በሶማሊያ የውጭ ጉዳይና ዓለም አቀፍ ትብብር ሚኒስትር ዴኤታ የተመራ ልዑክ የአንካራውን ስምምነት ተግብራዊ ለማድረግ አዲስ አበባ መግባታቸውንና “የአንካራውን ስምምነት አደናቃፊዎችን እንታገላለን” እያሉ ባሉበት ተመሳሳይ ቀን ግብጽ በአዲሱ የሶማሊያ ሰላም አስከባሪ ኃይል ውስጥ ተሳትፎ እንዳላት ዳግም ይፋ አደረገች።
በአዲሱ የሶማሊያ ሰላም አስከባሪ ኃይል ውስጥ እንደምትሳተፍ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯ ያስታወቁት የሶማሊያ ከፍተኛ ባለስልጣናት በአዲስ አበባ የአንካራውን ስምምነት ለማጽናት እየመከሩ ባለበት ወቅት ነው።
የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጀነራል አቶ ሬድዋን ሁሴን ከልዑክ ቡድኑ አባላት መካከል አንዱ የሆኑትን የሶማሊያ የብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ ዳይሬክተር አብዱላሂ መሐመድ አሊ ጋር መወያየታቸውን አስታውቀዋል።
አቶ ሬድዋን ሁሴን ከሶማሊያ የብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ ዳይሬክተር አብዱላሂ መሐመድ አሊ ጋር በኢትዮጵያና ሶማሊያ መካከል ስላለው ግንኙነትና ቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎች ዙሪያ መምከራቸውን ገልጸዋል።
ሁለቱ ሀገራት ከአንካራው ስምምነት በኋላ ያሉ አደናቃፊዎችን ለመታገልና ወደ ፊት ለመጓዝ ቁርጠኛ መሆናቸውን በኤክስ ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ገልጸዋል።
ኢትዮጵያና ሶማሊያ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን ለማሻሻል በአንክራ ስምምነት ከፈጸሙ በሁዋላ የኢትዮጵያ ጦር በሶማሊያ ስለመቀጠሉ ቃል በቃል የተሰጠ መረጃ ባይኖርም፣ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ለሶማሊያ ደህንነት የከፈለውን መዋዕትነት እንደሚያከብሩ፣ ዋጋ እንደሚሰጡ ፕሬዚዳንት ሃሰን ሸሪፍ መናገራቸው ይታወሳል። ከዛም በተከታታይ ጉዳዩን እንደሚያጤኑት ማስታወቃቸው አይዘነጋም።
ሶማሊያ “የኢትዮጵያ ጦር ከሶማሊያ ይውጣ ብትል እንኳን ሊሆን እንደማይችል፣ ከብሄራዊ ጥቅሟና ሰላሟ አንጻር ጥያቄውን ውድቅ ታደርገዋለች። ስለዚህ ፕሬዚዳንት ሃሰን በጉልበት ከመሸነፍ በሰላም ድርድሩ ሰበብ ፈቃደኛ በመሆን ተጠቃሚ ይሆናል” ሲሉ የሶማሊያ ተንታኞች ለአሜሪካ ሬዲዮ መናገራቸው ይታወሳል።
በትላንትናው እለት በሶማሊያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የተመራ ልዑክ ወደ አዲስአበባ ማቅናቱን ተከትሎ ግብጽ አትሚስን በሚተካው በአዲሱ በሶማሊያ የአፍሪካ ህብረት የድጋፍ ተልዕኮ (AUSSOM) ውስጥ እንደምትሳተፍ የሀገሪቱ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እንደ አዲስ መግለጫ የሰጡበት ምክንያት ይፋ ባይሆንም “ግብጽ በአደባባይ ተሸነፈች። የሶማሊያም እቅዷ ከሽፏል” ለሚለው ወቀሳ ማስተንፈሻ በሚል ታስቦ እንደሆነ ተገምቷል።
የግብጽ ታዋቂ አክቲቪስቶች ከሎንዶን በተከታታይ ባሰራጩት መረጃ አልሲሲ በአደባባይ በዲፕሎማሲ መሸነፋቸውን እያስታውቁ ነው። ቀደም ሲል በህዳሴ ግድብ ተሸነፉ፣ አሁን ደግሞ በሶማሊያ ዳግም ሽንፈት ተከናነቡ በሚል የግብጽ ህዝብ እንዲቃወም ጥሪም እያድረጉ ነው። የሶማሊያ ባለስልጣናት የአንካራውን ስምምነት ለማጽናት አዲስ አበባ መገኘታቸውን ተከትሎ ግብጽ ድምጿን ያሰማችው ተቃውሞውን ለማርገብ ነው።
በኢትዮጵያ እና ሶማሊያ መካከል በሶማሊላንድ የወደብ የመግባብያ ስምምነት መፈረሙን ተከትሎ በተፈጠረው የዲፕሎማሲ ውጥረት ግብጽ አጋጣሚውን በመጠቀም ወደ ሞቃዲሾ መሳሪያ አንጋግታ መግባቷ አይዘነጋም።
የግብጽ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ባድር አብዳላቲ ካይሮ ከሶማሊያ መንግስት በቀረበላት ጥያቄ መሰረት በአዲሱ የሰላም ማስከበር ተልዕኮ ላይ እንደምትሳትፍ ምንም አዲስ ነገር ሳያክሉ ገልጸዋል።
ሚኒስትሩ አክለውም “ሶማሊያ ሉዓላዊነቷን በሁሉም የሶማሊያ ብሔራዊ መሬት ላይ እንድታስከብር ፣ አንድነት እና ደህንነቷን የሚነኩ መመሪያዎችን ወይም የአንድ ወገን እርምጃዎችን ለመቃወም የምታደርገውን ጥረት እንደግፋለን”
ግብጽ በሚኒስትሯ አማካይነት ይህን ብትልም፣ የሶማሊያና የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ተመሳሳይ መግለጫ ሰጥተዋል። “ኢትዮጵያ ለአንካራው ስምምነት ተግባራዊነት ቁርጠኝኛ ናት” የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዲኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ ሲያስታውቁ፣ “ሶማሊያ የአንካራው ስምምነት በተፋጠነ ሁኔታ እንዲተገበር ትሻለች” ብለዋል።
በውይይቱ ስለተነሱ ጉዳዮች ዝርዝር ጉዳይ ባይነሳም ኢትዮጵያና ሶማሊያ ተባብሮ መስራት፣ ችግሮች ሲጋጥሙም ተቀራርቦ መፍትሄ መሻት እንደሚገባቸው መተማመናቸውን ይፋ አድርገዋል። ኢትዮጵያ ለሶማሊያ ሰላም ከፍተኛ መስዋዕትነትን እንደከፈለች አምባሳደር ምስጋኑ በውይይቱ ላይ ማንሳታቸውና የሶማሊያ አቻቸው እውቅና እንደሰጡ ተሰምቷል።
የሶማሊያ የውጭ ጉዳይና ዓለምአቀፍ ትብብር ሚኒስትር ዲኤታ አሊ መሃመድ ኦማር በበኩላቸው “ሶማሊያ የአንካራው ስምምነት በተፋጠነ ሁኔታ እንዲተገበር ትሻለች” ሲሉ በይፋ የአግራቸውን አቋም አስታውቀዋል። በአዲስ አበባ መገኘታቸውም ለስምምነቱ ተፈፃሚነት ሀገራቸው ያላትን ዝግጁነት እንደሚያሳይ ጠቅሰው ለጋራ እድገት የሶማሊያ መንግሰት ከኢትዮጵያ ጋር በትብብር ይሰራል ብለዋል።
ሁለቱ አገራ በሁለትዮሽና ቀጣናዊ ጉዳዮች ተቀራርበው ለመስራት ስምምነት ላይ መድረሳቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ይፋ አድርጓል። ተካሮ የነበረው የሁለቱ አገራት ዛሬ ባለበት ደረጃ ደርሶ የሰላም ንግግሩ በተጠናከረበት ወቅት፣ ቀደም ሲል በሁለቱ ጎረቤት አገራት መካከል ተነስቶ የነበረውን ቅሬታ በመታከክ ተከትሎ ግብጽ በአዲሱ የሰላም አስከባሪ ሀይል 5 ሺህ ፣ ከሶማሊያ ጋር በሚደረግ የሁለትዮሽ ስምምነት ደግሞ ተጨማሪ አምስት ሺ ወታደሮችን የማስፈር ፍላጎት እንዳላት ስታስታውቅ መቆየቷ አይዘነጋም።
የጦር መሳሪያዎችን፣ወታደራዊ አማካሪዎችን፣ አሰልጣኞችን እና የፀረ ሽብር ኮማንዶዎችን አስቀድማ ወደ ሞቃዲሾ ያጓጓዘችው ግብጽ ኢትዮጵያና ሶማሊያ በአንካራ ያደረጉት ስምምነት እንዳላስደሰታት መዘገቡ ይታወሳል።
በሶማሊያ የአፍሪካ ህብረት የድጋፍ ተልዕኮ (አውሶም) በ2024 መጠናቀቂያ ከቀናት በኋላት አትሚስን በመተካት የሚሰማራ ይሆናል፡፡
በቱርክ አደራዳሪነት ከአመት በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ በአንካራ ፊት ለፊት የተገናኙት የአዲስ አበባና ሞቃዲሾ መሪዎች በመካከላቸው የተፈጠረውን ልዩነት በውይይት ለመፍታት ባደረጉት ስምምነት መሰረት በሚኒስትሮች ደረጃ በአዲስ አበባ ቀጣይ ውይይት እያካሄዱ ነው።
የሶማሊያ የውጭጉዳይ ሚኒስትር ትላንት ባወጣው መግለጫ በሀገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አሊ ኦማር የተመራ ልዑክ ወደ አዲስአበባ እንደሚያቀና ማረጋገጫ በሰጠ በሰዓታት ውስጥ ግብጽ ይህን ማለቷ ለጊዜው “አትርሱኝ” ከማለት የዘለለ ትርጉም እንደማይኖረው እየተገለጸ ነው።


