የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የጀመሩት የንግድ ታሪፎች ፉክክር ባልተጠበቀ ሁኔታ እየጨመረ ቢመጣም በዚህ ምክንያት ግን ዓለምአቀፍ የኢኮኖሚ ድቀት አይኖርም ሲል የዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም አስታውቋል።
በንግድ ታሪፎች ምክንያት የዓለም የአክሲዮን ዋጋ እየወደቀ መሆኑን የጠቀሰው ተቋሙ፤ በሀገራት መካከል እየተደረጉ ያሉት የንግድ ታሪፎች በሀገሮች መካከል ያለውን መተማመን እንዳይሸረሽረው አስጠንቅቋል።
ይሁን እንጂ አዲሱ ዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ዕድገት ግምት ከፍተኛ የኢኮኖሚ መሻሻል እንደሚመጣ ያሳያል ከማለት ውጭ በንግድ ታሪፎች ፉክክር ምክንያት ሊመጣ የሚችለውን ፈተና ከመተንበይ ተቆጥቧል ተቋሙ።
አይኤምኤፍ ይህን መግለጫ ያወጣው የአሜሪካውፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በሀገራት ላይ በጠሏቸው የንግድ ታሪፎች ምክንያት የአክሲዮን ገበያዎች መሻሻል አለማሳየታቸውን ተከትሎ ነው።
የትራምፕን እርምጃ ተከትሎ የወደቀው ዓለም አቀፍ የአክሲዮን ገበያ መሻሻል አለማሳየቱ እና አንዳንድ ሀገራት የአጸፋ እርምጃ ለመውሰድ መገደዳቸው ዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ውድቀትን ሊያከትል ይችላል የሚሉ ትንበያዎች በዝተዋል።
የዓለም ንግድ ድርጅት ሰሞኑን ባወጣው ትንበያ በትራምፕ ታሪፍ ምክንያት በዚህ ዓመት ያለው ዓለም አቀፍ ንግድ ሊያቆለቁል ይችላል ብሏል።
ዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅትያለው ትንበያ ግን ከዚህ የተለየ እንደሆነ የድርጅቱ ዋና ዳይሬክተር ክርስታሊና ጆርጂዬቫ ተናግረዋል።
“የተሻለ ሚዛናዊና ጠንካራ የሆነ የዓለም ኢኮኖሚ ሊደረስበት ይችላል፤ ይህን ለማረጋገጥ እርምጃ መውሰድ አለብን” ያሉት ዋና ዳይሬክተሯ፣ ሁሉም ሀገራት የራሳቸውን ኢኮኖሚ ከውድቀት ለማዳን የሚያደርጉትን ጥረት በእጥፍ ሊያሳድጉ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
የአውሮፓ ሀገራት በውስጣዊ አገልገሎቶች ላይ የሚጥሉትን እገዳ በመቀነስ ነጠላ ግብይቶቻቸውን እንዲያጠናክሩ፣ ቻይናም የማኅበራዊ ዋስትናዋን እንድታሳድግ እንዲሁም አሜሪካ እዳዋን እንድትቀንስ ምክረ ሀሳብ ማቅረባቸውን ቢቢሲ ዘግቧል።
የአለም ንግድ ድርጅት፤ በተያዘው አመት አሁን እየተካሄደ ባለው የታሪፍ ጦርነት የተነሳ የዓለም የንግድ መጠን በ0.2 በመቶ እንደሚቀንስ ሲገልጽ፤ በ2025 መጨረሻ ላይ የአለም ንግድ 2.5 በመቶ ይሆናል ብሏል።
በተለይም አሜሪካ እና ቻይና በንግድ ታሪፍ ጭማሪ ላይ እየወሰዱ ያሉት እርምጃ የዓለምን የንግድ እንቅስቃሴ ብሎም የኢኮኖሚ ሁኔታ በእጅጉ እንደሚጎዳ ድርጅቱ ይገልፃል፡፡
የንግድ ጦርነቱ በዚሁ የሚቀጥል ከሆነ የአለም ንግድ እስከ 1.5 በመቶ እንደሚያሽቆለቁል እና ይህም እያደጉ ባሉ ሃገራት ላይ ጫና ሊያሳደር እንደሚችልም ተጠቁሟል።
የኢኮኖሚ ባለሙያዎች እንደሚገልጹት ከሆነ የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የታሪፍ ጭማሪ ካልቆመ በአሜሪካ እና በቻይና በኩል የሚደረገው የንግድ ግብይት ሙሉ ለሙሉ ሊቆም እንደሚችል ትንበያቸውን ያስቀምጣሉ።
በቅርቡ አሜሪካ በቻይና ላይ የ145 በመቶ ታሪፍ እንዲሁም ቻይና በአሜሪካ ላይ በምላሹ የ125 በመቶ ታሪፍ እንደጣሉ የሚታወስ ሲሆን አሜሪካ የታሪፍ መጠኑን ወደ 245 በመቶ ከፍ ለማድረግ ምክረ ሃሳብ ማቅረቧም ተዘግቧል።
በለሚ ታደሰ እና በቢታኒያ ሲሳይ ETV

