ከጥቂት ወራት በፊት በሞት የተለየን አስማማው ቀለሙ ወይም በቅፅል ስሙ “ፔድሮ” የኢትዮጵያ የመረጃ እና የደህንነት ሊቅ (guru) ቢባል አይበዛበትም። በቀለም ትምህርት እስከ PhD፣ በወቅቱ በነበረው ፖሊሳዊ ማዕረግ እስከ ሻምበልነት፣ በደህንነት አገልግሎት እስከ ምክትል ኃላፊነት፣ እንዲሁም በውጪ ጉዳይ አገልግሎት እስከ አምባሳደርነት የደረሰ ሁሉ-ገብ civil servant ነበር። በአጭሩ ለሃገሩ እና ለሙያው ካለው ፍቅር የተነሳ እንደ ግለሰብም እንደ ባለሙያም አሳክቶ ያለፈው ነገር በርካታ ነው። ለዛሬ ከወቅታዊው ሃገራዊ እና ቀጠናዊ ሁኔታ አንፃር አስማማው ቀለሙ ከባዱን “የሶማሊያን ፋይል” ከ1970ዎቹ እስከ ደርግ ውድቀት እንዴት በብቃት እና በልዕቀት እንደያዘው እንዘክራለን።
አስማማው በ70ዎቹ መጀመሪያ የPhD ትምህርቱን ከአውሮፓ ጨርሶ ሲመለስ የኢትዮ-ሶማሊያ ጦርነት በኢትዮጵያ አሸናፊነት ተጠናቅቆ ነበር። ሆኖም ግን ሁለት ወሳኝ ጉዳዮች መንግስትን እና የደህንነት መስሪያ ቤቱን ፋታ ነስተው ነበር፦ (1) በሶማሊያ እጅ የወደቁ በሺዎች የሚቆጠሩ የሲቪል እና ወታደራዊ የጦር እስረኞች (POWs) እና (2) በሶማሊያ ድጋፍ የሚደረግላቸው የኢትዮጵያ አማፅያን (WSLF፣ ኦነግ፣ ሻዕቢያ፣ ህወሐት እና ሶማሊ አቦ ግንባር) ጉዳይ። ይህንን አጥንቶ ከነመፍትሄ ሃሳቦቹ የማቅረብ ኃላፊነት የወደቀው ደግሞ በአስማማው ትከሻ ላይ ነበር። እሱም ጥናቱን ከነመፍትሄው በ200 ገፆች ላይ አስፍሮ አቀረበ። ከበርካታ አማራጭ መፍትሄዎች መሐልም ሁለቱ ተመረጡ፦ (1) በስውር ስምሪት (covert operation) የጦር እስረኞቹን ሁኔታ እና ቁጥር የሚገልፅ መረጃ ከሶማሊያ መሰብሰብ እና (2) ለተመረጡ ግን ጠንካራ ለሆኑ የሶማሊያ አማፅያን ድጋፍ በማድረግ በሶማሊያ ላይ ጫና ማድረግ። ከሁለቱ ከባዱ ችግር ደግሞ “በስውር ስምሪቱ የሚላከው ማን ይሁን?” የሚለው ነበር። ከብዙ ክርክር በኋላ የወቅቱ ፕሬዚደንት መንግስቱ ኃይለማሪም “የሃሳቡ ጠንሳሽ አንተው ነህና ራስህ ተወጣው” ሲሉ ወሰኑ። በintelligence ሙያ ቀድሞ በሞሳድ በኋላም በምስራቅ ጀርመኑ ስታሲ እና በሶቭየት ህብረቱ ኬጂቢ ስልጠና የወሰደው አስማማውም “አሳይንመንቱን” ሳያንገራግር ተረከበ።
ከወራት ዝግጅ በኋላ አስማማው ሞዛምቢካዊ ጋዜጠኛ ሆኖ፤ ስሙም “ፔድሮ” ተብሎ ከደቡባዊ አፍሪካዊቷ የኢትዮጵያ ወዳጅ ሃገር ሞዛምቢክ ወደ ሶማሊያ ተጓዘ። የሶማሊያ መንግስትን አመኔታ ለማግኘትም ሶማሊያን እና ዚያድ ባሬን የሚያወዳድሱ ዘገባዎችን እየሰራ ወደ ሞዛምቢክ መላክ ጀመረ። በተወሰኑ ወራት ውስጥም በሶማሊያ እጅ የሚገኙች ኢትዮጵያውያን የጦር እስረኞች ቁጥር ስንት እንደሆነ እና በየትኞቹ የሶማሊያ እስር ቤቶች እንደሚገኙ ዝርዝር መረጃ ካዘጋጀ በኋላ ሶማሊያን ለቅቆ ወጣ። በኋላ ላይ የጦር እስረኞች ልውውጥ ለማድረግ ድርድር ሲደረግ የኢትዮጵያ መንግስት ድርድሩን ያደረገው በዚህ መረጃ ላይ ተመስርቶ ነበር።
ሁለተኛው የአስማማው ተልዕኮ ሶማሊያ ለኢትዮጵያ አማፅያን ድጋፍ በማድረግ በኢትዮጵያ ላይ ለምትፈፅመው ማናጋት (destabilization) እና የውክልና ጦርነት (proxy war) አፀፋ፤ የሶማሊያ አማፅያን መርጦ እና አሰልጥኖ ማሰማራት ነበር። በዚህም መሰረት የዛሬዋን ሶማሊላንድ ገዢ ፓርቲ SNM (Somali National Movement) መሪዎች ከአውሮፓ ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጡ እና እንዲደራጁ፤ በሰሜን ሶማሊያ ወታደራዊ እንቅስቃሴ እንዲያደርጉ ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል። ከዚህ በተጨማሪም በ1969ኙ ጦርነት ወቅት ተማርኮ ከርቸሌ የነበረውን ኮ/ል አብዱላሂ የሱፍን በማደራጀት እና በማስታጠቅ በደቡባዊ ሶማሊያ ወታደራዊ እንቅስቃሴ እንዲያደርግ አመቻትቷል። በዚህም ሶማሊያ በኢትዮጵያ ላይ የምታካሂደውን የውክልና ጦርነት ሳትወድ በግድ ከማስቆም አልፎ ሁለቱ ሀገራት በ1980 “በጠላትነት ያለመፈላለግ ስምምነት” እንዲፈራረሙ ዕድል ፈጥሯል።
በመጨረሻም አስማማው ቀለሙ (ፔድሮ) የዚያድ ባሬ መንግስት እስከ ወደቀበት እና ሶማሊያ በግላጭ መፈረካከስ እስከጀመረችበት ጥር 1983 ድረስ በሶማሊያ የኢትዮጵያ አምባሳደር በመሆን አገልግሏል። በዚህም የኢትዮጵያን ዘላቂ ብሄራዊ ጥቅም እና ደህንነት የሚያስጠብቁ በርካታ ስራዎችን ሰርቷል። ሶማሊያ ፈራርሳ፤ ሶማሊላንድ “ከአሁን ወዲያ ነፃ ሃገር ነኝ” ብላ ስታውጅም፤ አስማማው “የሶማሊያን ፋይል” ለውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር እና ለህዝብ ደህንነት ሚኒስቴር ያስረከበው “ከዚህ በኋላ ሶማሊያ በኢትዮጵያ ላይ ቀጥተኛ ወታደራዊ ስጋት አትሆንም። ይህን አላማችንን በሚገባ ተወጥተናል” በማለት ነበር። እንዳለውም ከሶስት አስርት አመታት በኋላም ሶማሊያ እንደ ሀገር በኢትዮጵያ ላይ ብሄራዊ ደህንነት እና ጥቅም ላይ ቀጥተኛ ወታደራዊ ስጋት/አደጋ የምትደቅንበት ሁኔታ አልተፈጠረም። እንደ አል ኢትሃድ (በ1980ዎቹ) እና አል ሻባብ (ከ1990ዎቹ መጨረሻ ጀምሮ) ከሞካከሩት የሽብር ጥቃት በቀር።
እና ምን ለማለት ነው?!
1ኛ) ገና ለገና ከሶማሊያ ጋር ጦርነት ይጀመራል ብላችሁ የቋመጣችሁም ሆነ፤ የምታሟርቱ ቀቢፀ-ተስፈኞች ዕርማችሁን አውጡ። በሆነ ተአምር የዚያድ ባሬዋ ሶማሊያ resurrect ካላደረገች በስተቀር በሶማሊያ እና በኢትዮጵያ መሐከል ቀጥተኛ ጦርነት አይኖርም። ይህ እንዳይሆን ከ83 በፊት በአስማማው (ፔድሮ)፤ ከ1999 በኋላም በኮ/ል ገብሬ ዲላ (ስለ ኮ/ል ገብሬ ወደ ፊት እንጨዋወታለን) በቂ ስራ ተሰርቷል።
2ኛ) ግብፅን በተመለከተ፦ በሰሜን ምዕራብ ኢትዮጵያ (በሱዳን) በኩል ማድረግ ያልቻለችውን ነገር እያወቁ፤ “ግብፅ በሶማሊያ በኩል በኢትዮጵያ ላይ ጦርነት ስትከፍት እኛ መንግስትን ከውስጥ እንንደዋለን” ብለው የቋመጡ ቀቢፀ-ተስፈኞች ያዝናኑኛል። ያሳዝኑኛል። ኢትዮጵያ እና ግብፅ በምስራቅ በኩል ቀጥተኛ (የፊት ለፊት) ውጊያ ያደርጋሉ ብሎ ለማመን እጅግ ሲበዛ መደደብ እና የኢትዮጵያ እና የግብፅን መንግስታትም በተራ የሰፈር አማፂ ልክ (ማለትም እንደ “ሸኔ” ወይም “ፋኖ” አሳንሶ እና አውርዶ ማየት ይጠይቃል። ስለዚህ ምን አስግቶን ነው አጥሮቻችንሰ የምናጠባብቀው?! መልሱ ቀላል ነው! ግብፅ (በሶማሊያ በኩል) እና የኢትዮጵያን ውስጣዊ ችግር ተጠቅማ የውክልና ጦርነቶችን እና ቀጠናዊ መናጋቶችን ለማባባስ መትጋቷ አይቀሬ ነው። በኢትዮጵያም በኩል ለተመሳሳይ አፀፋ በቂ ዝግጅት እየተደረገ ነው። ተደርጓልም።
3ኛ) የውክልና ጦርነቱን ኢትዮጵያም ውስጥ ሆነ ሶማሊያ ውስጥ ለማካሄድ የተዘጋጁትን እንደ አመጣጣቸው ለማስተናገድ፤ ኢትዮጵያ ከቅድመ-83ቱ በተሻለ ነገ እንደ አስማማው ቀለሙ ሁሉ የምንዘክራቸው በርካታ “ፔድሮዎች” እና “የሶማሊያ ፋይል” handlers አሏት።
ማሳረጊያ፦ ከግብፅም ሆነ ከሶማሊያ ጋር ቀጥተኛ ጦርነት አይኖርም። በኢትዮጵያ ላይ ለሚከፈተው የውክልና ጦርነት ራሳቸውን በእጩነት ለግብፅ/ሶማሊያ ያቀረቡትንም ሆነ፤ በግብፅ የታጩትን እንደ አመጣጣቸው ለማስተናገድ በቂ አቅም እና ዝግጁነት አለ።
ጦርነት አንፈልግም። ሰልችቶናል። ስለዚህ ሁሌም ለሰላም ዕድል መስጠት አለብን። ይህን እንደ ድክመት አይተው ጦርነትን በላያችን ላይ ሊጭኑብን ከመጡ ግን፤ ከነተላላኪዎቻቸው ወደ መቀመቅ እንልካቸዋለን!
Oluma M. Wodajo
ብሄራዊ ጥቅም መሰረታችን!! "Reporting with Integrity: National Interest Above All."

