“በፍቅር ያበደች ሴት ካሳየኸኝ የማይሞት ሰው አሳይሀለው” አስገኘው አሽኮ
የኢትዮጵያ የሕግ ባለሙያ ሴቶች ማኅበር :- ሰሞኑን በማህበራዊ ሚዲያው ላይ በአንድ ታዋቂ ሙዚቀኛ (አስገኘው አሽኮ) ሴቶችን በተመለከተ በተሰጠ አስተያየት ላይ ከኢትዮጵያ የሕግ ባለሙያ ሴቶች ማኅበር የተሰጠ መግለጫ
እንደሚታወቀው በሀገራችን የሴቶችና የሴት ህፃናት ጥቃት ከጊዜ ወደጊዜ እየጨመረ፣ አይነቱን እየቀያየረና በአፈፃፀሙም እየረቀቀ የመጣ እጅግ አሳሳቢ ጉዳይ ነው።
ይህንንም ለመከላከል የተለያዩ የሚመለከታቸው አካላት እንዲሁም መላው የህብረተሰብ ክፍል የራሱን አስተዋፅዖ ማድረግ እንዳለበት እሙን ነው።
አብዛኛው የማህበረሰብ ክፍል ጥቃት ምን ማለት እንደሆነ በቂ ግንዛቤ የሌለው ከመሆኑም በተጨማሪ በአንዳንድ ግለሰቦች የሚሰነዘሩ ሴቶችን የተመለከቱ አስተያየቶች ለጥቃት መባባስ ጉልህ ሚና አላቸው።
ከዚህ ጋር ተያይዞ ሰሞኑን በአንድ ታዋቂ ግለሰብ ማለትም በድምፃዊ አስገኘው አሽኮ ሴቶችን በተመከተ በማህበራዊ ሚዲያ ላይ የተደረገው ንግግር ሴቶች በአካላዊ፣ በኢኮኖሚያዊ እንዲሁም በጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች እየደረሰባቸው ካለው ጥቃት በተጨማሪ በጠቅላላው በመፈረጅ የስነልቦናዊ ጥቃት እንዲደርስባቸው ያደረገ እና ብዙ ሴቶችንም ያስቆጣ ተግባር ነው።
በሌላ በኩል ደግሞ ጉዳዩን ብዙ ሰዎች እንዲቀባበሉት እና የበለጠ ሴቶች ላይ እንዲዘባበቱ ያነሳሳም ጭምር ነው።
ድምፃዊው ከዚህ ቀደም “የሀገር ካስማ” በተሰኘው ሴቶችን ለማበረታታት ታልሞ በተሰራ ህብረዝማሬ ላይ በመሳተፍ የሴቶች አጋር መሆኑን በማሳየቱ እንደተቋም እውቅና ሰጥተን የነበረ ሲሆን አሁን ባደረገው ንግግር ግን ሴቶች ላይ የጥላቻ ዘመቻ እንዲከፈት በማድረጉ ማኅበራችን እጅግ ያዘነ መሆኑን ለመግለፅ ይወዳል።
ድምፃዊው በንግግሩ “በፍቅር ያበደች ሴት ካሳየኸኝ የማይሞት ሰው አሳይሀለው” በማለት ሴቶችን ሁሉ በአንድ በመፈረጅ በአጠቃላይ የሴቶችን ስብዕና የሚነካና ሴቶች በህገመንግስቱ የተሰጣቸውን ክብራቸው ተጠብቆ የመኖር መብት የጣሰ አስተያየትን ሰጥቷል።
ይህ ንግግሩም በሀገራችን የጥላቻ ንግግር እና የሀሰተኛ መረጃ ስርጭትን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የወጣውን አዋጅ ቁጥር 1185/2012 አንቀፅ 2(2)፣ 4 እና 7ን የጣሰ እና የወንጀል ተጠያቂነትን የሚያመጣ ተግባር ነው።
በመሆኑም ማኅበራችን ግለሰቡ በተገቢው መልኩ በህግ ተጠያቂ እንዲሆን የሚሰራ መሆኑን እየገለፅን የተፈፀመውን ድርጊት አጥብቀን እናወግዛለን።
ዛሬ ላይ ያለተጠያቂነት የምትታለፍ አንዲት ጥላቻ ነገ ላይ በሴቶች ላይ ለሚፈፀም ከባድ ዘመቻ በር ከፋች በመሆኗ ይህንን ንግግር የምታሰራጩ የማህበራዊ ሚዲያዎችም ይህን ከማድረግ እንድትቆጠቡ እናሳስባለን።
በሴቶች ላይ የሚፈፀም ጥቃትን መከላከል የሁሉም የህብረተሰብ ክፍል ሀላፊነት ነው።
በሴቶች ላይ የሚፈፀም የጥላቻ ንግግርን አጥብቀን እንቃወማለን!!
Via የኢትዮጵያ የሕግ ባለሙያ ሴቶች ማኅበር
መጋቢት 28 ቀን 2017 ዓ.ም አዲስ አበባ

