የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረንስ / ኦፌኮ በመጪው ምርጫ እንደሚሳተፍ መገለጹ አላግባባም። ፓርቲው በምርጫ ይሳተፋል ያሉት አቶ ጥሩነህ ገምታ ናቸው። መናገራቸውን ተከትሎ ውዝግብ በመነሳቱ ፓርቲው ለዛሬ አስቸኳይ ስብሰባ ጠርቷል።
የጠራው ስብሰባ አቶ ጥሩነህን ለማውገዝ ቢሆንም በስብሰባው “ምርጫ አንሳተፍም” የሚል አቋም እንደማይያዝ ዜናውን የተናገሩት አመልክተዋል። በውጭ ያሉት የፓርቲው ደጋፊዎችና የቅርብ ሰዎች የተለየ አቋም አላቸው።
የኦፌኮ ስራ አስፈጻሚን አቶ ጥሩነህ ገምታ ሰሞኑን ፓርቲያቸው በምርጫ እንደሚሳተፍ አስታወቀዋል። እሳቸው እንዳሉት በመጪው ፓርቲ ካልተሳተፉ ኦፌኮ ከፓርቲነት ስለሚሰረዝ ምንም ይሁን ምን በምርጫ እንደሚሳተፉ አስታውቀው ነበር።
ይህን ዜና ተከትሎ በውጭ አገር የሚኖሩ የፓርቲው ደጋፊዎችና የቅርብ ሰዎች አቶ ጃዋርን ጨምሮ “እንዴት አሁን ላይ በዚህ መልኩ ምርጫ ላይ ስለመሳተፍ ይገለጻል። ይህ ብልጽግናን በዓለም ዓቀፍ ደረጃ ስሙን ማደስ ነው” በሚል ተቃውመዋል። ተቀዳሚ ዋና ሊቀመንበሩ አቶ ጃዋር መሐመድ ከፋኖ፣ ከትህነግና ሻዕቢያ ጋር በይፋ እየሰሩ እንደሆነ በአደባባይ እየገለጹ ቢሆንም ፓርቲው ድርጊቱን በይፋ አውግዞ አያውቅም።
አቶ ጃዋር ፓርቲውን ከተቀላቀሉ በሁዋላ “ተገፍተናል” በሚል ከኦፌኮ የለቀቁ የኦፌኮ ነባር የዞን አመራሮች ለኢትዮሪቪው እንዳስታወቁት፣ አቶ ጥሩነህ ገምታ ከስራ አስፈጻሚው ውሳኔ ውጪ ኦፌኮ በምርጫ እንደሚሳተፍ በመናገራቸው ዛሬ በተጠራው አስቸኳይ ስብሰባ ይገመገማሉ።
” አቶ ጥሩነህ ገምታ የሰጡት መግለጫ በስብሰባ ውሳኔ እንደማይቀየር አረጋግጠናል” ያሉት የዜናው ሰዎች፣ የግምገማው ዓላማ “ለምን አሁን” በሚል ብቻ እንደሆነ ጠቁመዋል።
በምርጫ አለመሳተፍ መንግስትን ማሳጣትና ለተቃውሞ አንዱ ዋና ቁልፍ ጉዳይ በመሆኑ አቶ ጥሩነህ ፓርቲው በውስጥ የያዘውን አቋም አስቀድመው መናገራቸው በትክክል እንደተባለው መሆኑን ለማረጋገጥ የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት በስልክ በጽሁፍና በመደወል ልናገኛቸው ብንሞክርም መልስ አልሰጡም።
ዛሬ ከስብሰባው በሁዋላ ፓርቲው የተለየ ሃሳብ ያለው መግለጫ ያወጣል ብለው እንደማይጠብቁ ያሉት ክፍሎች “ምን አልባት ምርጫው ሲቃረብ መናገር አለብን የሚል አቋም ካተያዘ በቀር ኦፌኮ በምርጫ አልወዳደርም አይልም” ብለዋል።
ኦፌኮ ባለፈው ምርጫ ባለመሳተፉ ምክንያት መጪውን ምርጫ “ይለፈኝ” ካለ በምርጫ ቦርድ ህግ መሰረት ሁለት ጊዜ ከምርጫ ራሱን ያገለለ ፓርቲ እንደሚሰረዝ ስለሚደነግግ በመጪው ምርጫ መሳተፉ ግድ ነው።
የዞን አመራሮችን ጨምሮ በርካታ አባላቱ ወደ ብልጽግና የፈለሱበት ኦፌኮ አሁን ባለው ድርጅታዊ አቋም በመላው ኦሮሚያ መወዳደር የሚያስችል አቅም እንደሌለው የሚናገሩ አሉ።
ከዚህ ቀደም እነዚህኑ ምንጮችና ስማቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁ የኦፌኮ አመራርን ጠቅሰን እንደዘገብነው የኦነግ አመራሮችና አባላት ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ፓርቲውን ጥለው ሄደዋል። የተቀሩት እጅግ ጥቂት ብቻ ናቸው። ኦፊኮም በርካታ የዞን አመራሮቹን ከበታች ካድሬዎች ጨምሮ ማጣታቸውን ጠቀሰን መጻፋችን ይታወሳል።
ይህ እስከታተመ ድረስ ስብሰባ የተቀመጠው የድርጅቱ ስራ አስፈጻሚ ውሳኔ ይፋ አልሆነም።

