የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር መላኩ ወልደ ማርያም በአማራ ክልል ያለውን ጦርነት በተመለከተ፣ “ በጣም የሚያሳዝነው ነገር በሁለቱም ወገን የሚፈሰው ደም የኢትዮጵያዊያን ደም ነው ” ሲሉ ተናገሩ።
የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ተፎካካሪ ፓርቲዎችንና የታጠቁ ኃይሎችን በማሳተፍ ረገድ ትችት ይሰነዘርበታል፤ የኮከስና ሌሎች ፓርቲዎች እንደሚሉት ደግሞ፣ ከኮሚሽኑ ራሳቸውን ያገለሉት “ ቅድሚያ ተኩስ አቁም ይታዘዝ ” በማለት ነው።
ኮሚሽኑ የሦስት ዓመት ሪፓርቱን ፓርላማ ባቀረበበት ወቅት ስለጉዳዩ ለቀረበለት ጥያቄ፣ “ጫካ ያሉ ሰዎች አጀንዳ አልመጣም” ብሎ እንደማያስብ መመለሱ ይታወሳል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያም፣ አጀንዳ የማሰባሰብ ሂደቱ በኦሮሚያ ክልል ተጠናቋል፤ በአማራ ክልልም ትንሽ እንደቀራችሁ ገልጻችኋል፤ የታጣቂዎች ጥያቄዎችን የያዙ አጀንዳዎች ወደ ኮሚሽኑ መጥተዋል ማለት ይቻላል እንዴ ? ሲል ለኮሚሽኑ ጥያቄ አቅርቧል።
የኮሚሽኑ ኮሚሽነር መላኩ ወልደ ማርያም በምላሻቸው፣ “ በተለያዩ ተሳታፊዎች አማካኝነት ቀርቦ ሊሆን ይችላል ለማለት ነው። መጥቷል አልመጣም የሚለውን የምናውቀው ከእነርሱ አንደበት ስንሰማ ነው። ‘አጀንዳችን ቀርቧል’ ብለው ሲናገሩ ነው፤ ያንን ባልሰማንበት ሁኔታ አጀንዳቸው ቀርቧል ማለት አንችልም ” ብለዋል።
“ አጀንዳቸውን የማቅረብ መብት እንዳላቸው በተደጋጋሚ ገልጸናል። አጀንዳቸውን የግድ እዚህ አቀርቡት አላልንም፤ ውጪ አገርም ቢሆን ያቅርቡት” ሲሉ አክለዋል።
ተፎካካሪ ፓርቲዎች ባገለሉበት ሁኔታም ኮሚሽኑ ሥራውን እየሰራ ነው፤ ለመሆኑ ፓርቲዎች ባገለሉበት ሁኔታ ምክክሩ ውጤታማ ይሆናል ? “ ቅድሚያ የተኩስ አቁም ይታዘዝ ” ለሚለው ሀሳባቸውስ ቀርባችሁ አነጋግራችኋቸው ነበር ? የሚል ጥያቄም ለኮሚሽኑ አቅርበናል።
ኮሚሽነር መላኩ ወልደ ማርያም ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ምን መለሱ ?
“ ‘ ጦርነት ይቀጥል ‘ የሚል ሰው የለም በመሰረቱ ጤናማ ከሆነ። ጦርነት መቀጠል፤ የሰው ሕይወት መጥፋት፤ ንብረት መውደም፤ ሰዎች አካላቸው መጉደል አለበት የሚልን ሰው ጤንነቱን እጠራጠራለሁ።
እንደ ኮሚሽን ጦርነት እንዲቆም እየጠየቅን ነው፤ ሁሉንም የሚመለከታቸውን ወገኖች። በጦርነትና በግጭት ያሉ ወገኖች ሁሉ ‘አሉን’ የሚሏቸውን ጉዳዮች አምጥተው በምክክር ችግሮች እንዲፈቱ ጥሪ እያደረግን ነው።
የስልጣን ጥያቄ ያላቸው ወገኖች ካሉ ይደራደሩ፤ መመካከር አይደለም ይደራደደሩ። ‘በምክክር ሀገር ትጸናለች’ የሚለው ወገን ደግሞ ይመካከር። ትልቁ ጥያቄ የሥልጣን ጥያቄ ነው። ስልጣን ደግሞ የህዝብ ነው።
በደል አለ። ይሄ ዛሬ የተጀመረ ነገር አይደለም የቆየ ነው። ለምሳሌ በአማራ ክልል በርከት ላሉ አመታት ከፍተኛ ችግር ሲንከባለል እንደመጣ ይታወቃል። አማራ ክልል ያለው አርሶ አደር ይናገራል፤ አይፈራም።
በጣም የሚያሳዝነው ነገር በሁለቱም ወገን የሚፈሰው ደምኮ የኢትዮጵያዊያን ደም ነው። ለምን? ችግር ካለ መፍትሄ አለ። ስለዚህ ግላዊ ነው ማለት ነው፤ መንስኤ ሌላ ነው ማለት ነው። የእውነት ምክንያቱ የህዝብ ጥያቄ ከሆነ ማስተናገድ የማይቻልበት ምክንያት አይኖርም።
የፓለቲካ ፓርቲዎችንም አነጋግረናል በተለያዬ ጊዜ። ለዚች ሀገር የሚያዋጣ ከምክክር የተሻለ ሀሳብ ካለ ንገሩን፣ እኛንም አሳምኑን፣ ከእናንተ ጋር እንቁም ነውኮ ያልናቸው። የተሻለ ሀሳብ ከሌላችሁ ግን እውነቱን ተናገሩ። ‘የግል ፍላጎት አለን’ በሉ። የግል ፍላጎት ከሆነ የግል ፍላጎት ነው መንጸባረቅ ያለበት።
ገና ለገና መንግስት አይፈጽመውም ተብሎ?፣ እሱኮ በሂደት የሚታይ ነገር ነው። የኢትዮጵያ ህዝብ መንግስት እንዲፈጽመው ማድረግ ይችላል። ‘ድምፄን አክብርልኝ’ ‘የተስማማሁበትን ነገር መሬት ላይ አውርድልኝ’ ማለት ይችላል” ብለዋል።
በሌላ በኩል፣ የኦሮሚያ ክልል አጀንዳ ከሌሎች ተለይቶ ይፋ የሆነበት ሁኔታ በመፈጠሩ ትችት ሲቀርብ የተስተዋለ ሲሆን፣ ለምን የአንድ ክልል አጀንዳ ብቻ ይፋ ሆነ? ስንል ኮሚሽነሩን ጠይቀናል።
ኮሚሽነር መላኩ በምላሻቸው፣ “እሱ ስህተት ነው። አንዳንድ ጋዜጠኞች እዛ የመግባት እድል በማግኘታቸው ይዘውት የወጡት እንጂ የኛ አሰራር አይደለም ” ብለዋል።
Via – Tikvah

