በተለያዩ ክፍለ ከተሞች በመንቀሳቀስ የውንብድና እና የቅሚያ ወንጀል ሲፈፅሙ የቆዩ 17 ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር ዋሉ፤ የተለያዩ ንብረቶችም ከተጠርጣሪዎቹ እጅ ላይ በኤግዚቢትነት ተይዘዋል።
የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ መስለው በተሽከርካሪ እየተንቀሳቀሱ የሃይል ተግባር በመጠቀም በተለያዩ ግለሰቦች ላይ የቅሚያ እና የውንብድና ወንጀል ፈፅመዋል የተባሉ 17 ግለሰቦች በቁጥጥር ስር ውለው ምርመራ እየተጣራባቸው እንደሚገኝ የገለፀው በየካ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ የአድዋ ድልድይ አካባቢ ፖሊስ ጣቢያ ነው፡፡
ተጠርጣሪዎቹ የሰሌዳ ቁጥር ኮድ 3-30785 ኦሮ በሆነ ሚኒባስ ተሽከርካሪ እየተንቀሳቀሱ ምሽት ላይ አንድን ግለሰብ ከቦሌ ጌታሁን በሻህ ህንፃ አካባቢ ጭነው ከወሰዱ በኋላ አመቺ ቦታ ሲደርሱ የግለሰቡን እግር በጫማ ገመድ አስረው እና በስለት አስፈራርተው ሞባይል ስልክ እና ጥሬ ገንዘብን ጨምሮ በአጠቃላይ 21ሺህ 500 ብር የዋጋ ግምት ያላቸውን ንብረቶች ወስደው ተሰውረዋል፡፡
አቤቱታው የደረሰው ፖሊስ ጣቢያው የተለያዩ መረጃዎችን በማሰባሰብ ባደረገው ክትትል ወንጀሉ የተፈፀመበትን ተሽከርካሪ በቁጥጥር ስር አውሏል፡፡ የወላጆቹ በሆነው ተሽከርካሪ በቀኑ ክፍለ ጊዜ የትራንስፖርት አገልግሎት ሲሰጥ ውሎ ምሽት ላይ እስከ 10 ሺህ ብር የሚደርስ ገንዘብ እየተቀበለ መኪናውን አሳልፎ ለወንጀል ፈፃሚዎቹ ሲሰጥ የነበረ ግለሰብን ጨምሮ በወንጀሉ ተሳትፎ አላቸው የተባሉ 17 ተጠርጣሪዎች ፖሊስ ባደረገው ክትትል ተይዘዋል፡፡
ተጠርጣሪዎቹ ከምሽቱ አንድ ሰዓት እስከ አራት ሰዓት ባለው ጊዜ ውስጥ በተለያዩ ክፍለ ከተሞች እና አካባቢዎች እየተንቀሳቀሱ ወንጀሉን ሲፈፅሙ የቆዩ እና በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ እና በሌሎች ፖሊስ ጣቢያዎች ተጨማሪ የምርመራ መዝገብ የተደራጀባቸው ስለመሆናቸው ከፖሊስ ጣቢያው የተገኘው መረጃ አመልክቷል ፡፡
34 የተለያዩ አይነት ሞዴል ያላቸው ሞባይል ስልኮች፣ ላፕቶፕ ኮምፒውተር እና ሌሎች ልዩ ልዩ ንብረቶች በተጠርጣሪዎቹ እጅ ላይ ተገኝተው የምርመራው ስራ መቀጠሉ ተገልጿል፡፡ ግለሰቦቹ በተለያዩ አካባቢዎች እየተንቀሳቀሱ ወንጀሉን ሲፈፅሙ መቆየታቸውን የገለፀው ፖሊስ በግለሰቦቹ ተመሳሳይ ወንጀል የተፈፀበትና ፈፃሚዎቹን ለይቶ የሚያውቅ የካ ክ/ከተማ ፖሊስ መምሪያ በአካል በመምጣት መረጃ መስጠት እንደሚችል አስታውቋል ።
የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ ተሽከርካሪዎች ባለ ንብረቶች የመኪናቸውን ውሎ እና ተግባር ትኩረት ሰጥተው ከመከታተል ባሻገር በአሽከርካሪዎቹ ላይ ተገቢውን ቁጥጥር በማድረግ መሰል ወንጀሎችን ለመከላከል የበኩላቸውን ሃላፊነት ሊወጡ እንደሚገባ የአዲስ አበባ ፖሊስ አሳስቧል፡፡

