በአዋሽ ፈንታሌ ከጥር 22 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ የወጣው የሚቲን ጋዝ መጠን እየጨመረ መሆኑንና ይህም እሳተ ገሞራ ሊያስከትል እንደሚችል ጤናዓለም አየነው (ፕ/ር) ገለጹ።
በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የስነምድር መምህር ጤናዓለም አየነው (ፕ/ር) ለጋዜጣ ፕላስ እንደገለጹት፤ ላለፉት ሁለት ወራት በኢትዮጵያ የስምጥ ሸለቆ ዙሪያ ተደጋጋሚ የመሬት መንቀጥቀጥ መከሰቱ የሚታወስ ነው።
የመሬት መንቀጥቀጥ እና የእሳተ ገሞራ ፍንዳታ የተያያዙ ናቸው ያሉት ፕሮፌሰር ጤናዓለም፤ በኢትዮጵያ አዋሽ ፈንታሌ አካባቢ እስካሁን ባለው መረጃ መሰረት ፍንዳታ ከመከሰቱ በፊት የሚፈጠሩ ሁኔታዎች እየተከሰቱ ነው ብለዋል።
በአብዛኛው ሙቅ ውሃ ከመሬት አየገነፈለ የሚወጣ ሲሆን፤ አልፎ አልፎ ደግሞ አሁን በአዋሽ ፈንታሌ እንደተከሰተው የሚተኑ ጋዞች እንደሚወጡ አስታውቀዋል።
በአዋሽ ፈንታሌ ከጥር 22 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ የሚቲን ጋዝ እየወጣ መሆኑን ገልጸው፤ የሚወጣው የጋዝ መጠን ከጊዜ ወደ ጌዜ እየጨመረ መሆኑን አመላክተዋል።
የሚቲን ጋዝ የሚከሰተው ከመሬት ውስጥ የቀለጠው አለት ከውሃ ጋር ሲገናኝ፣ ጥልቅ ከሆነ ቦታ የኬሚካል እንቅስቃሴ/ሪአክሽን/ ሲኖር እና በሌሎች መንገዶች መሆኑን አስረድተዋል።
የሚቲን ጋዝ ከእሳተ ገሞራ ፍንዳታ ጋር ተያይዞ ከሚወጡ የጋዝ አይነቶች አንዱ መሆኑን አስታውቀዋል።
የሚቲን ጋዙ እየጨመረ መምጣት የእሳተ ገሞራ ፍንዳታ ሊያስክትል እንደሚችል አመላክተው፤ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት በአካባቢው አስፈላጊውን ጥንቃቄ ሊያደርጉ ይገባል ነው ያሉት።
ኢትዮጵያ ካላት የኢነርጂ ሀብት አንዱ ከመሬት ውስጥ የሚወጣ የሙቀት ሀይል ቢሆንም የሚቲን ጋዝ መውጣት ጥሩ አጋጣሚ አለመሆኑን ተናግረዋል።
ሚቲን ጋዙ የአየርን የሙቀት መጠን የሚጨምር በመሆኑ በኢትዮጵያ የተከሰተው መጠኑ ከፍ እያለ ከሄደ በአካባቢ፣ በእጽዋትና እንስሳት ላይ ጉዳት ያስከትላል ብለዋል።
አካባቢን የሚበክሉ ጋዞች ሲከሰቱ በጥልቀት በመመራመር እና ሂደቱን በመከታተል የቅድመ ማስጠንቀቂያ ጥንቃቄ መስጠት እንደሚገባ ጠቁመዋል።
ሚቲን ጋዙ በሂደት ወደእሳተ ገሞራ የሚቀየር ከሆነ በአካባቢው የሚኖሩ ሰዎችን ከአካባቢው የማራቅ ስራን መስራት ይገባል ብለዋል።
የሚቲን ጋዙ በወጣበት አካባቢ የምርምር ማዕከል በማቋቋም የዘርፉ ባለሙያዎች ምርምር በማድረግ የሚያገኙትን ውጤት ለሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ሊያሳውቁ እንደሚገባም ጠቁመዋል።
በሄለን ወንድምነው ጋዜጣ_ፕላስ

