አዲስ ሪፖርተር – ማሩ አሁንም ጣፋጭነቱ የሚያስደምም ነው ተብሎለታል። የንብ ማር ልዩ ባህሪያት በድጋሚ በአስደናቂ ሁኔታ ተረጋግጧል የተባለ ሲሆን በግብፅ በሚገኙ ጥንታዊ የቀብር ስፍራዎች ውስጥ ለ3,000 ዓመታት ያህል የተቀመጠ ማር አሁንም ሳይበላሽ መገኘቱ የሳይንስ ሊቃውንትን አስገርሟል።
የማር ረጅም ዕድሜ ምስጢር በኬሚካላዊ ቅንብሩ ውስጥ ይገኛል ተብሏል። ማር የውሃ መጠን በጣም ዝቅተኛ ሲሆን፣ ከፍተኛ የስኳር ይዘት ያለው እና አሲዳማ በመሆኑ ባክቴሪያዎች እና ረቂቅ ተህዋሲያን እንዲያድጉበት አይፈቅድም ተብሏል።
ይህ ተፈጥሯዊ ሂደት ማሩን ለረጅም ጊዜ እንዲቆይ የሚያደርግ እንደ መከላከያ (preservative) ያገለግላል ተብሎለታል።
ምንም እንኳን “ማር አይበላሽም” የሚለው አባባል የተለመደ ቢሆንም፣ የሳይንስ ሊቃውንት ይህን ያህል ረጅም ዕድሜ እንዲኖረው የረዳው በግብፅ የቀብር ስፍራዎች ውስጥ የነበረው ደረቅና ከውጭ ተጽእኖ የፀዳ አየር አስተዋጽኦ እንዳለው ይገልጻሉ። ይህ ሁኔታ የማሩን ጥራት ለመጠበቅ ወሳኝ ነበር ተብሎለታል።
ይህ ግኝት የማርን ልዩ ተፈጥሮ ከማሳየቱም በላይ፣ የጥንት ግብፃውያን ለሕይወት አስፈላጊ የሆኑ ቁሳቁሶችን ለዘለቄታው ለማስቀመጥ የነበራቸውን ጥልቅ ግንዛቤ የሚያሳይ ነው ተብሏል።
ይህ ጥንታዊ ማር ለምግብነት ሊውል ቢችልም፣ በታሪክና በሳይንስ ምርምር ረገድ ያለው ጠቀሜታ ከጣዕሙ በላይ የላቀ ነው ተብሏል።

