አዋጁ ሲወጣ በደቦ ለቅሶ ሲጀመር “የያዙትን ሃብት እንዴት እንዳፈሩት ባለቤቶቹ ያውቁታል፤ ይህ ግልጽ ነው” ሲሉ ህጉን ያረቀቀው ቡድን አባል ተናግረው ነበር። እንደውም እንደኔ አስተያየት ለቅሶው ከፍየሏ ሞት በላይ ነው እንደሚባለው ነው። ሲሉ ነበር ኃላፊዋ ያስታወቁት። በወንጀል የተገኘን ንብረት ህጋዊ ማስመሰል እና ሽብርተኝነትን በገንዘብ ለመርዳት እንደሚውልም ዝርዝር ቀርቦ የህጉ አስፈላጊነት በዝርዝር አውዱን ያሳቱት የደቦ አልቃሾች እንደሚሉት እንዳልሆነ መገለጹ ይታወሳል። ዛሬ ደግሞ ዝመቻው የሚጀመርበት ጥርጊያው መጠናቀቁ እየተሰማ ነው።
ከፋይናንስ ስርዓትና ቁጥጥር ጋር በተያያዘ በርካታ አዋጆች ከመውጣታቸው በላይ የተለያዩ ደንቦችና የአሰራር ሂደቶች ተዘጋጅተው መረጃዎች በቋት የሚከዘኑበት ሁኔታ ስራ ላይ ውሏል። ይህን የሚናገሩ እንደሚሉት በአገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን ከአገር ውጪም ዝርፊያን አስመልክቶ ሰፊ ስራ ተሰርቷል።
አዲሷ የፍትህ ሚኒስትር ከዚህ ቀደም ያሉት ሕጎች ውስንና የተበታተኑ መሆናቸውን፣ የሀብት ማስመለስን በሚመለከት ሁሉን አቀፍና አንድ ወጥ የሆነ ሕግ ማዘጋጀት አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሰው፣ “የኢኮኖሚ ወንጀሎች ድንበር ተሻጋሪና ከፋይናንስ ጋር የተያያዙ በመሆናቸው ረቂቅ አዋጁ ይህንን ለማስቀረት ድንበር ተሻጋሪ ሥራዎችን መሥራት የሚያችል ነው” ማለታቸውን ሰሞኑን ከቁልፍ የአፍሪካ አገራት፣ ከቱርክ፣ ከአረብ ኤምሬትስ፣ ከአንግሊዝ፣ ቻይና፣ አካሜሪካና የፍትህ ተቁማት ጋር ውል ማሰሩን፣ እንዲሁም ከኢንተርፖል ጋር በስፋት ግንኙነትና ስምምነት እየተፈጠረ እንደሆነ ፌድራል ፖሊስ ከሚያሰራጨው ዜና ጋር የገናኙትም አሉ።
“…የኛም አዲሱ የሀብት ማስመለስ ረቂቅ ህግ ይህን ችግር ይቀርፋል ተብሎ ይታመንበታል። ከአዋጁ ጀርባ ያለው ምክንያት ወንጀል አትራፊ መሆን የለበትም የሚል ነው። እውነታው ይህ ሆኖ ሳለ ለቅሶው ከየት የመነጨ ነው የሚል ጥያቄ ማንሳት ያስፈልጋል። እውነት ለዜጎች መብት ከመቆርቆር ወይንስ የቀማኞች መደብ እንዲንሰራራ ከመፈለግ ነው? እንደኔ አስተያየት ግን ለቅሶው ከፍየሏ ሞት በላይ ነው እንደሚባለው ነው”
“ለሃብታቸው መነሻ ምንጩን ማቅረብ የሚችሉ ሁሉ አይፈሩም፤ ምንጩ የማይታወቅ ሃብት በሙሉ ህገወጥ ነው። ህገ ወጥነትን አይዋጋም የሚባል መንግስት፣ ሌብነትና ሌቦች ላይ ለመዘመት ህግ ሲያዘጋጅ የሚፈሩና ከፍርሃት በመነሳት የሚንጫጩ የጉዳይ ዋና ተዋንያኖች ካልሆኑ በቀር አጥንቱን የሚጋጠው ህዝብ አይደለም….” ሲሉ አዋጁ ንብረቱን ከየት እንዳመጡት የሚያውቁትን ካልሆነ በስተቀር ሕዝብን እንደማይጎዳ ህጉን ያዘጋጁት አመልክተው ወደ ተግባር ለመግባት ቀጠሮ ይዘው ነበር።
አዋጁን አስደንጋጭ ያደረገርው በመክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተነስገን ጥሩነህ የሚመራ ብሄራዊ የጸረ ሙስና ኮሚቴ በዝግ አገሪቱ ላይ በዝርፊያ የተገነቡ፣ የተገዙና የተቋቋሙ ድርጅቶችን በጥቆማ አጥርቶና ማስረጃ ሰብስቦ ወደ ተግባር ለመግባት ዝግጅት ላይ መሆኑን ተከትሎ እንደሆነ በወቅቱ ሲገለጽ ነበር። በአገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን በአንዳንድ አፍሪካ አገራት፣ በዱባይ፣ በቱርክ፣ እንዲሁም በአውሮፓና አሜሪካም የተዘርፈ ሃብት መሸሹ ማስረጃ እንደተሰበሰበበት ለጉዳዩ ቅርብ የሆኑ ወገኖችን ጠቅሰን መዘገባችን አይዘነጋም። መንግስትም ከአንዳንድ አገራት ጋር ሃብት የማስመለስ ስራ መጀመሩን አስታውቆ ነበር።
“የተሰማው ዜና መቼ ነው ተግባራዊ የሚሆነው?” በሚል የተለያዩ ጥያቄዎች በየአቅጣጫው ሲሰሙ ስንብተዋል። በአገሪቱ ውስጥ እዛና እዚህ መልክና ስፍራ እየቀያየረ የሚነሳው “ባለቤትና የራሳቸው ድብቅ ዓለማ አላው” የሚባለው ግጭቶች የራሳቸው ጫና እንዳሳደሩ ጠቅሰው የሚናገሩም ጥቂት አይደሉም።
ምንጩ ያልታወቀ ንብረት ማፍራት በአፍሪካና በተለያዩ ታዳጊ ሀገራት ትልቅ ሀገራዊ ችግር ሆኖ ቆይቷል። ቀደም ሲል ምንጩ ያልታወቀ ንብረት ማፍራት ተጠያቂነትን ለማስከተል በተደረገው ጥረትም ከሕግና ፍትሕ አካላት በኩል ርምጃ ለመውሰድ የሚያስችል ሙሉ የሕግ ማሕቀፍ እንደሌለና መረጃዎችም የተጠናከሩ አለመሆናቸው ለተግባራዊነቱ ችግር መሆኑን ግይዳዩ የሚመለከታቸው ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ውስጥ ችግሩ መኖሩ ቢታወቅም ወንጀሉን ለመከላከል ምንጩ ያልታወቀ ንብረት መውረስን መሠረት ያደረገው የንብረት ማስመለስ ረቂቅ አዋጅ ከግለሰቦች ሕገ መንግሥታዊ መብቶች ጋር እንዲጣጣም አድርጋ እያዘጋጀች እንደምትገኝ የኢዜአ ዘገባ ያስረዳል።
ምንጩ ያልታወቀ ንብረትንም ረቂቅ አዋጁ ከወጣበት ጊዜ ብቻ ሳይሆን አዋጁ ተግባራዊ ከመደረጉ በፊት እስከ 10 ዓመት እንዲሁም 10 ሚሊዮን ብርና ከዛ በላይ ያሉትንም ጉዳዮች ተጠያቂ እንደሚያደርግ አዋጁ አስቀምጧል፡፡ አዋጁ ወደሁዋላ አስር ዓመት ተመልሶ እንዲሰራ መደረጉ አንዱ የጫጫታው መነሻ ቢሆንም ህጉን ያወጡት ” በቀላል አማርኛ ገቢያችሁ ይህን ያህል ነው። ይህን ሃብት ማፍራት አትችሉም። ከየት እንዳመጣችሁት አስረዱ ነው የሚባለው” ካሉ በሁዋላ ቀደም ሲል ወንጀለኛ ቢጠየቅ እንኳን የተዘርረፈውን ንብረት ቤተሰብ እንደሚጠቀምበት አመልክተው፣ ይህ አሰራር መቀጠል እንደማይገባው አስረድተዋል። በህገወጥ የተገኘ ንብረት ወደ ተገቢው አካል እንዲመለስ እንደሚደረግ ገልጸዋል።
ተወካዮች ምክር ቤት የሕግና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምንጩ ከማይታወቅ ንብረት ማስመለስ ረቂቅ አዋጅ ዙሪያ ከፍትሕ ሚኒስቴር የሥራ ኃላፊዎችንና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ሰሞኑን ውይይት አድርጓል።
ለመሆኑ የንብረት ማስመለስ አዋጅ ፋይዳው ምንድነው፤ አዋጁ ያሉበት ስጋቶችስ የሚሉ ጉዳዮች ላይ የተለያዩ የሚመለከታቸው አካላት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
በፌዴራል ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ምንጩ ያልታወቀ ሀብት ማጣራት መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ አዳነ መለሰ ፤ በሥራ ላይ ያለው የንብረት ማስመለስ አዋጅ ውስንና ወጥ አለመሆን፣ መንግሥት የኢኮኖሚ ወንጀሎችን ለመከላከል ካለው ቁርጠኝነት እንዲሁም ኢትዮጵያ የፈረመቻቸው ዓለም አቀፍ ሕጎች ለአዋጁ መውጣት ምክንያት መሆናቸው ያነሳሉ፡፡
ረቂቅ አዋጁ ምንጩ ያልታወቀ ሀብት የፍትሐብሔር ተጠያቂነት በሁሉም ሰውና በሕግ ሰውነት ባላቸው ተቋማት ላይ ተፈፃሚ እንደሚሆን ያስቀመጠ ነው ይላሉ፡፡
የአዋጁ መነሻ ሃሳብ ከተባበሩት መንግሥታት ፀረ ሙስና ኮንቬንሽን የመነጨ መሆኑንና ወቅታዊና አስፈላጊ በመሆኑ የሚደገፍ ነው ያሉት፡፡
የንብረት ማስተዳደርን በተመለከተ በአዋጁ የፍትሕ ሚኒስቴር ኃላፊነት እንደሚወስድ አመላክተው፤ ይህም ግልጽነት የጎደለው አሠራር እንዳያስከትል እራሱን የቻለ ነፃና ገለልተኛ ተቋም ቢቋቋም የተሻለ ይሆናል ሲሉ ይናገራሉ ፡፡
በንብረት ማስመለስ ሂደት የሚገኘው ሀብት በአዋጁ እንደተቀመጠው ከሆነ በፍትሕ አስተዳደር ዘርፍ ላይ ለተሠማሩ አካላት አቅም ግንባታ እንደሚውል ያመለክታል ያሉት አቶ አዳነ፤ ነገር ግን የፀረ ሙስና ትግል ብዙ ባለድርሻ አካላትን የሚያካትት በመሆኑ የሚገኘው ሀብት ለተለያዩ ተቋማት ለትውልድ ሥነምግባር ግንባታ ቢውል መልካም መሆኑን ይገልጻሉ ፡፡
በሌላ በኩል በሀብት ማስመለስ ሥራው ወንጀሉን የሚጠቁመው አካል ደኅንነት ለመጠበቅ እንዲያስችልም የመረጃ ማሰባሰብ ሥራው ዲጂታል መሆን አለበት፡፡ ይህም በአዋጁ በግልጽ መቀመጥ ይኖርበታል ይላሉ፡፡
የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ጌታቸው ዋቄ እንደሚሉት፤ በረቂቅ አዋጁ አንቀጽ 25 ላይ በሚወረስ ንብረት ላይ ሦስተኛ ወገን መብት ካለ ማስረጃ አቅርቦ ማስቀየር ይችላል የሚል ሲሆን እዛው አንቀጽ ላይ ንዑስ ቁጥር አራት ላይ ግን በዋናው ገንዘብ ብቻ ይላል፡፡ ይህም በተለይም ባንኮች በንብረት የሚመሠረቱትን የመያዣ መብት የሚገድብና የወለድ ማስከፈል መብታቸውን የሚከለክል በመሆኑ መታየት ይኖርበታል፡፡
“በአሁን ወቅት ዓለምን በከፍተኛ ደረጃ ከሚያሰጓት ነገሮች ውስጥ አንዱ ሽብርተኝነት ነው። በእርግጥ በሕገወጥ መንገድ የተገኘ ገንዘብና ንብረት የሽብር ወንጀል ብቻ ሳይሆን ለሌሎች በርካታ ወንጀሎችም መፈፀሚያ መሣሪያ ሲሆን እንደየሽብር ቡድኑ አደረጃጀት፣ ዓላማና ሁኔታ ይለያይ እንጂ አብዛኞቹ የሽብር ወንጀሎች የሚፈጸሙት ሕጋዊ ባልሆነ መንገድ የተገኘ ገንዘብና ንብረትን በመጠቀም ነው”
በሌላ በኩል የሚወረሰው ንብረት ፋብሪካ አልያም ሌላ ንብረት ሊሆን ይችላል የሚሉት አቶ ጌታቸው፤ ይህም የሚተዳደርበት ሥርዓት እና የሚበላሹ ንብረቶች የሚወገዱበት ሥርዓት በአዋጁ በግልጽ ቢቀመጥ የተሻለ ይሆናል ይላሉ፡፡
አቶ ጌታቸው፤ የንብረት ግምት ማውጣት ለአዋጁ ተፈጻሚነት ፈታኝ የሚሆን ጉዳይ ነው ሲሉ ገልጸው፤ ኢትዮጵያ ውስጥ ንብረት የሚገምት ተቋም ባለመኖሩ ገማች ተቋም ማቋቋም አስፈላጊ ይሆናል ሲሉ ይናገራሉ፡፡
በዋናነት አዋጁ የፋይናንስ ተቋማትን የብድር ሥርዓት ሊያዛባና ባንኮችም የሰጡት ብድር ተመላሽ እንዳይሆን ስለሚያደርግ በጥንቃቄ ሊታይ እንደሚገባ ይገልጻሉ፡፡
ስለአዋጁ ዓላማ ማብራሪያ የሰጡት የፍትሕ ሚኒስትር ወይዘሮ ሐና አርዓያሥላሴ በበኩላቸው፤ የሀብት ማስመለስ አዋጁ በሀገሪቱ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሰ ያለውን የኢኮኖሚ ወንጀል ለመከላከልና ለመቆጣጠር አስፈላጊ ነው፡፡ በሕገ-ወጥ መንገድ የተገኙ ንብረቶችን ለማስመለስም ቁልፍ ሚና አለው ይላሉ።
ከዚህ ቀደም ያሉት ሕጎች ውስንና የተበታተኑ መሆናቸውን አንስተው፤ የሀብት ማስመለስን በሚመለከት ሁሉን አቀፍና አንድ ወጥ የሆነ ሕግ ማዘጋጀት አስፈላጊ መሆኑንም ነው ያስረዱት።
የኢኮኖሚ ወንጀሎች ድንበር ተሻጋሪና ከፋይናንስ ጋር የተያያዙ በመሆናቸው ረቂቅ አዋጁ ይህንን ለማስቀረት ድንበር ተሻጋሪ ሥራዎችን መሥራት የሚያችል ነው ሲሉ ያስረዳሉ።
ምንጩ ያልታወቀ ሀብት በዚህ አዋጅ የፍትሐብሔር ተጠያቂነት በሁሉም ሰውና በሕግ ሰውነት ባላቸው ተቋማት ላይ ተፈፃሚ እንደሚሆን አንስተው፤ ምንጩ ያልታወቀ ንብረትን አዋጁ ከወጣበት ጊዜ ብቻ ሳይሆን አዋጁ ከመውጣቱ በፊት እስከ 10 ዓመት ያሉ ጉዳዮችን ማየቱ የሀገሪቱን የመረጃ አያያዝ ከግምት ውስጥ በማስገባት መሆኑን ያብራራሉ፡፡
አዋጁ ወጥ የሆነ የንብረት ማስመለስ አስተዳደር ሥርዓት ሊዘረጋ የሚችልና በወንጀል የተገኘ ንብረትን የማስመለስ፣ ማጣራት፣ መያዝ፣ ማገድና መክሰስ የሚሉ በዝርዝር ጉዳዮችን የሚያስቀምጥ መሆኑንም ነው ያስታወቁት

