በኦሮሚያ ሰላም እንዲሰፍን፣ የክልሉ ህዝብ ወደ ሰላማዊና የተረጋጋ ህይወት እንዲመለስ የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሽመልስ አብዲሳ ተደጋጋሚ ጥሪ አቀረቡ። አቶ ሽመልስ አብዲሳ በይፋዊ ማህበራዊ ገጻቸው ባካፈሉት ሰፊ ጽሁፍ ህገወጥነት የሚያስተዳድሩትን ክልል ተግዳሮት እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡
በኢትዮጵያ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ኮሚሽን በይፋ የአጀንዳ ማሰባሰቡን ስራ በአዲስ አበባ እንደሚያስጀምር መገለጹን ተከትሎ ሽመልስ አብዲሳ “ሰላም፣ ሰላም፣ አሁንም ሰላም” ብለዋል። ርዕሰ መስተዳድር ሽመልስ አብዲሳ የኦሮሚያ ህዝብ ገዳ የመሰለ ባህላዊ የሰላም ስርዓት እያለውና በተረጋጋ ሁኔታ የመኖር እድል ቢኖረውም በ “ህገወጥነት” መፈተኑን ገልጸዋል።
“ዛሬ ትናንት አይደለም” ያሉት ሽመልስ አብዲሳ የኦሮሞ ህዝብ መብቱን አረጋግጧል፣ እድሉን በራሱ የመወሰን መብት ተጎናጽፏል ካሉ በሁዋላ ዛሬ ጫካ ጠመንጃ ትግል በማለፉ አይጠቅምም በዋል። የሰላማዊ ትግሉ ምህዳር ተከፍቷል ሲሉም የጫካ ትግል ሊያከትምና የሰላም መንገድን መከተል እንደሚገባ ጽፈዋል።
ርዕሰ መስተዳድር ሽመልስ በመግለጫቸው “ህዝቡ አግኝቷል” ያሉት የነጻነት መንገድ “ባሁን ወቅት ታጥቆ ጫካ ውስጥ በሚንቀሳቀስ” ባሉት አካል መስተጓጎሉን ገልጸዋል፡፡ በተለይም ባለፉት አራት ዓመታት በክልሉ የተካሄደው ግጭት አለመረጋጋትን አስከትሎ “ብዙ ክስሮናል” ነው ያሉት፡፡
“ነገሮች ሁሉ በሰላማዊ መንገድ ተጠናቀው ሰላምና መረጋጋት መስፈን እንዳለበት እናምናለን” ሲሉ የመንግስታቸውን አቋም የገለጹት አቶ ሽመልስ አስከፊ ያሉት ጭቆና በኦሮሞ ህዝብ ላይ መፈጸሙ ቆሞ ህዝቡ በሰላም ወጥቶ በመግባት እራሱን የማልማት መብቱ እንዲከበርለት ያስፈልጋል በማለት ሀሳባቸውን ዘርዝረዋልም፡፡
የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት በህግ ከተሰጠው የህግ የበላይነትን የማስከበር ኃላፊነቱ ጎን ለጎን በነባር የማህበረሰቡ እሴት መሰረት ችግሮችን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ተጀምሯል ያሉት የሰላም ጥሪዎችን አሁንም እንደቀጠለ ነው ብለዋልም፡፡ በዚህም የሰላም ንግግር ሂደቱ እንዳተቋረጠ ፍንጭ ሰጥተዋል።
መሰል የሰላም ጥሪዎች መንግስትን በኃይል ለሚወጉት ስቀርብ የመጀመሪያው አይደለም፡፡ ተደጋጋሚ ጥሪዎች ብቻም ሳይሆን የተጀመሩ ፊት ለፊት ተገናኝቶ የመወያየት እድሎችም ሳይሰምሩ ሲከሽፉ ታይተዋል፡፡ የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድሩ ተከታይ ጥሪ ባሁን ወቅት የተሰማም በክልሉ በተለያዩ አከባቢዎች ግጭቶች አለማቧራታቸው ብቻ ሳይሆን የተዋጊዎች ምልመላዎችም ጎልተው በቀጠሉበት ወቅት ነው፡፡
የኢትዮጵያ ፖለቲካ ፓርቲዎች ምክር ቤት ሰብሳቢ ፖለቲከኛ ደስታ ድንቃ በዚሁ ሀሳብ ላይ ለዶቼ ቬለ በሰጡት አስተያየትም “በቃል የሚነገሩ መሰል አስተያየቶች በተግባር ልደገፉ ይገባል” ብለዋል፡፡ ለዚህ ደግሞ የፖለቲካ ቁርጠኝነት ይሻል ነው ያሉት፡፡
ባለፉት ወራት የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት በተደጋጋሚ የሰላም ጥሪ ማሰማቱን አስታውሰው ዛሬ በይፋዊ ማህበራዊ ገጻቸው ላይ አስተያየት የሰጡት የኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስ (ኦፌኮ) የውጭ ጉዳይ ሃላፊና የፖሊቲካ ተንታኝ ጀዋር ሙሃመድ ለጦርነት ከመቀስቀስ ሰላምን ማወጅ ጥሩ እምርታ ቢሆንም ጥሪው በተግባር ሊታጀብ ይገባል ብለዋል፡፡ ፖለቲከኛ ጃዋር “በፍርድ ቤት በነጻ የተሰናበቱ” ያሏቸውን የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ፖለቲከኞችን መፍታት እና በቅርቡ የተገደሉትን የኦነግ የፖለቲካ ኦፊሰር የአቶ በቴ ዑርጌሳን ፍትህ ማረጋገጥ ለቁርጠኝነቱ አንዱ ማሳያ ሊሆን ይገባል ሲሉም ሃሳባቸውን ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ ፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢው አቶ ደስታ ዲንቃም ከመንግስት ባሻገር ስለ የፖለቲካ ተቋማት አስተዋጽኦ ተጠይቀው፤ “በሰላማዊ መንገድ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ድርጅቶች በሙሉ የሰላም ጥሪና ተማጽእኖ ከማቅረብ ቦዝነው አያውቁም” ብለዋል፡፡የኦሮሚያ የተራዘመ ግጭት በተለይም ባለፉት አራት ዓመታት ተስፋፍቶ ከፍተኛ ሰብዓዊና ቁሳዊ ጉዳቶች ማድረሱ ተደጋግሞ ተዘግቧል፡፡
ትርጉም ጀርመን ድምጽ


