” ቅልጥ አለቱ በመሬት ውስጥ ተረጋግቶ ሊቀርም ወይም ወደ መሬት ላይ ሊፈስም ይችላል። ይህንን በሂደት የምናየው ነው ” – ኤልያስ ሌዊ (ዶ/ር)
በአፋር ክልል፣ ፈንታሌ ተራራ አካባቢ ባለፉት ሳምንታት በተደጋጋሚ የመሬት መንቀጥቀጥ እየተከሰተ መሆኑ ይታወቃል።
አደጋው ትላንት ምሽት ከለሊቱ 6:04 ላይ በዚሁ አካበቢ የተከተሰተ ሲሆን፣ ንዝረቱም አዲስ አበባ ድረስ መሰማቱ ታውቋል።
ስለትላንቱ ርእደ መሬትና መንስኤው ሙያዊ ማብራሪያ እንዲሰጡበት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፤ የጂኦፊዚክስ፣ ስፔስ ሳይንስና አስትሮኖሚ ተቋም ዳይሬክተር የሆኑትን ኤሊያስ ሌዊ (ዶ/ር)ን ጠይቀናል።
እሳቸውም፣ ” የየቀን ተግባራችንን እያከናወንን ክስተቱ የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ በንቃት ሁኔታወን ቢከታተሉ ጥሩ ነው ” ብለዋል።
” ይሄ በአሁኑ ወቅት በፈንታሌ አካባቢ እየተከሰተ ያለው ርዕደ መሬት፤ ቅልጥ አለት (ማግማ) መሬት ውስጥ ከሚያደርገው እንቅስቃሴዎችና ተዛማጅ ሁኔታዎች ጋር የተገናኘ እንደሆነ ቀደም ሲልም አስታውቀናል።
ቅልጥ አለቱ መሬት ውስጥ የሚያደርገው እንቅስቃሴ የቀነሰ ቢመስልም አልተቋረጠም።
እዚህ ሰሞኑን ከሚሰማው የመሬት መንቀጥቀጥ ጋር ተያይዞ ፤ በወፍ በረር 130 ኪ.ሜ ላይ የሚገኘው ፈንታሌ አካባቢ እየተከሰተ ያለው የቅልጥ አለት እንቅስቃሴ ግን ወዴት እንደሚያመራ አናውቅም።
ይህ ቅልጥ አለት በመሬት ውስጥ ተረጋግቶ ሊቀርም ወይም ወደ መሬት ላይ ሊፈስ ይችላል። ይህንን በሂደት የምናየው ነው።
ተቋማችን ባለው አቅም እንዲሁም በሀገር ውስጥና በዓለም ዓቀፍ ደረጃ አብረውን ከሚሰሩ ባለሙያዎች ጋር ግንኙነቶችን በማድረግ ሳይንስ የደረሰበት የእውቀት ደረጃን በሙሉ ለመተግበር የሚገባውን በማድረግ ላይ እንገኛለን።
የእኛ ተቋም የምርምር ተቋም በመሆኑ የሚያከናውነው ይህ ርዕደ መሬት የት ተከሰተ? መጠኑ ስንት ነው? መንስኤው ምንድነው ? የቅልጥ ዓለቱስ እንቅስቃሴ ወዴት ሊያመራ ይችላል ? እና የመሳሰሉ ሃሳቦች ላይ መመራመር ሲሆን፤ ይህንን የምርምር ውጤትም ግብአት አድርገው ባለድርሻ አካላት ከዚህ በኋል መሰራት ያለባቸውን ሥራዎች ይሰራሉ። “
ምናልባት የቴክኖሎጂ እጥረት ይኖር ይሆን ? አደጋውን መቆጣጠር የሚቻልበት የተለዬ ሁኔታስ የለም ? ስንል ላቀረብንላቸው ጥያቄ ኤልያስ (ዶ/ር) ማብራሪያ ሰጥተዋል።
” እየተከሰተ ያለውን ርእደ መሬትም ሆነ የቅልጥ አለት እንቅሰቃሴን ሂደት በቅርብ መከታተል የሚቻል ሲሆን፤ ማቆምም ሆነ መቆጣጠር ግን አይቻልም።
እኛ ብቻ አይደለንም በዓለም ላይ ያሉ ማናቸውም ባለሙያዎች መቆጣጠርና ማቆም አይችሉም። በፈንታሌ አካባቢ ያለውን ሁኔታ እኛ ብቻችን ሳይሆን፤ ሀገር ውስጥና በዓለም አቀፍ ደረጃ ካሉ ተባባሪ ባለሙያዎች ጋር በቅርብ ምክክር በማድረግ እየሰራን ነው።
የእኛ ዩኒቨርሲቲም ሆነ ኢንስቲትዩታችን በዚህ ሥራ ላይ የተሰማሩ ብቁ የሆኑ ባለሙያዎችና ለዚህ ተግባር የሚያገለግሉ ዘመናዊ የሆኑ መሳሪያዎች ያሉት ቢሆንም፣ ዓለም የደረሰበት ሁሉም ዓይነት መሰሪያዎች ግን አሉን ማለት አይደለም።
ለምሳሌ የርቀት ዳሰሳ ወይም ሪሞት ሴንሲንግ የሳተላይት መረጃዎችን የሚያሰባስቡ ሳተላይቶች ስለሌሉን ከዓለም ዓቀፍ ማዕላት መረጃ በመቀበል፣ በመተንተንና ከተባባሪዎቻችን ጋር ሆነን በመቀመር እንሰራለን።
በኢትዮጵያ ውስጥ በተለያዩ ቦታዎች መረጃ እንዲያሰባስቡ የተከልናቸው የርእደ መሬትና የGNSS መረጃ ማጠናቀሪያ ጣቢያዎች በዓለም ላይ ደረጃቸውን የጠበቁ ሲሆኑ፤ ብዛታቸውን ግን አሁን ካለው በላይ ማስፋፋት ይጠበቃል።
ይህ ደግሞ መጠነ ሰፊ መዕዋለ ንዋይን ማፍሰስ ይፈልጋል። ከዚህም በተጨማሪ ከቦታ ቦታ ተዘዋውሮ አሁን ከተጠቀምንበት ተጨማሪ መረጃዎችን ለመሰብሰብ በአሁኑ ወቅት አስቸጋሪ ስለሆነ ባለን ለመስራት እየተጋን ነው።
ምንም እንኳን ተጨማሪ ጣቢያዎች ያስፈልጉናል ቢባልም፣ ፈጣሪ ይመስገንና በዓለም ደረጃ ስመጥር በሆኑ ባለሙያዎቻችን የማያሰልስ ጥረትና ችሎታ ትክክለኛውን መረጃ ከማንም ባላነሰ መልኩ እያቀረብን እንገኛለን።
አሁን የሚጠበቀው ይህንን መረጃ ወስዶ በተቀናጀ መልኩ ምናልባት ሊፈጠር ከሚችል አደጋ ለመከላከል ዝግጁ መሆን ነው። እኛ የአንድ ዩኒቨርሲቲ የምርምር ማዕከል ነን። ከዚህ ውጭ ያለው ሥራ ግን የሌላ ብዙ ባለድርሻ አካላትን መቀናጀትን ይጠይቃል።
አሁን እያደረግን ካለው ውጭ የማድረግ ማንዴቱም የለንም ተልእኳችንም አይደለም። ይህም ሆኖ ግን የሚቻለውን ሁሉ ለማድረግ ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር የሚቻለንን ሁሉ እያደረግን ነው ” ብለዋል።
አደጋውን በተመለከተ መደረግ ስላበት የጥንቃቄ ሥራ ባስተላለፉት መልዕክት ደግም፣ ” እንዳንዘናጋ ! የእለት ከእለት ተግባራችንን እያከናወንን በንቃት ሂደቱን እንከታተል ” ሲሉ አስገንዝበዋል።
” የስምጥ ሸለቆዎች ባሉበት ሀገር ስለሆነ የምንኖረው ክስተቱ በታየበት ሰሞን ብቻ ሳይሆን፣ አኗራራችን፣ ግንባታዎቻችን፣ አስተሳሰባችን፣ የትምህርት ካሪክለሞቻችን ባጠቃላይ ዝግጁነታችን በዚሁ የተቃኘ መሆን አለበት ” ነው
Via tikvahethiopia



