” የሂሳብ መዝገብ እንዲይዙ በህግ የሚገደዱ ግብር ከፋዮች ከመጪው ሀምሌ የግብር ማሳወቂያ ወር ጀምሮ የተሟላ የሂሳብ መዝገብ በመያዝ ካልመጡ በስተቀር አይስተናገዱም “- የገቢዎች ቢሮ
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ቢሮ ከመጪው ዓመታዊ የግብር ማሳወቂያ ወር ጀምሮ የደረጃ “ሀ” እና “ለ” ግብር ከፋይ ሆነው በህግ የሚገደዱ ግብር ከፋዮች ያለ ሂሳብ መዝገብ የማይስተናገዱ መሆኑን አሳውቋል።
አይስተናገዱም የተባሉት በደረጃ “ሀ” እና “ለ” የግብር ከፋይነት የተመዝገቡ እና በህጉ መሰረት የሂሳብ መዝገብ እንዲይዙ የሚገደዱትን ብቻ ነው።
የቢሮው የኮምዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ሰውነት አየለ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ እንደተናገሩት በህጉ መሰረት የሂሳብ መዝገብ እንዲይዙ የሚገደዱ ነጋዴዎች ከሚቀጥለው በጀት አመት በኋላ ግብር ለመክፈል ያላቸውን አጠቃላይ ወጪ እና ገቢያቸውን በዝርዝር የሚያሳይ መዝገብ መያዝ ይጠበቅባቸዋል ብለዋል።
አቶ ሰውነት አየለ በዝርዝር ምን አሉ ?
” የሂሳብ መዝገብ ማለት ያላቸውን አጠቃላይ ሽያጭ እና ወጪ በዝርዝር የሚያሳይ ሰነድ/መዝገብ ነው።
ህጋዊ የሆነ ግብይት የሚፈጸም ከሆነ እና በደረሰኝ ላይ የተመሰረተ ግብይት ካለ ከዚህ መዝገብ ጋር ተያይዞ ነው የሚቀርበው።
ይህ ህግ ከወጣ ረጅም ጊዜ ነው ነገር ግን አፈጻጸም ላይ የተለያዩ ክፍተቶች በመኖራቸው በቁርጥ ግብር የሚስተናገዱ ነበሩ።
ለእነዚህ ግብር ከፋዮች በተለያየ መንገድ መረጃዎችን እያደረስን ነው ያለነው ከሚቀጥለው በጀት አመት በኋላ ከዚህ ሂሳብ መዝገብ ውጪ እንደማናስተናግዳቸው እንዲያውቁ እያደረግን ነው።
ግብይቶቻቸውን በደረሰኝ ላይ ተመስርተው ፈጽመው በሂሳብ ባለሙያ አልያም የድርጅታቸው ተቀጣሪ በሆነ የሂሳብ ባለሙያ የተዘጋጀ የሂሳብ መዝገብ ማቅረብ አለባቸው።
ግብር ከፋዮች ከግምት የጸዳ የግብር አሰባሰብ ስርዓት የራሳቸውን ሚና እንዲጫወቱ ለማስቻል ይህንን የማሳወቅ ስራ እየሰራን ነው።
በደረጃ “ሀ” እና “ለ” ከ120 ሺ በላይ ግብር ከፋዮች አሉ ከእነዚህ ውስጥ ገቢ እና ወጪያቸውን በአግባቡ እየመዘገቡ ፣ደረሰኝ እየቆረጡ አመታዊ ግብራቸውን የሚያሳውቁ አሉ ነገር ግን ከዚህ ውጪ ሲስተናገዱ የቆዩ ግብር ከፋዮቾም ነበሩ።
ይህ አሰራር ተለምዶ ከአመት አመት ዝም ብሎ በቁርጥ ግብር ለመስተናገድ የመፈለግ አዝማሚያ ይታያል ህጉ ግን ይህንን አሰራር የማይፈቅድ በመሆኑ ከመጪው ሐምሌ ወር ጀምሮ ሲመጡ በተሟላ መንገድ ሂሳብ መዝገባቸውን ይዘው ካልመጡ በስተቀር አይስተናገዱም።
መያዝ አለባቸው እያልን ያለነው በደረጃ “ሀ” እና “ለ” የግብር ከፋይ ተመዝግበው በህጉ መሰረት የሂሳብ መዝገብ እንዲይዙ የሚገደዱትን ብቻ ነው።
ሁሉንም ማለት አይደለም በተሰማሩበት የንግድ ዘርፋቸው ምክንያት እዚህ ውስጥ የማይካተቱ ይኖራሉ የሚመለከተው የተሰማሩበት የስራ ዘርፍ የሂሳብ መዝገብ መያዝ እያስገደዳቸው በተለያየ ምክንያት የማይዙትን እና በቁርጥ ግብር ሲስተናገዱ የነበሩ የንግዱን ማህበረሰብ ነው።
ይህ አይነቱ አሰራር ግብር በዛብኝ በማለት ለሚቀርቡ ቅሬታዎች መፍትሄ የሚሆን ነው ” ብለዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ

