የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ስደተኛ ባልሆኑ የቪዛ አመልካቾች ላይ የፖሊሲ ለውጥ ማድረጉን ማሳወቁ ይታወሳል። የፖሊሲ ለውጡ ከሐምሌ 1/2017 ዓ.ም. ጀምሮ ለኢትዮጵውያን የሚሰጠው ቪዛ ለአንድ ጊዜ ብቻ የሚያገለግል እና የሦስት ወር ቆይታ ብቻ እንዲኖረው ያደረገ ሆኗል።
በኢትዮጵያ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ በአዲሱ መመሪያ መሠረት ወደ ሃገሪቱ በጊዜያዊነት ጉዞ ለማድረግ የቪዛ ጥያቄ የሚያመለክቱ ዜጎችን የበይነ መረብ (online) አጠቃቀም ላይ ሁሉን አካታች እና ጥልቅ የሆነ ማጣራት እንደሚያካሄድ አሳውቋል።
አምባሲው ” በአዲሱ መመሪያ መሠረት በጉብኝት ቪዛ መደብ ውስጥ የF ፣ M እና J ሁሉም የተማሪ እና የልውውጥ (Exchange) ቪዛ አመልካቾችን የበይነ መረብ (online) አጠቃቀም ጨምሮ ሁሉን አካታች እና ጥልቅ የሆነ ማጣራት እናካሄዳለን ” ብሏል።
ይህን የማጣራት ሥራ ለማቀላጠፍም ሁሉም የ F ፣ M እና J የጉብኝት ቪዛ አመልካቾች ሁሉንም የማህበራዊ ትስስር ገጽ መለያቸውን ከግል ሴቲንግ ወደ ክፍት/ይፋዊ ሴቲንግ (public setting) እንዲያስተካክሉ ጠይቋል።
የአሜሪካ መንግስት ወደ ሃገሪቱ ለመግባት የሚያመለክቱ ዜጎችን የጉዞ አላማ እና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን በመመልከት በሃገሪቱ የስደተኞች ህግ መሰረት ምን አይነት ቪዛ እንደሚያስፈልግ ምድብ የሚሰጥ መሆኑ ይታወቃል።
ለጊዜያዊ ጉዳዮች እና በቋሚነት ወደ አሜሪካ ጉዞ ለሚያደርጉ ዜጎች በዩኤስ ኤምባሲ ወይም ቆንስላ ሲያመለክቱ ኦፊሰሮች በህጎች ላይ በመመስረት ቪዛ ለመቀበል ብቁ ሆነው ለተገኙ ዜጎች የትኛው የቪዛ ምድብ ለአመልካቹ ተገቢ እንደሆነ ይወስናሉ።
F፣ M እና J የተሰኙ የቪዛ ምድቦች ስደተኛ ያልሆኑ እና ለትምህርት ፣ ለአካዳሚክ ጉዳዮች እና ከተለመደው የቱሪስት ቪዛ ውጪ ለጉብኝት እንዲሁም ለልዩ ልዩ ጉዳዮች ወደ አሜሪካ በጊዜያዊነት ለመግባት ለሚያመለክቱ ዜጎች የሚሰጥ ቪዛን ያመለክታል።
° ኤፍ ቪዛ (F-1/F-2) ፡-
በዋነኛነት በዩኤስ ኮሌጆች፣ ዩኒቨርሲቲዎች ወይም የእንግሊዝኛ ቋንቋ ተቋማት የሙሉ ጊዜ ትምህርት ለሚከታተሉ የአካዳሚክ ተማሪዎች።
° M ቪዛ (M-1/M-2)፡
እንደ የቴክኒክ ክህሎት ስልጠና ላሉ፣ ለሙያ ፣ አካዳሚክ ያልሆኑ ወይም የሙያ ፕሮግራሞችን ለሚከታተሉ።
° ጄ ቪዛ (J-1/J-2)፡
ለተፈቀደላቸው የልምድ ልውውጥ መርሃ ግብሮች፣ የሁለተኛ ደረጃ እና የዩኒቨርሲቲ ጥናቶች፣ የባህል ልውውጥ ፕሮግራሞችን ጨምሮ በስራ እና በጥናት ላይ የተመሰረተ የልምድ ልውውጦችን ለሚያደርጉ አካላት የሚሰጥ ቪዛን ያመላክታል።
በተጠቀሱት የቪዛ አይነቶች ጥያቄያቸው ያቀረቡ አመልካቾች የማህበራዊ ሚዲያ አጠቃቀም እና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ጥልቅ እና ሁሉን አካታች ማጣራት እንደሚያካሂድ ኤምባሲው አሳውቋል።

