“ከዚህ ምርጫ በኋላ ለአገሬ የምመኘው ሰላም፣ አንድነት እና ብልፅግና ነው፡፡ እኔም በ91 ዓመቴ በምርጫው የተሳተፍኩኝ ሲሆን ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ የማስተላልፈው መልእክት የአገሪቱን ሰላምና አንድነት እንድትጠብቁ አደራ እላለሁ፡፡ አገር ከፖለቲካ ፓርቲዎች በላይ ናት፡፡”
አቶ ቡልቻ ደመቅሳ ሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም በተካሄደው ሀገራዊ ምርጫ ለኢትዮጵያ ህዝብ ያስተላለፉት መልእክት
አቶ ቡላቻ ደመቅሳ ህዝብ በግብራቸው የሰጣቸውን አክብሮት ሳያበላሹ ጠብቀው ያለፉ ጉምቱ ፖለቲከኛ ነበሩ። በፖለቲካ ህይወታቸው የሚያውቋቸው ብቻ ሳይሆን አገር በይፋ እንደሚያውቀው በብሄር ተሸፍነው “ፍለጠው፣ አስወጣው፣ አባረው …” ሲሉ ተሰምተው አያውቁም።
ካጃዋር መሐመድ ጋር መዋል ከጀመሩ በሁዋላ ” አማራ አታግቡ፣ ከአማራ ጋር አትገበያዩ …” ሲሉ እነነበሩት አንደበታቸውን አንድም ቀን ሳያረክሱ እንዳማረባቸው ያለፉት አቶ ቡልቻ፣ እድሜ ጠግበው ቢያልፉም ህዝብ ሃዘኑን የገለጸላቸው ሌሎችን ዘር ሳይለዩ የሚያከብሩ ጨዋ ሰው በመሆናቸው ነው።
አቶ ቡልቻ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ በመሆናቸው ከኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች ጋር በኢትዮጵያ ላይ ሲያሴሩ፣ ሲመክሩባት፣ እንድትተራመስ ሲቀሰቅሱ ታይተውም ተሰምተውም አያውቁም። አንዳንዶች በሽምግልና ሳይቀር እዛና እዚህ እየረገጡ አገር ሲያተራምሱ እንደሚታዩት አይነት ክብረ ነክ ታሪክ የላቸውም።
የራሳቸውንም ይሁን የድርጅታቸውን ዓላማ ግልጽ በሆነ መድረክ የሚያራምዱ፣ በብሄር ጃኖ ተሸፍነው ህዝብ እንደሚያተራምሱት ዓይነት ምግባር የሌላቸው ጨዋ ሰው እንደነበሩ በቅርብ የሚያውቋቸው በህይወት እያሉ ደጋግመው የመሰከሩላቸው ጥሩ የኢኮኖሚክስ ባለሙያ ነበሩ።

በብሄር ፖለቲካ እንደተጠለሉት አብዛኛ የደም ነጋዴዎች በአንድም ቦታ ስማቸው የማይነሳው አቶ ቡልቻ በስራ ገበታቸው፣ በተሰጣቸው ኃላፊነቶች፣ በፖለቲካ ድርጅት መሪነታቸው ስማቸው በክፉ ተነስቶ አያውቅም። ሌላው ቀርቶ ውድ የኦሮሞ ፖለቲከኞችን ሲያሳድኑ የነበሩት፣ እነ ነዲ ገመዳን የስለቀጡት አቶ መለስ እንኳን ከግርማቸው የተነሳ ያከብሯቸው ነበር።
ለዚህ ይመስላል ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አቶ ቡልቻ ደመቅሳ በማረፋቸው የተሰማቸውን ሀዘን ሲገልጹ “ሊተኩ የማይችሉ” ያሉዋቸው።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ “በሚችሉት ሁሉ ሀገራቸውንና አፍሪካን ያገለገሉ፣ በአቋማቸው ጽኑ፣ ሕዝቦችን ለማቀራረብ የተጉ፣ እውነት ነው ብለው ያመኑትን የትምና መቼም የሚናገሩ ነበሩ” ሲሉ በተባ ብዕራቸው ምስክርነት የሰጡዋቸው።
“እንዲህ ዓይነት ብርቱ ሽማግሌዎችን ማጣት ጉዳቱ ለሀገር ነው” በማለት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ፈጣሪ ነፍሳቸውን እንዲቀበል ተመኝተዋል። አቶ ቡልቻ የተወለዱት በ1922 ዓ.ም. ሲሆን የኦሮሞ ፌደራሊስት ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ መስራች እንደሆኑ ይታወሳል።

ኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን ቦጂ ድረመጂ ወረዳ የተወለዱት አቶ ቡልቻ የቤተሰባቸው አራተኛ እና ብቸኛ ወንድ ናቸው። የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን በጊምቢ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ደግሞ በኩየራ አድቬንቲስት ተከታትለዋል።የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ከያኔው ቀዳማዊ ኃይለስላሴ ዩኒቨርሲቲ በኢኮኖሚክስ አግኝተዋል።
ቢቢሲ ታሪካቸውን ሰብስቦ እንደሳፈው አቶ ቡልቻ ደመቅሳ የመንግስት ስራን የጀመሩት በአጼ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግስት የገንዘብ ሚኒስቴር ምክትል ሚኒስትር በመሆን ነበር።
አሜሪካ ሀገር በሚገኝ ሴርኪኡዝ ዩኒቨርሲቲ ትምህርታቸውን የተማሩት አቶ ቡልቻ ለአስር ዓመታት ያህል ምክትል ሚኒስትር ሆነው ካገለገሉ በኋላ በ1966 አብዮቱ ሲፈነዳ ተመልሰው ወደ ውጭ አገር ሂደዋል።
በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ውስጥ የሰሩት አቶ ቡልቻ ኢህአዴግ ሥልጣን ከያዘ በኋላ የፓርላማ አባል ነበሩ። በአንድ ወቅት ከቢቢሲ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ “የኢትዮጵያን ፓርላማን ለማየት እንጅ የእዉነት ነው ብየ አይደለም የገባሁት” ብለዋል።
አቶ ቡልቻ ከፖለቲካ ተሳትፏቸው በተጨማሪ ከቀዳሚ የግል ባንኮች አንዱ የሆነውን አዋሽ ባንክ አቋቁመዋል። አቶ ቡልቻ የባንኩ ዓላማ ለኦሮሞ አርሶ አደሮች ብድር ማመቻቻት እንደሆነ ተናግረው ነበር።
ትውስታ … አቶ ቡልቻ በርካታ ትውሳታዎች ቢኖሯቸውም በብዛት በማህበራዊ ሚዲያዎች የተሰራጨው፣ ቲክቫህን የመሳሰሉ የቴሌግራም ወሬ አቀባዮች የሚከተለውን ሰንደውላቸዋል።
አቶ ቡልቻ ደመቅሳ በምን ይታወሳሉ ?
በኢህአዴግ ጊዜ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ሀገራቸውን በሚመሩበት ወቅት ፓርላማ የነበሩት ጉምቱው ፖለቲከኛ እና የኢኮኖሚ ምሁር አቶ ቡልቻ ደመቅሳ ጠንከር ያሉ ምሁራዊ ጥያቄዎችን ለጠቅላይ ሚኒስትሩ በማንሳት ይታወቃሉ።
ንግግራቸው ለዛ የነበረው ፣ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስን ጨምሮ መላ የፓርላማ አባላትን ሳቅ በሳቅ የሚያድረግ ፤ ድፍረትና እውቀት የተሞላበት ነበር።
በተለይ ደግሞ በኢኮኖሚ ጉዳዮች ላይ የዳበረ እውቀት ስለነበራቸው ሁሉም ሰው እሳቸው እድሉን አግኝተው እስኪናገሩ በጉጉት ነበር የሚጠብቀው።
በብዙዎች የሚታወሰው እና ሁሌም ተደጋግሞ የሚነሳው ከኢትዮጵያ ኢኮኖሚ እድገት ጋር በተያያዘ ያነሱት ጥያቄና ፓርላማውን ሳቅ በሳቅ ያደረጉበት ንግግራቸው ነው።
” ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፣ መንግስቱም ደጋግሞ ደጋግሞ ‘ ኢትዮጵያ በ110 ፣ በ111 አድጋለች ‘ ይላል ፤ እኔ ፣ እሳቸውም የኢትዮጵያ ኢኮኖሚስቶችም ያውቃሉ በ111 ማደግ ማለት ተአምር ነው። ይሄን ተአምር የሰራችው ቻይና እንደውም አሁን እየሰራች አይደለም ፣ ታይዋን ፣ ደቡብ ኮሪያ ናቸው።
ኢትዮጵያ እንዴት አድርጋ ነው በ111 ያደገቸው ? አንጎላ አሁን በ112 እያደገ ነው ለምንድነው በአንድ ጊዜ ብዙ ዘይት አገኙ፣ ዘይት ያገኙ ሰዎች ወይም ሌላ ነገር ያገኙ በ110 ወይም በ111 ቢያድጉ አይገርምም። 111 አደግን ብለን ለዓለምስ እንዴት አድርገን ነው የምንገልጸው ?
የዓለም የገንዘብ ድርጅት ኢትዮጵያ እና ሌሎች የምስራቅ አፍሪካ ሀገሮች ቢበዛ በ106 ያድጋሉ ብሏል እኛ ግን እንቢ ብለን ‘ አስራ አንድ ነው ! ‘ እንላለን ይሄ ተገቢ ነው ? “
ሌላ በእጅጉ ከሚታወሱበት ንግግራቸው መካከል ደግሞ መንግሥት ስለሚሳተፍባቸው የተለያዩ ሽያጮች ጉዳይ ነው።
” መንግሥት ለምንድነው ማዳበሪያን የሚሸጠው ብቻውን ? ፤ መንግሥት ለምንድነው ሆቴል ውስጥ ገብቶ የሚነግደው ? ፤ መንግሥት ለምንድነው ቱሪዝም ውስጥ ገብቶ የሚነግደው ? ፤ መንግሥት ለምንድነው ሲሚንቶ የሚሸጠው ? ፤ አልፎ ፍራፍሬ ሽንኩርት የሚሸጠው ለምንድነው ? መንግሥት ሶሻሊት ኢኮኖሚ አይደለም የሚያራምደው ? “
አቶ ቡልቻ ደመቅሳ በምዕራብ ወለጋ የተወለዱ ሲሆን በትላልቅ ዩኒቨርሲቲዎች የተማሩ የተዋጣላቸው የኢኮኖሚ ምሁር ነበሩ። የአዋሽ ባንክ እንዲሁም የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስን (ኦፌኮ) መስራችም ነበሩ።

