የቻይናው አሊባባ ግሩፕ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ እና ከኢትዮጵያ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ማህበር ጋር በመተባበር በኢትዮጵያ ስራ ለመጀመር የሚያስችለውን እንቅስቃሴ መጀመሩን ይፉ የሚያደርግበት መድረክ ተካሂዷል።
በዝግጅቱ ላይ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ይሽሩን አለማየሁ የአሊባባን አሊ ኤክስፕረስ በኢትዮጵያ ስራ መጀመሩ ዓለም አቀፋዊ የኤሌክትሮኒክስ ንግድ ሥራ ወደ ኢትዮጵያ ገበያ መግባቱን ብቻ ሳይሆን ለዲጂታል ፈጠራና ለኢኮኖሚ ዕድገት ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር የተሰሩ ስራዎች ማሳያ ነው ብለዋል።
ይህ ጅማሮ ለኢትዮጵያውያን ሸማቾችና ነጋዴዎች በአዲሱ የዓለም ገበያ ምርትና አገልግሎትን ለመገበያየት ያስችላል።
አሊባባ የሚያቀርባቸውን ዲጂታል መሳሪያዎችና መድረኮችን በመጠቀም ኢትዮጵያ በአለም አቀፉ ዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ ጉልህ ተዋናይ ለመሆን ያላትን አቅምና ዝግጁነት ማሳየት እንደሚገባም ተገልጿል።
በኢትዮጵያ አየር መንገድ የኢኮሜርስ ሎጂስቲክስ አገልግሎት ስራ አስኪያጅ አቶ ቴዎድሮስ አያሌው የኢትዮጵያ አየር መንገድ አሊባባ ግሩፕ በኢትዮጵያ የሚጀምረውን የኢኮሜርስ ስራ ለማሳለጥ የሚያስችል የኢኮሜርስ ሎጂስቲክስ አገልግሎትን የሚሰጥ ሀብ ዝግጁ ማድረጉን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ይህንን የኢኮሜርስ ሎጂስቲክስ አገልግሎትን የሚሰጥ ሀብ ማዘጋጀቱ አሊባባ ግሩፕ በኢትዮጵያ ስራ ለመጀመር እንዲችል ትልቁን አስተዋጽኦ እንዳበረከተ ተነስቷል።
የድርጅቱን ፕላትፎርም ያስተዋወቁት በአፍሪካ ገበያ የአሊ ኤክስፕረስ ቢዝነስ ዳይሬክተር ጄፍሪ ጂያንግ አሊ ኤክስፕረስ በኢኮሜርስ ያለውን አለም አቀፍ ልምድ በመጠቀም የኢትዮጵያውያን ሸማቾችንና የንግድ ቦታዎችን በአንድ ቁልፍ ስትራቴጂያዊ እንቅስቃሴ በማስተሳሰር እንደሚሰራ ተናግረዋል።
በዝግጅቱ ላይ የኢትዮጵያ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ማህበር ፕሬዝዳንት ፍቅር አንዳርጋቸው ማህበሩ የኢትዮጵያን የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን እንቅስቃሴ ውጤታማነት ለማገዝ ከሚመለከታቸው እካላት ጋር በመተባበር እየሰራ መሆኑን ገልጸው እንደ አሊባባ ያሉ የኢኮሜርስ ድርጅቶች በኢትዮጵያ ገበያ መቀላቀላቸው የዘርፉን ውጤታማነት ለማሳደግ ጉልህ ሚና እንደሚኖረው መናገራቸውን የሚኒስቴር መስሪያቤቱ መረጃ ያመለክታል።
ማህበሩ በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር እማካኝነት ቻይና በሚገኘው የአሊባባ ግሩፕ በመገኘት ልምድ በመቅስም ይህ የግንኙነት መስመር እንዲጀመር የድርሻውን መወጣቱ ተገልጿል።
ነሐሴ 16 ቀን 2016 ዓም EPD

