በሀገሪቱ ባለው የእርስ በእርስ ጦርነት ምክንያት ሱዳን ከኢትዮጵያ የገዛቸውን የኤሌትሪክ ኃይል እዳ አለመክፈሏን ተከትሎ፤ የእዳ መክፈያ ተጨማሪ የ1 ዓመት ከ6 ወር ጊዜ እንዲሰጣት ጥያቄ ማቅረቧ ተገልጿል፡፡
በሱዳን አሁን ላይ አንፃራዊ ሰላም በመኖሩ ያለባትን እዳ ለመክፈል የልኡኳን ቡድኗን ወደ ኢትዮጵያ መላኳን፤ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ሞገስ መኮንን ለአሐዱ ተናግረዋል፡፡
በዚህም ሱዳን እዳዋን ለመክፈል የአንድ ዓመት ከስድስት ወር ጊዜ እንዲሰጣት የጠቀች ሲሆን፤ በኢትዮጵያ በኩል ግን እስከ 9 ወር ባለው ጊዜ እንዲጠናቀቅ በሚል ምላሽ መሰጠቱን እና ንግግር መደረጉን ገልጸዋል፡፡
ከዚህ በፊት የነበረባት የእዳ መጠን 80 ሚሊየን ዶላር ሲሆን፤ አሁን ላይ ቁጥሩ መጨመሩንም አቶ ሞገስ አንስተዋል፡፡
ሱዳን፣ ከኢትዮጵያ ለምትገዛው ኤሌክትሪክ ኃይል በምትኩ ፔትሮሊየም ለማቅረብ ከስምምነት ላይ እንደደረሰች የሀገሪቱ የኢነርጂ ሚንስቴር ባወጣው መግለጫ ማስታወቁ ይታወሳል፡፡
ይሄንን በተመለከተ አሐዱ ላነሳላቸው ጥያቄም የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተሩ፤ እንዲህ አይነት ስምምነት ስለመደረጉ ተቋሙ መረጃ እንደሌለው አስታውቀዋል፡፡
በሱዳን እየተካሄደ ባለው የእርስ በርስ ጦርነት ምክንያት ኢትዮጵያ ወደ ሱዳን የምትልከው የኤሌክትሪክ ኃይል በ80 በመቶ ስለመቀነሱ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ማስታወቁ ይታወሳል፡፡
ከሁለት ዓመታት በፊት ከሱዳን ጋር የተደረገው ስምምነት መሠረትም እስከ 100 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል ከኢትዮጵያ ለመግዛት ሥምምነት ላይ ተደርሶ የነበረ ቢሆንም፤ ነገር ግን በሀገሪቱ በሚካሄደው ጦርነት ምክንያት የኃይል መሠረተ ልማቶች ላይ ከፍተኛ ጉዳት በመድረሱ አሁን ላይ መጠኑ በእጅጉን መቀነሱ ተገልጿል፡፡
በዚህም ምክንያ ኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ ከ10 እስከ 20 ሜጋ ዋት ብቻ ወደ ሱዳን እየላከች እንደምትገኝ ተመላክቷል፡፡
ኢትዮጵያ ከሱዳን በተጨማሪ ወደ ጅቡቲ እና ኬንያ የኤሌክትሪክ ኃይል የምትልክ ሲሆን፤ በመጪዎቹ ወራቶችም በኬንያ በኩል ወደ ታንዛኒያ የኤሌክትሪክ ኃይል መላክ ለመጀመር ዝግጅት እየተደረገ መሆኑ ተገልጿል።
በተጨማሪም ኢትዮጵያ ከደቡብ ሱዳን እና ሶማሌላንድ ጋር የኤሌክትሪክ ኃይል መላክ እየተወያየች ሲሆን፤ ሁለቱም የኤሌክትሪክ ሃይል ለመግዛት ፍላጎት አሳይተዋል ተብሏል።
(አሐዱ ሬዲዮ)

