ጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ ከተቀጠሩ ከ5 ዓመት በላይ የሆናቸው እና የ2ኛ ዲግሪ የሌላቸው ከ300 በላይ መምህራኑን በ2017 ዓ.ም. የትምህርት ዘመን ምንም አይነት ኮርስ እንዳይሰጡ ውሳኔ ማሳለፉን አስታውቋል።
ዩኒቨርስቲው በመምህራኑ ላይ ወርሃዊ ደመወዝ እንዳይከፈላቸው እግድ አስተላልፎ የነበረ ቢሆንም ይህንን ውሳኔውን ለጊዜው መቀልበሱን ገልጿል።
” ይህ ውሳኔ ላይ የተደረሰው የመጀመሪያ ዲግሪ ኖሯቸው የተቀጠሩ መምህራን ፤ የድህረ ምረቃ ትምህርታቸውን እንዲቀጥሉ ዩኒቨርሲቲው ያስተላለፋቸውን ተደጋጋሚ ጥሪዎች ተቀብለው ወደ 2ኛ ዲግሪ ትምህርት ባለመግባታቸው ነው ” ሲል ዩኒቨርሲቲው አመልክቷል።
የጅግጅጋ ዩኒቨርሰቲው አካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር አብዲ አህመድ ምን አሉ ?
ጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ ከ1,400 መምህራን በላይ እንዳሉት ፤ ከእነዚህ ውስጥ 800 ገደማው የሁለተኛ ዲግሪ እንዳላቸው ጠቁመዋል።
ከአጠቃላይ መምህራን ውስጥ 350 ያህሉ የመጀመሪያ ዲግሪ ብቻ ያላቸው ናቸው ብለዋል።
የመጀመሪያ ዲግሪ ካላቸው መምህራን ውስጥ በትምህርት ላይ ያሉት ” የተወሰኑት ” እንደሆኑም ገልጸዋል።
ዩኒቨርሲቲው ከ4 ዓመት በፊት ባደረገው እንቅስቃሴ ከተቀጠሩ 5 እና ከ5 ዓመት በላይ የሆናቸው አብዛኞቹ መምህራን በ2 ዓመት ውስጥ 2ኛ ዲግሪ እንዲይዙ አድርጎ እንደነበር አስታውሰዋል።
ከዚያን ጊዜ ጀምረው 2ኛ ዲግሪ ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ እና እየተከታተሉ ያሉ መምህራን እንዳሉ የገለጹት ም/ ፕሬዝዳንቱ፤ ” አንዳንዶች ለመማር ፈቃደኛ ያልሆኑ ግን እዚያው በዩኒቨርሲቲው ውስጥ የቀጠሉ ናቸው ” ብለዋል።
መምህራኑ የድኅረ ምረቃ ትምህርት ላለመቀጠላቸው የተለያዩ ምክንያቶች ሊኖሩ እንደሚችሉ አንስተው ” አንዳንድ መምህራን ሌላ ተደራቢ ሥራ አግኝተው መምህርነቱን እንደ ሁለተኛ ሥራ መመልከታቸው አንዱ ምክንያት ” ነው ብለዋል።
ዩኒቨርሲቲው እነዚህ መምህራን የድኅረ ምረቃ ትምህርት ያልጀመሩበትን ምክንያት በተመለከተ በተደጋጋሚ ስብሰባዎችን ቢጠራም ” ሳይሳተፉ ቀርተዋል ” ሲሉ ተናግረዋል።
” 2017 ዓ.ም. ሊጀመር ሲል አንደኛ ዲግሪ ያላቸውን መምህራን ብቻ ስብሰባ ጠርተን ነበር። መጀመሪያ ላይ የመጡልን 11 መምህራን ብቻ ናቸው። ሁለተኛ ዕድል እንስጥ ብለን የዛሬ ሳምንት ስብሰባ ጠርተን ነበር። ከ300 በላይ መምህራን ውስጥ 48 መምህራን ነው የመጡት ” ሲሉ ወቅሰዋል።
በዚህም መምህራኑ 2ኛ ዲግሪ ባለመያዛቸውና እና የዩኒቨርሰቲው አመራር በጠራቸው ስብሰባዎች ላይ አለመካፈላቸውን ተከትሎ እየተጀመረ ባለው የ2017 ትምህርት ዘመን ” ምንም ዓይነት ኮርስ እንዳይሰጡ ” ውሳኔ መተላለፉን አስታውቀዋል።
” እነዚህ መምህራን መማርም ስለማይፈልጉ፤ በአንደኛ ዲግሪ ያለ መምህር አንድም ኮርስ እንዳይሰጥ ወስነናል። ” ሲሉ ተናግረዋል።
መምህራኑ ከተላለፈባቸው የማስተማር እገዳ በተጨማሪ ደመወዝም እንዳይከፈላቸው ውሳኔ ተላልፎ እንደነበር ዶ/ር አብዲ ተናግረዋል።
ይሁንና ውሳኔው በተላለፈበት በአሁኑ ወቅት የመስከረም የደመወዝ መክፈያ ጊዜ በመድረሱ እና ” በዚህ ጊዜ ደመወዝ ማቋረጥ ስለማይቻል ” ዩኒቨርሲቲው ይህንን ውሳኔውን ለጊዜው መሻሩን ዶ/ር አብዲ አስታውቀዋል።
መረጃው የቢቢሲ አማርኛው አገልግሎት ነው።

