ሀገራችን ወደብ አልባ መሆኗ ከከነከናቸው ቀዳሚዎች መካከል አንዱ ናቸው።
ጦር ሰብቀን ወደብ እናግኝ ግን አላሉም። በጊዜው የነበረው መንግሥት አልባሌ ሥም እየለጠፈ ቢያሸማቅቃቸውም ካፓርቲያቸው ጋር ሆነው 150 ሺህ ፊርማ አሰባስበዋል።
እኝህ ሰው ፕሮፌሰር አድማሱ ገበየሁ ይባላሉ። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አሁንም እያገለገሉ ይገኛሉ።
ሕወሓት ኤርትራ ስትገነጠል በአሰብ ጉዳይ መደራደር ይችል ነበር ይላሉ ፕሮፌሰር አድማሱ በቁጭት።
በጊዜው ኤርትራ አጥብቃ የኔ ነው የምትለው ነገር እንዳልነበራት አንስተው፤ ኢትዮጵያም ወደ ኋላ የምታፈገፍግበት ምክንያት አልነበራትም በማለት ይገልጻሉ።
ጉዳዩን የተለያዩ ኮንፍረንሶችን አዘጋጅቶ ታሪካዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ሁኔታውን ሚዛን ውስጥ አስገብቶ መከራከር ይቻል ነበር ሲሉም ነው የሚያስረዱት።
እስከ 1997 ዓ.ም ድረስ የፖለቲካ ፓርቲ መሪ ነበርኩ ያሉት ፕሮፌሰር አድማሱ፤ በወቅቱ ፓርቲያቸው ኢዲአፓ መድኅን እንደነበርና አንዱ አጀንዳው የአሰብ ጉዳይ እንደነበር ይገልጻሉ።
የወደብ ጉዳይ ተሸፋፍኖ ኢትዮጵያ ወደብ እንድታጣ የተደረገበትና በታሪኳ በር ተዘግቶባት እንድትቀር ያደረገ ሁኔታ መሆኑን ጠቅሰው፤ የአሰብን ጉዳይ በጉልበት ሳይሆን በዲፕሎማሲያዊ መንገድ ለመፍታት መሞከራቸውን ያነሳሉ።
በመነጋገርና በመወያየት እልባት ሊገኝለት ይችላል የሚል እምነት ስላደረብን ፖለቲካዊ አጀንዳ አድርገን መስቀል አደባባይ ሁለት ጊዜ ሕዝባዊ ሰልፍ አካሂደናል በማለት ይናገራሉ።
ከ150 ሺህ በላይ የተረጋገጠ አድራሻ ያላቸውን ሰዎች ፊርማ ማሰባሰባቸውን እና የሰነዱን ቅጂዎች ለአፍሪካ ኅብረት እና ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ማስረከባቸውንም ነው የሚያስረዱት።
አሁን በኤርትራ የሚገኙ ወደቦችን የመጠቀም ዕድልን በተመለከተም ሲገልጹ፤ አሰብንም ሆነ ምፅዋን ወደብን ለመጠቀም የሚፈልግ ሌላ ጎረቤት ሀገር የላቸውም።
ወደቡን በመጠቀም እድገታቸውን ለማፋጠን ባለመምረጥ ምክንያታዊ ያልሆነ አቋም መያዛቸው ይገርመኛል ይላሉ።
ኢትዮጵያ በተለያዩ ትርፋማ የልማት ድርጅቶቿ ውስጥ ድርሻ እንዲኖራቸው በማድረግ ጭምር በሰጥቶ መቀበል መርሕ በጋራ ተጠቃሚ እንሁን የሚል ጥያቄ እያቀረበች ነው ሲሉም ገልጸዋል።
የኤርትራ መንግሥት ይህን ዕድል ገፍቶ ከግብፅም ሆነ ከሌሎች ወገኖች ጋር ከወገነ በአንደኛ ደረጃ እየበደለ ያለው የራሱን ሕዝብ መሆኑን ጠቅሰዋል።
ታሪካችንን ከተመለከትን ተለያይተን የኖርነው ትንሽ ጊዜ ነው ያሉት ፕሮፌሰሩ፤ አንድ ሀገር ሆነን መቀጠል ባንችልም እንኳን እንደ ጎረቤት ሀገር ከየትኛውም ጎረቤት ሀገር በላይ ለእኛ የሚቀርቡ ናቸው ብለዋል።
የኢትዮጵያን ጥቅም በተመለከተ አብረን መቆም አለብን ሲሉም መክረዋል።
ጋዜጣ_ፕላስ

