ግብፅ ወታደሮቿንና ጦር መሳሪያዎችን በሶማሊያ ማሰማራት ጀምራለች
የግብፅ ወታደሮች፣ መሳሪያዎችና ወታደራዊ አውሮፕላኖች የሶማሊያ መዲና ሞቃዲሾ መድረሳቸው ተገለጸ። ይህ ሂደት 10 ሺህ የሚደርሱ የግብፅ ወታደሮችን በሶማሊያ ለማሰማራት የታቀደው አካል ነው።
ወታደሮቹ በኢትዮጵያና በሶማሊያ ድንበር አካባቢ ማለትም በጌዶ፣ በሂራን እና በባይ ባኮል ስፍራዎች ላይ እንደሚሰፍሩ እየተገለጸ ይገኛል።
የሶማሊያ ፕሬዝዳንት ሀሰን ሼክ ሞሃሙድ እና የግብፁ ፕሬዝዳንት አብዱል ፈታህ አል ሲሲ በካይሮ በቅርቡ የተፈራረሙትን የመከላከያ ስምምነት ተከትሎ c-130 የተባሉ ሁለት የግብፅ ወታደራዊ አውሮፕላኖች በአደን አዴ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ አርፈዋል ተብሏል።
ግብጽ ወታደሮቿንና የጦር መሳሪያዎችን በሶማሊያ ያሰማራችው በቅርቡ በኢትዮጵያ እና በሶማሊላንድ መካከል የተፈረመው የባህር በር የመግባቢያ ስምምነትን ተከትሎ በቀጠናው ውጥረት በነገሰበት ወቅት ነው።
የሁለቱ ወታዳራዊ ትብብር በፈረንጆቹ 2025 የአፍሪካ ህብረት የሽግግር ተልዕኮ በሶማሊያ (አትሚስን) ለመተካት በታቀደው በሶማሊያ የአፍሪካ ህብረት የድጋፍ ተልዕኮ AUSOM አካል መሆኑ ቢገለፅም – በሶማሊያ የግብፅ ጦር መገኘት ታላቁ የህዳሴ ግድብን በመቃወም ኢትዮጵያ ላይ ዙሪያ ለቋጠረችው ቂም እንዲሁም በአፍሪካ ቀንድ ለሚኖረው ፍላጎቶች እንደ ስትራቴጂካዊ እርምጃ ተደርጎ ይወሰዳል ሲል የፑትላንዱ ጋሮዌ ኦንላይን መጣጥፍ ይጠቁማል – ይህም ከግብፁ ሰሞንኛ እንቅስቃሴ ጀርባ በርካቶች የሚስማሙበት መነሾ ነው።
(እስሌይማን አባይ)



