLF) categorically rejects claims of affiliation with armed groups and reaffirms its unwavering commitment… Read more: ONLF Rejects Claims of Affiliation With Armed Groups
- Beyond the Ballot: How Professor Alemayehu G. Mariam Explains Ethiopia’s Democratic ‘Escape Velocity’ on ETVIn an incisive broadcast on EBC English analyzing the architectural shifts of Ethiopia’s 7th General Election, renowned scholar Professor Alemayehu G. Mariam… Read more: Beyond the Ballot: How Professor Alemayehu G. Mariam Explains Ethiopia’s Democratic ‘Escape Velocity’ on ETV
- Dr. Jote Tafese: “Curing Incurable Diseases Through Science”VOE June 06, 2026 – Although genetic engineering is a relatively new field of science—spanning no more than 40 years—it is currently… Read more: Dr. Jote Tafese: “Curing Incurable Diseases Through Science”
- ዶ/ር ጆቴ ታፈሰ- መድኃኒት አልባ ሕመሞችን በሳይንስ መፈወስሰዎችን – ከሞት አፋፍ መመለስቪኦኢ ሰኔ 30 ቀን 2018 ዓ.ም – የዘረ መል ምህንድስና (Genetic Engineering) ዕድሜው ከ40 ዓመታት የማይበልጥ አዲስ የሳይንስ ዘርፍ ቢሆንም፣ በአሁኑ ወቅት… Read more: ዶ/ር ጆቴ ታፈሰ- መድኃኒት አልባ ሕመሞችን በሳይንስ መፈወስሰዎችን – ከሞት አፋፍ መመለስ
- ኬሞቴራፒን ማስቀረት የተቻለበት አዲስ ተስፋ፡ የ64 ዓመቷ ካረን የ«ዳግም መወለድ»ቪኦኢ ሰኔ 30 ቀን 2018 – ከካርዲፍ የመጣችው የ64 ዓመቷ አዛውንት ካረን ቦንሃም፣ የጡት ካንሰር እንዳለባት በወቀችበት ወቅት እንደማንኛውም ታካሚ ከፍተኛ ድንጋጤ… Read more: ኬሞቴራፒን ማስቀረት የተቻለበት አዲስ ተስፋ፡ የ64 ዓመቷ ካረን የ«ዳግም መወለድ»







