የገቢ ግብርን አስመልቶ የሰራተኞች ማህበር በዋናነት እንደምሳሌ አንስቶ ሙግቱን ሲያቀርብ “14 ሺህ ብር በላይ የሚያገኝ አንድ ሰራተኛ፣ 35 በመቶ ግብር ይከፍላል። በሚበላው የምግብ ሸቀጥና ኧቃዎች ላይ ቫት ወይም የተጨማሪ ዕሴት 15 በመቶ ግብር ታክስ ይከፍላል። ለጡረታ 7 በመቶ ይቆረጥበታል። በድምሩ ከሚከፈለው 14ሺህ ብር ላይ 57 በመቶ ይቆረጣል” ይህን በመያዝ ጉዳዩን ከሃዘኔታ ይልቅ የፖለቲካ ማገዶ ለማድረግ ርብርቡ ከፈተኛ ነበር።
ማህበሩ እንደሚለው ይህ ሰራተኛ ደሞዙ 14 አራት ሹህ ነው ቢባልም የሚደርሰው ከታክስ በሁዋላ የደሞዙ 43 በመቶ ነው። ቫትን አክሎ መሟገቱ ከአመክኖ አንጻር ልክ ባይሆንም የሰራተኞችን የመግዛት አቅም የፈተነውን የኑሮ ትኩሳት ከማሳየት አንጻር ጉዳዩ አነጋጋሪ መሆኑ ሚዛን የደፋ ሆኖ ከርሟል።
ኢትዮጵያ በምርት ብዛት ሊደበቅ የማይቻል እመርታ ብታሳይም፣ ከሚመረተው ብዛት አንጻር የዋጋ ንረቱ አይነኬ ሆኗል። ምሳ ውጭ መብላት የለመደው ሰራተኛ አሁን ላይ ይህን ልማዱን ማስቀተል አለመቻሉን በማንሳት የችግሩን አሳሳቢነት ሲገልጹ ” የሆቴል ቱሩ የሚለመኑ አሉ” በማለት ነው።
በአውሮፓና በአሜሪካ ምግብን ከቤት ቋጥሮ መውጣት፣ እጅግ አነስተኛ መጠን ያለው ምሳ መመገብ የተለመደ መሆኑን የሚያውቁ፣ በምሳ ሰዓት ውጪ መብላት ትክክል ያልሆነ ባህል እንደሆነ፣ በምሳ ሰዓት ጠግቦ መብላት ለጤናም አግባብ ባለመሆኑ ባለሙያዎች ምክር እንዲሰጡ እግረመንገዳቸውን አስተያየት ሲሰጡ ተሰምቷል።
ሰሞኑን ለርዕስ የተመረጠውን የ”ቱሩ ” ጉዳይ በማንሳት ነገሩን መንግስትን ከማስወገድ ጋር አያይዘው ሲያቀርቡ የነበሩ፣ በፍጹም ርህራሄ ጉዳዩን በማህበራዊ አውዳቸው በማንሳት አሳብ ሲያንሸራሽሩ የነበሩትን ጨምሮ ውሳኔው ምን ሊሆን እንደሚችል ሲጠብቁ ነበር።
የኢትዮጵያ ሠራተኞች ማሕበራት ኮንፌደሬሽን ፕሬዝዳንት ካሳሁን ፎሎ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የገቢ ግብር ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ ዙሪያ በተደረገ ውይይት ላይ “ሠራተኛው በቀን አንድ ጊዜ በልቶ መዋል አልቻለም” ሲሉ ባነሱት መከራከሪያ ላይ ” መብላት ካቃተው ሰራተኛ ላይ ግብር አትቁረጡ” ሲሉ ተደምጠው ነበር።
በምንዛሪ አስተዳደር ለውጡ ምክንያት በሁሉም መስክ ዋጋ መጨመሩን ያስታወሱት የረዥም ጊዜ የኢሰማኮ ፕሬዝዳንት አቶ ካሳሁን ፎሎ፣ የኑሮ ውድነቱን በወጎ በማሳየት የግብር አስከፋፈሉ ላይ የራሳቸውን መነሻ አኑረውም ነበር።
የማሻሻያ አዋጁ ሪፖርትና የውሳኔ ሀሳብ ያቀረቡት በምክር ቤቱ የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጄ ናቸው።
የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ለረጅም ጊዜ አገልግሎት ሲሰጥ የነበረው የገቢ ግብር አዋጅ ዲጂታል ኢኮኖሚውን ታሳቢ ያላደረገ መሆኑን ገልጸው፤ በአዋጁ ላይ የተደረገው ማሻሻያ ከዲጂታል ኢኮኖሚው ጋር የተጣጣመ ዘመናዊ የታክስ ሥርዓት መፍጠር ያስችላል ሲሉ ተደምጠዋል።
የታክስ መሰረትን በማስፋት የመንግስትን ገቢ የመሰብሰብ አቅም በማሳደግ የታቀደው የኢኮኖሚ ዕድገት እንዲመዘገብ እንደሚያስችልም ገልጸዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምር ቤት የፕላን፣ በጀት እና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ደሳለኝ ወዳጄ የገቢ ግብር አዋጅ ማሻሻያው ከግብር ነጻ የሆነው ከመቀጠር የሚገኘ ገቢ ከፍ እንዲል የተደረገ በመሆኑ ሲያስታውቁ
- ዝቅተኛ ገቢ ባላቸው ተቀጣሪዎች ላይ የግብር ጫናው እንደሚቀንስ፤
- የግብር መሰረቱ እንዲሰፋ፤
- መንግስት ከገቢ ግብር የሚያገኘው ገቢ በአንጻራዊ ሁኔታ ከፍ እንዲል አጋዥ መሆኑን አመልክተዋል።
በማሻሻያው ላይ ከበርካታ ባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት እንደተደረገበት እና እንደ ቋሚ ኮሚቴም ሰፊ ጊዜ ተወስዶበት የተዘጋጀ ማሻሻያ ነው ብለዋል።
የገንዘብ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ክቡር እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ” ማሻሻያው ለረጅም ጊዜ ውይይት የተደረሀበት እና የሀገራት ልምድ የተወሰደበት ነው። ማሻሻያው ዘመኑን የዋጀ ነው ” ሲሉ ተናገረዋል።
አዋጁን የተቃወሙ የምክር ቤት አባላት የገቢ ግብር ማሻሻያው የመንግስት ሠራተኛውን የኑሮ ሁኔታ ታሳቢ ያላደረገ ማሻሻያ በመሆኑ ምክር ቤቱ ማሻሻያውን በድጋሚ እንዲፈትሸው ጠይቀዋል፡፡
የገቢ ግብር አዋጁ ከዚህ ቀደም ሰፊ የክርክር ነጥቦች የተነሳባቸው ጉዳዮች ላይ ማስተካከያ ሳይደረግበት ነው በ5 ተቃውሞ ፣ በ12 ድምጸ ተዓቅዶ በአብላጫ ድምጽ የፀደቀው።

