አንዳንድ ሰዎች የሳቱት ነገር፤ ጠንካራ ዲፕሎማሲም ሠራህ አልሠራህ “ግብጽ” የምትባል ሀገር ለኢትዮጵያ ውጋት ከመሆን አትታገድም። .. ከድሮ ጀምሮ የመካከለኛው ምስራቅ ዋነኛ “አቃጣሪ፣ አስጠቂና በወገኖቿ ደም የምትነግድ” ተላላኪ ሀገር በመሆኗም ከአሜሪካ እስከ አውሮጳ ኅብረት ያሉ ሀገራትን በር እያንኳኳህ ‘አቤቱታ ብታሰማ፣ ብትሰብክ፣ ደጅ ብትጠና የሚሰማህ አይኖርም።
ከጥንት ጀምሮ በሁሉም የሀገራችን አቅጣጫዎች በተለይ በምሥራቅና በሰሜን በኩል ኢትዮጵያን ወርራ እንደነበር ይታወቃል። ሐረርን ይዛም ቆይታ ነበር።
“በሰሜን በኩል የኢትዮጵያን ግዛት ለመውረር የመጣው የግብጽ ጦር በ1866 ዓ.ም. በኅዳር ወር ‘ጉንደት’ ላይ፤ .. እንዲሁም በ1868 ዓ.ም. በየካቲት ወር ‘ጉራዕ’ ላይ ‘ያልሰለጠነ መንጋ ወታደር ነው’ ብሎ በናቀው በአጼ ዮሐንስ እና በራስ አሉላ አባ ነጋ በሚመራው የኢትዮጵያ ጦር ድል ተመትቶ መመለሱ” ታሪክ የመዘገበው ነው።
በ1969 ዓ.ም. በተስፋፊው የዚያድ ባሬ ጦር ኢትዮጵያ ስትወረርም የግብጽ ድጋፍ ገሃዳዊ ነበር።
ሰፍኖ የነበረው የውስጥ ፖለቲካዊና አስተዳደራዊ መበስበስና ጭቆና ያደረገው አስተዋጽኦ እንዳለ ሆኖ ከጀብሃ እስከ ሻዕቢያ ያሉትን ታጣቂዎች በፕሮፓጋንዳ፣ በትጥቅና በሎጀስቲክስ በማገዝ የዛሬይቱ ወደብ-አልባ ሀገር እንድትፈጠር አድርገዋል።
በ1990ዎቹ ዓ.ም. መጀመሪያ ላይ ተፈጥሮ በነበረው የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ላይ ከተማረኩት የጦር መሣሪያዎች መካከል ግብጽ-ሠራሽ ጸረ-ተሽከርካሪና ጸረ-ሰው ፈንጂዎች ይበዙ ነበር። ይህም በጦርነቱ ላይ የነበራትን ሚና አመላክቷል።
በየዘመናቱ ሁሉ (የመንግሥታቱ ኢ-ዲሞክራሲያዊነትና አምባገነንነት አስተዋጽኦ ማድረጉ እንዳለ ሆኖ) በሀገራችን በተፈጠሩ ግጭቶች ውስጥ የግብጽ እጅ የሌለበት የለም ብሎ አፍ ሞልቶ መናገር ይቻላል።
የቀይ ባህርና የዓባይ ጉዳይ እንቅልፍ የሚነሳት እና በፍትሐዊነትና በጋራ መጠቀምን እንደሞት የምትቆጥረው ግብጽ፣ .. ከአዲስ አበባ እስከ ካይሮ የአልማዝ ምንጣፍ ቢነጠፍላት ወዳጅ እንደማትሆንና ኢትዮጵያን ሰላም ከመንሳትም ወደ ኋላ እንደማትል የታወቀ ነው። ተላላኪያቸው ናትና ምዕራባውያን ሀገራትም “ታገጅ” ሊሏት አይሹም። ስለዚህም ሺህ ጊዜ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ቢደረግም ለውጥ ይኖረዋል ብዬ አላምንም።
ያለው ብቸኛ መፍትሔ የበረታች ኢትዮጵያን .. በተለይ በፖለቲካው፣ በኢኮኖሚው እና በወታደራዊው ረገድ መፍጠር ነው የሚያስፈልገው።
በመሆኑም በሰሞነኛው ጭቅጭቅ “ብልጽግና”ን መቃወምንና የሀገርን ጥቅም ያልለዩ ቡድኖች “አውቀው በድፍረት፣ ሳያውቁ በስህተት” እየተንደረደሩበት ካለው አጥፊ መንገድ ቢመለሱ ጥሩ ነው እላለሁ። ሀገራችን ላይ ማንኛውም ጥቃት መሰንዘር አይደለም ቢታሰብ ከመንግሥት ጎን ሆኖ ይህቺን ከዘመን ዘመን ጠላትነቷ ያልተገታን ሀገር ለመፋለም መቁረጥ ያስፈልጋል!
by Jemil Yirga

