ስልጣን ከተረከቡ 48 ሰዓት ያልሞላቸው የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሩስያን አስጠነቀቁ።
ዶናልድ ትራምፕ “ትሩዝ ሶሻል” በተባለው የራሳቸው የትስስር ገጽ ላይ ባሰፈሩት መልዕክት ሩስያ ከዩክሬን ጋር ሰላም ካልፈጠረች ከባድ ቅጣት ይጠብቃታል።
ተንታኞች እንደሚሉት፣ ትራምፕ ይህንን እያሉ ያሉት በሩስያና በዩክሬን መካከል ሰላምን ለማምጣት ቃል መግባታቸውን ተከትሎ ከወዲሁ ጫና በመፍጠር ስምምነት ላይ እንዲደርሱ ለማድረግ ነው።
ሞስኮ በዩክሬን ያለውን ጦርነት ለማስቆም በቅርቡ ስምምነት ላይ መድረስ ካልቻለች ዩናይትድ ስቴትስ ሩሲያን በአዲስ የንግድ ማዕቀቦች ትቀጣለች ሲሉ ነው ትራምፕ መልዕክታቸውን ለፑቲን ያስተላለፉት።
“ስምምነት ካላደረግን ሩሲያ ለዩናይትድ ስቴትስ እና ለተለያዩ ሌሎች ሀገራት በምትሸጣቸው ሸቀጦች ላይ ከበድ ያለ ታሪፍ እና ማዕቀብ ከማስቀመጥ ሌላ ምርጫ የለኝም” ብለዋል ትራምፕ በመልዕክታቸው።
“እኔ ፕሬዝዳንት ብሆን ኖሮ ይህ ጦርነት ፈጽሞ አይጀመርም ነበር በማለት ባይደንን ሸንቆጥ ያደረጉት ትራምፕ፣ ይህ ጦርነት እንዲያበቃ ቀላሉን መንገድ እንደሚከተሉም ገልጸዋል።
የባይደን አስተዳደር ሩስያ ዩክሬንን መውረሯን ተከትሎ አንዳንድ ማዕቀቦችን ቢጥልም በሩስያ የጋዝና የነዳጅ ንግድ ላይ ማዕቀብ ለማድረግ አልደፈረም።
የትራምፕ የግምጃ ቤት ኃላፊ ሰሞኑን ለኮንግረሱ እንደተናገሩት በሩሲያ የነዳጅ ዘይት ፋብሪካዎች ላይ ማዕቀብ መጣል ሩሲያን ወደ ጠረጴዛው ከሚያመጡ ነገሮች አንዱ ነው።
አሜሪካ ለዩክሬን የምትሰጠውን ወታደራዊ ዕርዳታ ላይም ከባይደን የተለየ ምልከታ ያላቸው ትራምፕ፣ በቅርቡ ከፑቲን ጋር ሊገናኙ እንደሚችሉም ጠቁመዋል።
ትራምፕ በጽሁፋቸው ላይ “ከፕሬዚዳንት ፑቲን ጋር ያላቸውን ጥሩ ግንኙነት” በመጥቀስ ሩሲያን “ለመጉዳት” አልፈልግም፣ ነገር ግን ስምምነት ላይ እንዲደረስ ግፊት አደርጋለሁ ሲሉ ገልጸዋል።
ለዩክሬኑ ፕሬዝዳንት ቮሎዲሚር ዘለንስኪ ቅርብ የሆኑ አንድ የዩክሬን ከፍተኛ ባለስልጣን ለትራምፕ በሰጡት አስተያየት “ፑቲን ጦርነቱን ማቆምም ሆን ስለሰላም ጫና እንዲደረግባቸው አይፈልጉም” ብለዋል.
የትራምፕ ልዩ መልዕክተኛ ኪት ኬሎግ በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ ለፎክስ ኒውስ እንደተናገሩት ትራምፕ በ “100 ቀናት” ውስጥ መፍትሄ እንደሚፈልጉ ተስፋ አድርገዋል።
ኬሎግ በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ በኪዬቭ ውስጥ ከከፍተኛ ባለስልጣናት ጋር ስብሰባዎችን ለማድረግ የያዙትን እቅድ ለሌላ ጊዜ አስተላልፈው እንደነበር ተነግሯል። ትራምፕ ይህንን ያደረጉት ሩሲያን ወደ ድርድር ለማምጣት እና ጦርነቱን ለማቆም እቅድ ስላልነደፉ ነው ሲሉ አንዳንድ ተንታኞች ተችተዋል ።
Via- ጋዜጣ ፕላስ


