አዲሱ ትውልድ አባቶቹ በአርበኝነት ተጋድሎ በመሥዋዕትነት ያጎናጸፉትን ነጻነት ተጠቅሞ የሃሳብ፣ የቴክኖሎጂና የኢኮኖሚ አርበኛ መሆን ይኖርበታል ሲሉ የጥንታዊት ጀግኞች ኢትዮጵያ አርበኞች ማህበር ፕሬዚዳንት ገለጹ።
የጥንታዊት ጀግኖች ኢትዮጵያ አርበኞች ማህበር ፕሬዚዳንት ልጅ ዳንኤል ጆቴ የካቲት 12 የሚከበረውን የሰማዕታት ቀን ምክንያት በማድረግ ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እንደገለጹት፤ ፋሺስት ወራሪ ኃይል በዓድዋ ጦርነት የደረሰበትን ሽንፈት ለመበቀልና ኢትዮጵያን በቅኝ ግዛት ስር ለማድረግ ዳግም የወረራ ሙከራ አድርጓል። የካቲት 12 አብርሃ ደቦጭና ሞገስ አስገዶም በግራዚያኒ ላይ የፈጸሙትን የቦንብ ጥቃት ተከትሎ በርካታ የበአዲስ አበባ ከተማ ንጹኋንን ጨፍጭፏል። ያም ሆኖ አርበኞች በፈጸሙት የአምስት ዓመት ተጋድሎ ፋሽሽቶች ተሸንፈው ወጥተዋል። ኢትዮጵያም ዳግም ነጻነቷን አረጋግጣለች።
አዲሱ ትውልድ በአርበኞች ተጋድሎ ያገኘውን ነጻነት ሀገሩን ለማሳደግ ሊጠቀምበት ይገባል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ ነጻነቱን በጉያው ይዞ የሃሳብ ፣ የቴክኖሎጂና የኢኮኖሚ አርበኛ መሆን ይገባዋል ሲሉ ተናግረዋል።
ወጣቱ ትውልድ ትናንት የነበረውን ታሪኩን ማወቅ አለበት፤ አባቶቹ ዋጋ የከፈሉለት ለምን እንደሆነም መረዳት አለበት ፤ ዛሬ ያለው ሁኔታ ምን እንደሆነና ወደፊትም ምን ሊሆን እንደሚችል ወጣቱ መገንዘብ ይኖርበታል ነው ያሉት።
አዲሱ ትውልድ ሀገርን ወደፊት ሊያራምድ በሚችል ነገር ላይ በማተኮር ራሱ ማብቃት ፤ ቀጥሎም ወገኑ እና ሀገሩ ማብቃት ላይ ትኩረት ማድረግ ያስፈልገዋል ብለዋል።
አዲሱ ትውልድ እንደ አባቶቹ ሁሉ ለሀገሩን ክብር እና ለሕዝቡ ጥቅም ቅድሚያ የሚሰጥ መሆን እንዳለበት አስገንዝበው፤ ሀገሩን የሚጎዳ እና ጎረቤቱን የሚበድል መሆን እንደሌለበት አጽንኦት ሰጥተዋል።
ወጣቱ ድህነቱን ተጠቅመው ሌሎች ኃይሎች ለሌላ እኩይ ዓላማ እንዳይጠቀሙበት ራሱን በኢኮኖሚ ማሳደግ እንደሚኖርበት አመልክተው፤ ባለንበት ዘመን አንዳንድ ወጣቶች ቻይና ሄደው፤ ቋንቋ ተምረው በንግድ ሥራ ላይ ተሠማርተዋል። ትውልዱ ኢኮኖሚውን ለማሳደግ ከዚህም በላይ መሥራት እንዳለበት ተናግረዋል።
ኢኮኖሚ ብቻ ሳይሆን አስተሳሰብንም ድህነት እንዳያጠቃው ማስተዋል ይኖርበታል ያሉት ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ የሚያነብ ፣ የሚሠራ ፣ የሚመራመርና የሚያስብ ትውልድ ሲፈጠር ሀገር ይጸናል እንጂ አይፈርስም ነው ያሉት።
መጪው ዘመን የቴክኖሎጂ እንደሆነ የተናገሩት ፕሬዚዳንቱ፤ ወጣቱ የሚሠራውን ሥራ ሁሉ ከሳይንስ ጋር እያጣጣመ በመጓዝ የአዳዲስ እውቀትና ፈጠራ ባለቤት በመሆን የቴክኖሎጂ አርበኛ መሆን ይጠበቅበታል ብለዋል።
መንግሥት ለዘርፉ በሚሰጠው ትኩረትም ይሁን በራሱ ጥረት ወጣቱ በቴክኖሎጂ ለውጥ ለማምጣት መጣር እንዳለበት አመልክተው፤ የዓለምን መረጃ በሙሉ እጃችን ላይ ባለው ተንቀሳቃሽ ስልክ ማግኘት እንደሚቻል ጠቁመዋል።
ፕሬዚዳንቱ፤ ኢትዮጵያ ከዓለም ሥልጣኔ ጋር እንደትራመድ ወጣቱ የቴክኖሎጂ አርበኛ በመሆን እንደ አባቶቹ የኢትዮጵያን ክብር መጠበቅ አለበት ሲሉ ተናግረዋል።
አባቶቻችን ዘመናቸውን መስለው ሀገራቸውን እንዳኮሩ ሁሉ አዲሱ ትውልድም ዘመኑ በሚፈልገው ቴክኖሎጂ ታሪክ በመሥራት ለሀገሩ ኩራት መሆን እንዳለበት አስገንዝበዋል።
ወጣቶች በሌሎች አስተሳሰብ እንዳይጠለፉ በራሳቸው አረዳድ በጥልቀት አስበው ውሳኔ ላይ መድረስን ማዳበር ይኖርባቸዋል። የነገሮችን ትክክለኛነት መረዳት ያለባቸው በራሳቸው ግንዛቤ እንጂ በሰዎች ጫና መሆን እንደሌለበትም አስረድተዋል።
አለመግባባትን የሚፈጥርና ልዩነትን የሚያሰፋ ጥሩ ያልሆነ ሃሳብ ለውጭ ጠላቶች በር የሚከፍት እንደሆነ ጠቅሰው፤ ከሰሞኑ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት መዳፈር የፈለጉ ሀገራትን ማየታችን የዚህ አንዱ ማሳያ ነው ብለዋል።
ወጣቶች የመጥፎ ሃሳብ ተገዢ ከመሆናቸው በፊት ከስሜት ወጥተው ቆም ብለው ማሰብ ያስፈልጋቸዋል። ወጣቱ በመነጋገር ፣ በመወያየት፣ በመግባባት፣ በመከባበር መቶ በመቶ እንኳን ባይሆን ቢያንስ 90 በመቶ የውስጥ ችግሩን ፈትቶ የሀገሪቱን እድገት ማስቀጠል እንደሚገባው አሳስበዋል።
አዲሱ ትውልድ የትናንት ታሪኩን በደንብ አውቆ መጥፎውን በመተው ፤ መልካሙን ወስዶ የኢትዮጵያን የዕድገትና የሥልጣኔ ጉዞ እንዲያስቀጥል የጥንታዊ አርበኞች ማህበር ፕሬዚዳንት ልጅ ዳንኤል ጆቴ መልዕክት አስተላልፈዋል።
ኢያሱ መሰለ አዲስ ዘመን

