ኢትዮጵያ ሁለት ሊታረቁ የማይችሉ ጎዳና ላይ ትገኛለች። አንደኛው ጠቅላይ ሚኒስትር የሚከንፉበት “የፈጥነት ባቡር” ሲሆን፣ ሌላኛው መንገድ ደግሞ መልካቸውንና ቁመናቸውን መሽቶ ሲነጋ የሚቀያይሩ፣ ጠዋት ተጣምረው ከሰዓት በሚበተኑ፣ ቋሚ መርህና አማራጭ አሳብ ሳያቀርቡ በመቃወም ብቻ የሚያዘግሙበት የእድሜ ልክ የሽግግር መንግስት ናፋቂዎች ባቡር …
አብይ አሕመድ እንደሚሉት ፍጥነትና ተኝታ ለኖረች አገር ፍቱን መድሃኒት ነው። እሳቸው እንደሚሉት የተለየነውን ዓለም መቀላቀል የምንችለው በፍጥነት ጉዞና በከፍታ በመብረር ነው። ሌሎቹ ደግሞ ትንሽ ደስኩረው ማሳረጊያቸው “ሽግግር መንግስት፣ አዲስ ጥምረት፣ የተለያዩ የህብረትና የቅንጅት ስም ማስተዋወቅ፣ የምድሩን ጨርሰው በሰማይ ላይ ‘አንቀጥቅጥ’ ስለፍ አለን” የሚሉቱ ናቸው።
ሰውየው ኢህአዴግን ሲያፈርሱ የሮጡበት ፍጥነት ያልገባቸው ዛሬ ላይ በፍጹም ጥላቻ የተቀነባበረ ዘመቻ ላይ የተረባረቡት ኢትዮጵያን ለዚህ ሁሉ ጣጣ የዳረጋት የዘር ፖለቲካ እየከሰመ መሄዱ፣ በቀጣይም የዘር ፖለቲካ ሕዝብ ስለጠላው ለተቀናቃኞች ለቅሶ ሲባል እንደማይቀጥል ግልጽ እየሆነ በመምጣቱ እንደሆነ የገባቸው እየተናገሩ ነው። የፍጥነትን ጉዳይ አስመልክቶ ስብሃት ነጋ የተናገሩት እጅግ ገላጭ ይሆናል።
“ጠዋት ስንነቃ ብዙ አዳዲስ ነገር ይዞ ይመጣል። እኛ በዚህኛው ጉዳይ ለመነጋገር ቀጠሮ ስንይዝ በላይ በላይ ብዙ ነገር ይደራረባል። ፍጥነቱን አልቻልነውም” በሚል ስብሃት ነጋ ትህነግ ወደ መቀለ ከተመለሰ በሁዋላ መናገራቸው ይታወሳል። ዶክተር ደብረጺዮንም በተመሳሳይ “ጠዋት እዚህ ሲባል…” ብለው ፍጥነታቸውን አልቻልነውም ብለው ነበር።
ስብሃት ነጋ የመጡበትና የኖሩበት የትህነግ ፖለቲካዊ ባህል በአንድ ጉዳይ ሶስት ወር በር ዘግቶ መገማገም ነው። በራሳቸው ታጋዮች በተደጋጋሚ ምስክርነት ሲሰጥ ለዓመትም የቆዩበት ጊዜ አለ። የሚያስገርመው ትህነግ ሊገማገም በር ዚዘጋ ሕዝብ ቁጭ ብሎ የመጠበቁ ጉዳይ ነው።
አብይ አሕመድ ወደ ስልጣን ሲመጡ ይህ ባህል ተቀይሯል። ሁሉም ስራ ፍጥነቱ አስገራሚ ሆኗል። በፕሮጀክቶች አፈጻጸም ጭምር የታየው የማድረስና የመፈጸም ብቃት ትህነግ ከኖረበት ባህል ጋር የሚጣጣም ባለመሆኑ መቸገራቸውን በመደነቅ የመሰከሩትም ወደው አልነበረም።
ከፋና ጋር አራተኛውን መጽሃፋቸውን አስመክቶ ማብራሪያ የሰጡት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ፣ ስለፍጥነትና ሲናገሩ ከከፍታ ጋር በማያያዝ ነው። ለውጡን መከተል ያልቻሉና ለማደነቃቀፍ የሞከሩትም የተንጠባጠቡት በዚሁ የፍጥነትና የከፍታ ጉዞ መቀጠል አለመቻላቸው ነው።
በአንድ አውሮፕላን ውስጥ እባብ የተመለከተች የበረራ አስተናጋጅ፣ ለፓይለቱ እባብ ማየቷን ነገረችው። ፓይለቱም የእባቡን መኖር ሲሰማ የአውሮፕላኑን ከፍታ ጨመረ። ከዚያም የበረራ አስተናጋጇን “ሂጂና እይው” አላት። እንድተባለችው ሄዳ ስትመለከተው እባቡ እንዳልሆን ሆኖ አክትሞለታል። ተመልሳ ለፓይለቱ ያየችውን ነገረችው። ፓይለቱን ከፍታ ሲጨምር እባብ መተንፈስ እንደሚሳነውና ላይመለስ እነደሚሰናበት አስረዳት።
ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ለውጡ ከፍታውን መጨመሩና በፍጥነት መካሄዱ ሊያደነቃቅፉና የራሳቸውን የቀድሞ እሳቤ ሊመልሱ የፈልጉ ሳይሳካላቸው ሊንጠባጠቡ መቻላቸውን ለማስረዳት ነበር ይህን ምሳሌ ያነሱት። ከላይ የተገለጹት ሁለቱ ቱባ የትህነግ መሪዎች “ፈጥነቱን አልቻልነውም” ያሉት ከዛሬ ሰባት ዓመት በፊት ለውጡን ተከትለው ወደ መቀለ ከተመለሱ በሁዋላ ነበር።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህን ያሉት የመደመር መንግስት የሚለውን መጽሃፋቸውን አስመልክቶ ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት ነው። ከዚህ ቀደም በመደመር ሐሳብ ላይ ያተኮሩ መደመር፣ የመደመር መንገድ እና የመደመር ትውልድ የተሰኙ ሦስት መጽሐፍትን ለንባብ ማብቃታቸው ይታወቃል፡፡
ሃሳብ አልባ ፖለቲካ
የፖለቲካ መረጋጋት እና መግባባት መፍጠር ሌላኛው አስቻይ ሁኔታ እንደሆነ ጠቅሰው ፥ ይህም የፖለቲካ ስርዓት መረጋጋት የማሕበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ለውጦችን በፍጥነት ለመምራት መሰረት እንደሚጥል አስረድተዋል።
ይህንን ለማሳካት የመደመር መንግስት እስካሁን ባለው ልምምድ ሆደ ሰፊነትን የሚከተል እንደሆነ እና አንዳንድ ነገሮችን ይቅር በማለት በዋናው ግባችን ላይ ማተኮር እና የጋራ ራዕይ በትብብር ለሚደረግ ጥረት የልብ ምት ነው ብሎ ያምናል ብለዋል።
በዚህ ውስጥ ሃሳብ አልባ የፖለቲካ ተግዳሮት ከብልጽግና ግብ እንዳንደርስ መደነቃቀፍን የሚፈጥር ነው ብለዋል።
የመደመር መንግስት ብቸኛ ከዚህ ማምለጫ መንገዱ የሀሳብ ገበያ በመፍጠር፤ ይህም እንዲሰፋ እና እንዲሻሻል ማድረግ እንደሆነ ያብራራል ነው ያሉት።
በፖለቲካ ምሕዳር ውስጥ እውነት እና እውቀት እንዲሰለጥኑ ማድረግ እንዲሁም መርህ እና ሕጋዊ ሂደትን የሚከተል ተቋማዊ አሰራር ማስፋት እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል።
ብሔራዊ መግባባትን ለማምጣት እና የሀገራችንን ችግር ለመፍታት አማራጭ ሃሳቦች እንዲበራክቱና አማራጭ ሀሳቦችን በመደመር መፍትሔ መፍጠር ከሀሳብ አልባ ፖለቲካ ማምለጫ መንገድ እንደሆነ አስገንዝበዋል።
የመደመር መንግስት ከሌሎች የመንግስታት እሳቤዎች በውጤቱ ይለያል
የመደመር መንግሥት ከሌሎች የመንግስታት እሳቤዎች በውጤቱና ሂደቱ ይለያል አሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የመደመር መንግሥት በተሰኘው አዲሱ መጽሐፋቸው ዙሪያ ከፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን ጋር ባደረጉት ቆይታ፥ የመደመር መንግሥት ዋነኛ ግብ ኢትዮጵያን ለውስን ግለሰቦችና ቡድኖች ፍላጎቶች ሳይሆን ለኢትዮጵያዊያን መሻቶች ማስረከብ ነው ብለዋል፡፡
ሁለንተናዊ ብልጽግናን ለማሳካት በሂደቱ አቅምና አቋም መደመር እንዳለባቸው ጠቅሰው፥ በዚህም ሁሉም ኢትዮጵጵያውያን ዜጎች በሀገራቸው ጉዳይ እንዲሳተፉ በመደረጉ አጋር ተብለው የነበሩ ክልሎች በመደመር መንግስት የሀገር ባለቤት መሆናቸውን አንስተዋል፡፡
በመንግስትና ዜጎች መካከል ሚዛናዊ ግንኙነት እንዲኖርና ጤናማ ስርዓት እንዲገነባ እየተሰራ ነው ያሉ ሲሆን፥ የበዛ ነጻነት ወደ ስርዓት አልበኝነት ስለሚመራ ሚዛናዊነት አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የታለመው ግብ ጋር ለመድረስ በመንግስት በኩል ሁሉንም ነገር በመጠቅልል አምባገነናዊ ስርዓት እንዳይፈጠርና ህጋዊነቱን በምርጫ ከዜጎች እንዲያገኝ ሚዛናዊነትን መከተል አስፈላጊ መሆኑንም ነው ያነሱት፡፡
የመደመር መንግስት መገለጫ ምናባዊ ከፍታ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ በሰሩት ስራ በመርካት መቆም እንዳይኖር በምናባዊ ከፍታ አሻግሮ ማየትና ስራን መከወን እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡
ሌላኛው የመደመር መንግስት መገለጫ የማድረግ አቅም መሆኑን ጠቁመው፥ የታቀዱ ህልሞችን መጨረስና መሬት ላይ ማውረድ ባህሪው ነው ብለዋል፡፡
የተላማጅነት ባህሪ የመደመር መንግስት ሌላኛው መገለጫው ሲሆን፥ ለዚህም የኮቪድ 19 ወረርሽኝን ጨምሮ ሌሎች ችግሮችን ወደ እድል የተቀየረበትን መንገድ አንስተዋል፡፡
“የመደመር መንግስት” የተሰኘው 4ኛ መጽሐፍ በተመለከተ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት፤ በአሁኑ ወቅት የኮሪደር ልማት ስራዎች ምስክርነት እየተሰጠባቸው ነው ብለዋል።
ለማሳያነትም እንጦጦ ሽሮሜዳ አካባቢ የተከናወነው የኮሪደር ልማት ከዚህ ቀደም ያልነበሩ ከ700 በላይ አዳዲስ የቢዝነስ ሱቆች መከፈታቸውን ጠቁመው፤ ይህም ለበርካታ ሰዎች የስራ ዕድል መፍጠሩን ተናግረዋል፡፡
የወንዝ ዳርቻ ልማት ለበርካታ ሰዎች የቢዝነስና የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ጠቁመው፤ ለመላው አፍሪካ ልክ እንደ አረንጓዴ ዐሻራ ምልክትና አርአያ ሊሆን የሚችል ስራ ነው ብለዋል።
የኮሪደር ልማት በተለያየ መልኩ ስራ መፍጠር፣ የሀገርን ገጽታና ምልከታ መቀየር እንዲሁም ጤናማነትን ማረጋገጥ የቻለ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
የኮሪደር ልማት ለሁሉም አፍሪካ ምሳሌ መሆን የሚችል እንደሆነ አንስተው፤ በአሁኑ ወቅት የአፍሪካ መሪዎች ልዑካን እየላኩ ልምድ የሚቀስሙበትና የሚቀምሩበት ነው ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ የከተማ ኮሪደር ልማት፣ የወንዝ ዳርቻ ልማትና የገጠር ኮሪደርና ፕሮጀክቶች የሚጨበጡ፣ የሚታዩ ስራዎች መሆናቸውንም ገልጸዋል፡፡
ስራዎቹ ኢትዮጵያውያን በሙሉ ሊኮሩባቸው የሚገቡ ልማቶች መሆናቸውን አንስተው፤ እጅግ የሚያኮራ በመደመር መንግስትና በህዝብ መካከል ባሉ የጋራ ራዕይ ስነቃ የተገነቡ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡
የኮሪደር ልማት ከፍተኛ ምሳሌያዊ ስራ ሆኖ ለብዙ ሀገራት የሚያገለግል፤ የመደመር ትውልድ በዘመኑ ውስጥ ያስቀመጠው አሻራ፣ የማይናወጥና አኩሪ ተግባር መሆኑንም አብራርተዋል፡፡
መደመር በሁሉም ሕብረተሰብ ውስጥ የሚገኝ ኢትዮጵያዊ እሳቤ ነው
ጠቅላይ ሚኒስትሩ “የመደመር መንግሥት” የተሰኘውን አዲሱ መጽሐፋቸውን በተመለከተ ከፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን ጋር ባደረጉት ቆይታ እንዳሉት÷ መደመር የተሟላ የፖለቲካ እና ኢኮኖሚያዊ ሥርዓታዊ ምላሽን የሚያረጋግጥ ሰፊ ጉዳዮችን በውስጡ የያዘ ጉዳይ ነው።
መደመር ውስብስብ ችግሮችን ለመፍታት፣ ሥርዓታዊ ምላሽ ለመስጠት የተነደፈ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ እሳቤ እንደሆነም አብራርተዋል፡፡
የመደመር እሳቤ ‘ከደቡብ አፍሪካው ኡቡንቱ’ እና ‘ከግሪኩ ወርቃማው አማካይ’ የተለየ መሆኑን አንስተው÷ ስለግለሰቦች ግንኙነት ብቻ ሳይሆን ውስብስብ ችግሮችን ሥርዓታዊ መፍትሔዎችን ለማምጣት የተነደፈ ነው ብለዋል፡፡
በተፈጥሮ ያለው የሃብት እጥረት፣ ከሰው ተፈጥሯዊ ባህሪ የተነሳ ፉክክር እንደሚፈጠር እና ሰው መልካም እና ለሌሎች አሳቢ በመሆኑ ደግሞ መተባበር እንደሚፈጠር ፤ሁለቱም እኩል ሆነው ሚዛናቸውን ካልጠበቁ ደግሞ መልሰው ችግር እንደሚፈጥሩ አንስተዋል።
ትብብር የሌለበት ሕይወት ተስፋ አስቆራጭ እንደሆነ እና ትብብር ሲበዛ ደግሞ ስንፍና እንዲበራከት እና ፈጠራ እንዲቀንስ፤ ለለውጥ ዝግ እንዲሆን እንደሚያደርግ ገልጸው÷ ፉክክር ሲበዛ ወደ ግጭት እና ወደ መጠፋፋት እንደሚያመራ እና ይህም መልሶ ችግር እንደሚፈጥር አመልክተዋል።
የመደመር መንግስት ሙሉ ዕይታ በግልጽ ለመረዳት ሙሉ ዕይታ መኖር፣ የተሰናሰለ ተግባር፣ ገቢር ነበብነት እሳቤ ሊኖረን ይገባል ነው ያሉት።
መደመር በሁሉም የኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ውስጥ የሚገኝ ኢትዮጵያዊ እሳቤ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ÷ የእኛ የሚለየው የነበረንን የመደመር እሳቤ ፍልስፍናዊ በሆነ መንገድ ተንትነን፤ የፖለቲካ እና የኢኮኖሚ እሳቤ አድርገን መቀመራችን ነው ሲሉ አብራርተዋል።
የመደመር እሳቤ ሀገር በቀል ነው የምንለው ሁላችንም በዚህ እሳቤ የኖርንበት፣ የሰራንበት እና የቀጠልንበት በመሆኑ እንደሆነ እና ከኢትዮጵያ ውጪ በዝርዝር ‘መደመር’ በሚል መጠሪያ፣ በውጤት እና በሂደት ስለ አንድ ሀገር መንግስትና ኢኮኖሚ ደረጃ በሚያስቀምጠው መልክ የትም ሀገር በንድፍ ደረጃ የሌለ መሆኑን ጠቁመዋል።
የፋና መረጃዎች ከሌሎች የግል እየታዎች ጋር አንድ ላይ የቀረበ


