ምንም ያህል የቆዳ ቀለም ልዩነት ቢኖረን፣ መኖሪያችንም ቢለያይ፣ ምንጫችን ከአፍሪካ ነው ሲሉ የሰው ዘር መነሻ የሆነችው ሉሲን ያገኙት ፕሮፌሰር ዶናልድ ጆሃንሰን ተናገሩ።
የ3.2 ሚሊዮን ዓመት ዕድሜ ያላት የሰው ዘር መነሻዋ ሉሲን ቅሬተ አካል በአፋር ያገኙት ፕሮፌሰር ጆሃንሰን፣ ሉሲ የተገኘችበትን 50ኛ ዓመት ኢትዮጵያ መጥተው አክብረዋል።
ፕሮፌሰር ጆሃንሰን ከኢቲቪ ጋር በነበራቸው ቆይታ፥ ከግማሽ ምዕተ ዓመት በፊት የሉሲን ቅሬተ አካል ባገኙበት ወቅት ወጣት ተመራማሪ እንደነበሩ አስታውሰው፤ “አዲስ ነገር እንደማገኝ ተስፋ ነበረኝ” ይላሉ።
ከተደጋጋሚ ፍለጋ በኋላ ህዳር 24 ጠዋት የሉሲን ቅሬተ አካል አገኘን ያሉት ፕሮፌሰር ጆሃንሰን፣ አነስ ያለ ቅሬተ አካል ሳገኝ የራሴን አካል ያገኘሁ ያህል ነበር የተሰማኝ በማለት ይገልፃሉ።
ከዚያም ተጨማሪ ቅሬተ አካል እያገኘን ስንሄድ የሰው ዘር መገኛ ከዚህ ከኢትዮጵያ መሆኑን ተረዳሁ የሚሉት ፕሮፌሰሩ፤ ሉሲን ያገኘሁበት ቅጽበት ህይወቴንና ሙያዬን ያገኘሁበት ጭምር ነው ሲሉ ይገልፃሉ።
አካባቢው የተለያየ ስያሜ የሚሰጣቸው ቅሬተ አካላት መገኛ መሆኑን ያወቅነውም ያኔ ነበር የሚሉት ፕሮፌሰሩ፤ ዛሬ በተለያየ ሁኔታ ውስጥ የምንገኝ ሰዎች መገኛችን ኢትዮጵያ ናት ብለዋል።
ፕሮፌሰር ዶናልድ ጆሃንሰን፥ “ወደ ኢትዮጵያ በመጣሁ ቁጥር የማስበው ህብረተሰቡ የባህል ሃብታም መሆኑን ነው” ብለዋል።
በኢትዮጵያ ስለ ሰው ልጅ አመጣጥ የሚደረግ ምርምር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል ያሉት ፕሮፌሰሩ፤ ምንም እንኳን ሉሲ ከ3 ሚሊዮን ዓመታት በፊት የኖረች ብትሆንም የሚያገናኘን ነገር እንዳለ እረዳለሁ በማለት ነው የገለጹት።
በኢትዮጵያ ተወልደው ያደጉ፣ የሰለጠኑ ባለሙያዎች አሉ የሚሉት ፕሮፌሰር ዶናልድ ጆሃንሰን፤ እነዚህም ወደፊት በሰው ዘር አመጣጥ ሳይንስ ዘርፍ መሪ የሚሆኑ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ሊገኙ የሚችሉ አዳዲስ ክስተቶችንም የሚመሩ ይሆናሉ ብዬ አስባለሁ ብለዋል።
የቱሪዝም ሚኒስቴርም የሉሲ ቅሬተ አካል የተገኘበት የአፋር መልዓ ምድር በስፋት እንዲጎበኝ ትልቅ ስራ መስራት አለበት ሲሉ ምክረ ሃሳባቸውን አቅርበዋል።
በመሀመድ ፊጣሞ

