የተለያዩ የኤርትራ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ጥምረት በመመስረት በጋራ ለመታገል መወሰናቸውን አስታወቁ
የተለያዩ የኤርትራ ተቃዋሚ ፓርቲዎች አምባገነን ያሉትን አሁን በሥልጣን ላይ ያለውን መንግሥት ለመታገል የጋራ ጥምረት መመስረታቸውን አስታወቁ።
ፓርቲዎቹ በደቡብ ምዕራብ ጀርመን በምትገኘው ቪዝባደን በተባለችው ከተማ ሲያካሂዱት የነበረውን ጉባኤ ማጠናቀቃቸውን ገልጸዋል።
«የኤርትራ ፖለቲካዊ ሃይሎች ጥምረት» የተሰኘ የጋራ ግንባር መመስረታቸውን የአደራጅ ኮሚቴው ምክትል ፕሬዚደንትና የቀይ ባሕር ዓፋር ዴሞክራሲያዊ ድርጅት ከፍተኛ አመራር አባል አቶ ያሲን መሐመድ ዓብደላ እንደገለጹለት የጀርመን ድምጽ ሬድዮ ዘግቧል።
የኤርትራ ፖለቲካዊ ሃይሎች ጥምረት የተባለው የጋራ ግንባር የመሰረቱት ፓርቲዎች የቀይ ባሕር ዓፋር ዴሞክራሲያዊ ድርጅት፣ የኤርትራ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ እና በሥሩ አራት ፓርቲዎችን ያካተተው የኤርትራ አንድነት የጋራ ግንባር የተባሉ እንደሆኑ አቶ ያሲን መግለጻቸውን ዘገባው አስታውቋል።
ኤርትራ ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች የሚከበሩባት ሀገር እንድትሆን፣ የራስን ዕድል በራስ የመወሰን መብት እንዲከበር፣ በሕገ መንግሥት የሚመራና ተገማች መንግሥት ለማቋቋም፣ በኤርትራ የመድብለ ፓርቲ ሥርዓት እንዲቋቋም በጋራ ለመሥራት መስማማታቸውን ዘገባው አካቷል። ለአፍሪቃ ቀንድ መተራመስ አስተዋጽኦ እያደረገ ነው ላሉት በኤርትራ ያለው መንግሥት ለመታገል በምናደርገው ጥረት የአካባቢው ሃገራትና የኤርትራ ሕዝብ እንዲሁም ዓለም አቀፍ ድርጅቶችና መንግሥታት ከጎናቸው እንዲቆሙ አቶ ያሲን ጥሪ ማቅረባቸውን ዘገባው አስታውቋል

