በመጪው አዲሱ የትምህርት ዘመን ትምህርት ቤቶችን ማዕከል ያደረገ አመጽ ለማቀጣጠል በጀት መመደቡ ተሰማ። ኦሮሚያ ሕዝብ በተከታታይ በሚሞከሩ የአመጽ ጥሪዎች ተሳታፊ ባለመሆኑ ” ኦሮሚያ ሕዝብ አልነሳም ብሎናል” በሚል ግምገማ መደረጉም ታውቋል።
መረጃውን ያካፈሉን በቅርቡ “ትክክለኛ ነው” የተባለውንና መንግስትን ጨምሮ በርካቶች የደገፉትን ጥያቄ ይዘው የተነሱትን የህክምና ባለሙያዎች ሰላማዊ እንቅስቃሴ በመጥለፍ ወደ አመጽ እንዲሸጋገር በመናበብ ሲሰሩ የነበሩ ቡድኖች ናቸው ዕቅዱን የነደፉት።
የኢትዮሪቪው የዋሽንግቶን ዲሲ ተባባሪ እንዳለው በመጪው አዲስ የትምህርት ዘመን ትምህርት ቤቶችን የአመጽ ማዕከል ለማድረግ ኃላፊነቱን ወስደው የሚሰሩትን የሚያስተባበሩት መቀመጫቸውን በውጭ አገር ያደረጉና ሰላማዊ ትግል የሚሉ ቡድኖች ናቸው።
አመጹን ለማነሳሳት አዲስ አበባ የሚገኙ የሻዕቢያ ብር አስተላላፊዎች ተሳታፊ እንደሆኑም ተመልክቷል። ለዚሁ የአመጽ ማስፋፊያ ይሆን ዘንድ በጀት የተመደበ ሲሆን፣ ስራውን የሚያከናውኑ የየአካባቢ ኃላፊዎች ተመልመለዋል።
ትምህርት ሲጀመር ትምህርትን ከማስተጓጎል በተጨማሪ ቤተሰብ ልጆቹን ወደ ትምህርት ቤቶች እንዳይልክ ጫና የሚፈጥሩ የማህበራዊ ሚዲያ ሰራዊትና የመንደር ተዋናዮች መዘጋጀቱና ወጥ የሆነ ቅስቀሳ እንዲያካሂዱ ዝግጅት እየተደረገ ነው። ስራው በመናበብ የሚሰራና ከአንድ የፕሮፓጋንዳ ማዕከል የሚቀዳ ነው ተብሏል።
በጀቱ ከሚታወቁ ሁለት የውጭ መንግስታት መገኘቱ የተመለከተ ሲሆን፣ የሚውለውም አገር ቤት ሆነው አመጹን ለሚያስተባብሩና ይህንኑ አመጽ በዩቲዩብና በተለይም በፌስቡክ ለሚያሰራጩ እንደሆነ ተባባሪያችን አመልክቷል።
ተባባሪያችን እንዳለው አመጹን እንዲያስተባብሩና አገር አቀፍ እንዲያደርጉት የመምህራን ማህበርን አሳምኖ ለማስገባት ሙከራ ተጀምሯል። እንቅስቃሴው ቢጀመረም የመምህራን ማህበር ኃላፊዎችን ለማግባባት አለማቻሉ ተሰምቷል። ከዚያም በላይ በቅርቡ ከመምህራንና ከመምህራን ማህበር አመራሮች ጋር በተደረጉ ውይይቶች የተደረሰው ስምምነት እንቅፋት እንደሚሆን ተመልክቷል። በሁሉም አግባብ ካልተሳካ በገንዘብ ማህበሩን ለመክፈል ጥረት ሊደረግ እንደሚችል ተጠቁሟል።
ከሁሉም አቅጣጫ ጦርነት ለመክፈት በሲዳማ ጃዋር በገሃድ አደራጅቶ ሲረዳቸውና በሚዲያዎቹ ሲያስተዋቃቸው የነበረውን ኢጀቶ የተሰኘ ሴል፣ በሶማሌ ክልል አብዲሌ አደራጅቶት የነበረውን ጽነፈኛ የሂጎ ሴል፣ በደቡብ እስከ ወላይታ ወጣ ገባ የሚለውን እንቅስቃሴ ዳግም ለማደራጀት ከሚሰራው ስራ በተጨማሪ ትምህርት ቤቶችን በሌላ መልኩ የአመጽ ማዕከል ለማድረግ የታሰበው።
“በኦሮሚያ ሕዝብ አልነሳም አለ” በሚል የገመገሙት እነ ጃዋር አስቀድሞ በኦሮሚያ ብልጽግና ውስጥ መከፋፈል እንዲፈጠር የተጀመረውን አመራሮችን እየለዩ ማጥቃት እስከ መስከረም ድረስ እንዲቀጥል መክረዋል። የዲሲ ተባባሪ የመረጃ ምንጮቹን ጠቅሶ እንዳለው የኦሮሚያ ብልጽግና ውስጥ መለያየት እስካልተፈጠረ ድረስ ለውጥ ለማምጣት አስቸጋሪ ስለሆነ ሰፊ የፕሮፓጋንዳ ስራ እንዲሰራ ዕቅድ ተይዟል። በዚሁ መሰረት አሁን ከተሰሙት በላይ ለማመን የሚቸግሩ መረጃዎች ውጭ ባሉ በሚታወቁ ሚዲያዎች እንዲሰራጭ ይደረጋል። ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ቀጥሎ አቶ ሽመልስ አብዲሳ ላይ ዘመቻው እንደሚያነጣጥርም ተሰምቷል። ምልክቶችም እየታዩ ነው።
በዚሁ ዕቅድ መሰረት ሕዝብ ሊያምናቸው የሚችሉ የብልጽግና አመራሮች ወይም አብረው ሲሰሩ የነበሩ በገሃድ ወጥተው መረጃ የሚሰጡና አመራሮችን ሊከፋፍል በሚችል መልኩ ቃለ ምልልስ ካደረጉ በቂ ድጎማ ለነሱና ለቤተሰቦቻቸው እንደሚሰጥ ታውቋል። ክፍያውንና ለቤተሰብ የሚሰጠውን ድጎማ ኢትዮጵያ ውስጥ ሆነው በዶላር አጠባ የሚሰሩ እንደሚፈጽሙላቸው አመልክተዋል።
አመጽን ለማነሳሳትና ብልጽግናን ለመከፋፈል የሚሰሩ ፕሮፓጋንዳዎችን በተለያዩ ማህበራዊ ሚዲያዎች ለሚያሰራጩ በሚፈለገው መጠን ገንዘብ ለመክፈል ችግር እያጋጠመ መሆኑን እነ ጃዋር በስጋት የቀረበላቸው መረጃ ሰለመኖሩ በምክክራቸው ወቅት አንስተዋል። የዚህ ችግር ደግሞ የመንግስት የብሔራዊ ባንክ የገንዘብ ፖሊሲና ቁጥጥር አንዱና ዋና መሆኑ ተመልክቷል። ለጊዜው ሻዕቢያ በአዲስ አበባና በውጭ አገራት በተለይም ከአሜሪካ ዶላር እየለቀመ አዲስ አበባ ባሉ ኤጀንቶቹ በሚፈጽመው የክፍያ ኔት ዎርክ ለመጠቅም አቅደዋል።
ከዚህ በዘለለ ግን መንግስት ገንዘብን ዲጂታላይዝድ በሆነ ሲስተም እንዲዛወር የዘረጋቸውን ሲስተም እየከረረና ሕዝቡም አዳዲስ የገንዘብ ማዘዋወሪያ ስልቶቹን መጠቀሙ በተቃውሞ እንቅስቃሴ ላይ ጫና ማሳደሩን አንስተዋል። በዚህም ሳቢያ ችግሩን ለማስወገድ ኃይማኖታዊ ሽፋን መስጠት አስፈላጊ እንደሆነ አቋም ተይዟል። እንደ መረጃ አቀባዮቹ ይህንኑ እንዲሰሩ “የትግሉ መንፈሳዊ ክንፍ” በሚታወቁ ሰባኪያን ኢትዮጵያ የጀመረችውን የዲጂታላዜሽን እንቅስቃሴ ከክፉ መንፈሳዊ አሰራር ጋር በማያያዝ በዘመቻ እንዲያወግዙ ማድረግ አስፈላጊ በመሆኑ አቋም ተይዞበታል። አንዳንድ ወንጌል እናስተምራለን የሚሉ ትምህርቱን መስጠት እንደጀመሩ ለማወቅና ለመመልከት ተችሏል።
በዘመናዊ ዓለም በዲጂታል መታወቂያ፣ በዲጂታል የባንክ ሲስተምና አሰራር የሚንቀሳቀሱ ሆነው ሳለ ኢትዮጵያ ዲጂታል መታወቂያ ማዘጋጀቷን የሚቃወሙት ወገኖች የማንነት ችግር ያለባቸው፣ በተለያየ ማንነት የሚንቀሳቀሱ፣ በተለይም ኢትዮጵያዊ ሳይሆኑ በኢትዮጵያ ፓስፖርት የሚጠቀሙ መሆናቸውን ጠቅሰው ኃላፊዎች ማብራሪያ መስጠታቸው አይዘነጋም።
ኢትዮጵያ የዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ ስታጠናቅቅ ብቻ የአገሪቱ አማካይ የነብስ ወከፍ ገበያ በሁለት ዲጂት እንደሚጨምር መገለጹ የሚታወስ ነው። ከምንም በላይ ደግሞ ወንጀልና ወንጀለኞችን ለመከታተል የሚኖረው ፋይዳ እጅግ የሰፋና በዓለም ላይ በተግባር የታየ በመሆኑ የሚቃወሙት ከወንጀል ጋር ንክኪ ያላቸው ቡድኖች እንደሆኑ መገለጹ አይዘነጋም።
ከአመጹ ጋር በተያያዘ አቶ ልደቱና አቶ ጃዋር ስለሚገኙበት በግል የዋትስ አፕ ስልካቸው አማካይነት ለማነጋገር በተደጋጋሚ ቢደውልላቸውም ለመመለስ ፈቃደኛ አልሆኑም።

