ትግራይን እንዲመሩ በፌደራሉ መንግስት የተሰየሙት የቀደሞው ሌተናል ጄነራል ታደሰ ወረደ አቋም አነጋጋሪ እንደሆነ ቀጥሏል። ትህነግ ባዘጋጀው ኮንፍረስን ላይ መንግስትን ለመጣል በቂ ትጥቅና ኃይል እንዲሁም አጋዦች እንዳሉ ባስታወቁ ማግስት ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ጎን የታዩት ታደሰ ወረደ ሌ/ጄነራል ፃድቃን ገብረትንሳኤ ከሰዋቸዋል። ክሱም ተጨባጭ ዝርዝር ያለውና በትግራይ ለውጥ ለማምጣት የተቀናጁት ክፍሎች እሳቸው ከሃላፊነት እንዲነሱ በቅድመ ሁኔታ ማስቅመጣቸው አመልክተዋል።
በፕሪቶሪያው ስምምነት መሰረት የትግራይን እንዲመራ የተቋቋመውን ጊዜያዊ አስተዳደር ከማገዝ ይልቅ፣ የክልሉ የጸጥታ ኃላፊነታቸውን ተገን በማድረግ ክህደት መፈጸማቸውን ሌ/ጄነራል ፃድቃን ገብረትንሳኤ አስታውቀዋል።
ለኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ሰፊ ቃለ መጠየቅ የሰጡ ሌ/ጄነራል ፃድቃን፣ ዝርዝር ባይሆንም ኢትዮጵያ ድጋሚ አሰብን የመውሰድና የኢትዮጵያን ታሪካዊ ጠላት ሻዕቢያን ለማስወገድ መልካም አጋጣሚ የነበርበት ወቅት ላይ ኢትዮጵያን ይመሩ የነበሩት አቶ መለስን ጨምሮ በርካታ ባለስጣናት አጋጣሚውን ለመተቀም የቀረበውን አሳብ ውድቅ ማድረጋቸውን አስታወቅዋል። ከአቶ ተፈራ ዋልዋ በስተቀር ሁሉም በሚባል ደረጃ የኢሳያስ ደጋፊ እንደነበሩ በቁጭት ሲናገሩ፣ ታደሰ ወረደ እያሉ በትግራይ ለወጥ ለማምጣት እንደሚያስቸግር አቋም መያዙን አመልክተዋል።
ጊዜያዊ አስተዳደሩን በሴራና በትጥቅ ያፈረሱት የዛሬው የትግራይ መሪ መነሳት እንዳለባቸው የትግራይ ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ሶስት ታዋቂ ግለሰቦች ያካተተው ጥምረት እንደ ቅድመ ሁኔታ ማስቀመጡን ያስታወቁት ሌ/ጄነራል ፃድቃን፣ የፌደራል መንግስት እንዴት ከታደሰው ወረደ ጋር እንደሚሰራ ግራ እንደሚገባቸውም አመልክተዋል። ምን ምክኛት እንዳለው የሚያውቀውም የፌደራል መንግስቱ እንደሆነ ጠቁመዋል።
ጄነራሉ በሰጡት ሰፊ ቃለ ምልልስ፣ “ የትግራይ ህዝብ ከሻዕቢያ መንግስት ጋር የሚደረግ ትብብር/ፅምዶ አልፈልግም ነው ያለው “ በሚል አሁን ላይ ስላለው አዲስ የፖለቲካ ሽርጉድ አስታውቀዋል።
ትግራይ የሚገኙት የትህነግ አመራሮች ከሻዕቢያ (ከኢሳያስ መንግሥት ጋር) ሽርክና በመፍጠር ጦርነት ለመቀስቀስ እየሰሩ ሌ/ጄነራል ፃድቃን ገብረትንሳኤ ሲያስታውቁ ከፋኖ ጋር ጭምር ጥምረት ተፈጥሮ አገር የማተራመስ ስራ እየተሰራ ነው ሲሉ አስረድተዋል።
ሌ/ጄነራል ፃድቃን ፤ የትህነግ ሰዎች ከኢሳያስ መንግስት ጋር በማበር ጦርነት ለመቀስቀስ እየሰሩ ያሉት የወንጀል ስራዎቻቸውን ለመሸፈን እንደሆነ ጠቁመዋል። “ የወንጀል ስራዎች እና ወደ ጦርነት የተገባበት ውሳኔ እራሱ (የቀድሞው ጦርነት) accountable መሆን አለበት “ ብለዋል።
ሌ/ጄነራሉ ፥ እጅግ በጣም ብዙ የጠፉ ፣ የተሰረቁ ፣ የተዘረፉ ንብረቶች፣ ወርቅ፣ መሬት ፣ ገንዘብ እንዳለ ጠቁመዋል። በዚህ የወንጀል ተግባር ውስጥ በግልጽ የሚታወቁ ትላልቅ አመራሮች እንዳሉበት ገልጸዋል።
እነዚህ አካላት የወንጀል ስራዎቻቸውና የፖለቲካ ስልጣን ፍላጎታቸው አንድ ላይ እንደተቀላቀሉ ፤ ይህን ለመከላከል ወይም ከሰሯቸው የወንጀል ስራዎች ነጻ ለመሆን የሚያስችላቸው አንዱ መንገድ ጦርነት መፍጠር እንደሆነ እንደሚያምኑ አመልክተዋል። ለዚህም “ ከኢሳያስ መንግሥት ጋር መተባበር ነው – ፅምዶ “ ብለው እየሰሩበት እንደሆነ ገልጸዋል።
“ የትግራይ ህዝብ እያንዳንዱ የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ አውቆባቸዋል “ ያሉት ሌ/ጄነራሉ ፤ የትግራይ ጄኖሳይድ ኮሚሽን ባጠናው ጥናት በትግራይ ጦርነት ወቅት 75% የግፍና የወንጀል ስራዎችን የሰራው የኤርትራ ሰራዊት እንደሆነ መመላከቱን ተናግረዋል።
- ሰው የገደለው
- ሴቶች የደፈረው
- ሴቶች ማዕፀን ላይ ያልሆነ ነገር ያስገባው የኤርትራ ሰራዊት እንደሆነ ገልጸዋል።
“ የአክሱም ነፍሰ ገዳይ የሻዕቢያ ወታደር ነው ፤ የማህበረ ደጎ ነፍሰ ገዳይ የሻዕቢያ ወታደር ነው ፤ የማርያም ደንገላት ነፍሰ ገዳይ የሻዕቢያ ወታደር ነው ፤ ደቡብ ትግራይ ራያ ላይ መጥቶ በመቶዎች የሚሆኑ ሰዎችን ረሽኖ የሄደው የሻዕቢያ ወታደር ነው “ ብለዋል።
ህዝቡ ይሄንና የወታደራዊ እና የፖለቲካ መሪዎቹን ፍላጎት እንዲሁም የሚያደርጉትን ግንኙነት ስለሚያውቅ ከሻዕቢያ ጋር የሚደረግ ትብብር /ፅምዶ “ አልፈልግም “ ነው ያለው ሲሉ ተናግረዋል።
ከእነሱ ጋር በወንጀል የተሳሰረው ካልሆነ በስተቀር ህዝቡ ከኢሳያስ መንግሥት ጋር መተባበር ጥፋት እንደሚያመጣ አምኖ አልተቀበለውም ሲሉ አክለዋል።
እነዚህ ጦርነት እንዲነሳ የሚፈልጉ እና እየሰሩ ያሉ አካላት በኤርትራ ፣ በሱዳን በኩል ጥይት፣ ጠመንጃ እንደሚያስገቡ ፤ የጦር መሳሪያም እንደሚገዙ ይህንንም ሰው እንደሚያውቅ ሌ/ጄነራል ፃድቃን ገብረትንሳኤ ተናግረዋል።
ሌ/ጄነራሉ በትግራይ ጦርነት ወቅት ጦር የመሩ፣ በኃላም የሰላም ስምምነቱን ተከትሎ በትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ውስጥ ከፍተኛ አመራር ሆነው የሰሩ ፣ አለመግባባት ሲፈጠር ትግራይን ለቀው የወጡ አንጋፋ የትግራይ ጄነራል ናቸው።



