ሌ/ጄነራል ታደሰ ወረደ በመፈንቅለ መንግስት ከስልጣን እንዲወርዱ የተደረጉትን አቶ ጌታቸው ረዳን ሲተኩ በገቡት ቃለ መሰረት የትግራይ ሁኔታ ሊቀየር እንደሚችል ግምት ነበር። ይህ የአብዛኞች ግምት መነሻው ታደሰ ወረደ ቀድሞውንም ከአቶ ጌታቸው ጋር የጸጥታውን ኃላፊነት ወስደው ይሰሩ የነበሩት ይይስሙላ እንደሆነ በርካታ መረጃና ማስረጃዎች የሚጣቀሱበት ነው።
የእሳቸው ሹመት ይፋ እንደሆነ ‹‹ከጦርነቱ በኋላ እኛ ከጫካ ወደ ከተማ ስንገባ እነሱ ወደ ዝርፊያ ገቡ›› የሚሉና በጓሮ ከሻዕቢያ ጋር የተጀመረውን ሽርክናና የወርቅ ዝርፊያ የተቃወሙ የጦር አመራሮች ድምጽ ተሰማ።
ከፕሪቶሪያው ስምምነት በሁዋላ ተኩስ ቢቆምም ትግራይ ውስጥ የተጀመረው አዲስ ፖለቲካ ሻዕቢያን በብርሃን ፍጥነት ከጠላትነት በተቃራኒ ሙሉ በሙሉ ወዳጅ አድርገ። “ከሻዕቢያ ጋር ፅምዶ (ቅንጅት) እየፈጠራችሁ ስለሆነ እናጠፋችኋለን ስለተባልን ነው ለጦርነት የምንዘጋጀው” ሲሉ በእነ ዶክተር ደብረጽዮን ቡድን በኩል ያለውን የትግራይ ታጣቂ ኃይል ከሚመሩት መካከል አንዱ የሆኑት ጄነራል ኃይለ ሥላሴ ግርማይ (ወዲ እምበይተይ) ሰሞኑን ኮማንዶ ሲያስመርቁ ተናገሩ። ይህ ንግግራቸው የሻዕቢያንና የወያኔን ዳግም ፍቅር አደባባይ ያወጀ ሌላኛው አዋጅ ሆነ።
“ይህ አዲስ ፍቅር በቅጽበት ሻዕቢያን ጽድቅ አደረገ። በጅምላ የጨፈጨፋቸውን የትግራይ ልጆች አስረሳ። በደቦ የተደፈሩትን፣ በቫይረስ እንዲበከሉ የተደረጉትን፣ ማህጸናቸው ውስጥ ባዕድ ነገሮች የተጨመረባቸውን እናቶችና እህቶች ስቃይ ፋቀ። በቅርሱ ሴንቸሪና ዘ ጋርዲያን ያወጡትን ለማንበበና ለመመልከት የሚከብድ ሪፖርት ሁሉ አስጣለ። ከፋብሪካ እስከ ቆርቆሮና በር ነቀላ፣ ከቤት ቂሳቁስ እስከ ሽሮና በርበሬ የዘረፈውን ክፉ ኃይል ‘ ጄኖሳይድ አልፈጸምክን፣ ሴቶችን አልደፈርክም’ በሚል ምህላ ትግራይ ምድር ላይ ዳግም እንዲፏልል አደረጉት” በሚል ሃዘናቸውን ገልጸው አቶ ግሩም ተስፋዬ ሃዘናቸውን ገልጸዋል።
ጄነራል ኃይለ ሥላሴ ግን “… እኛ ከሌሎች ጋር አጋርነትን [ኤርትራና ግብጽና ሱዳንን ማለታቸው ነው] በዓይነት ስንጨምር ጠላት (አራት ኪሎ ያለው) ወዳጆቹን አጥቷል” በማለት ሕዝብ እየሰማ በጭብጨባ ታጅበው በይፋ እውነቱን አበሰሩ። ሌሎች በጅምላ ሲያወሩ እሳቸው የጉዳዩን እምባርት አስታወቁ።
ይህ በሆነ በቀናት ልዩነት የቀይ ባህር አፋሮች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት በኤርትራ በሻዕቢያ የግፍ ቀበር ስር ያሉትን አፋሮች ነጻ ለማውጣት የትጥቅ ትግሉን እንደሚያጠናክር አስታወቀ። በሰመራ በሺህ የሚቆጠሩ አባላቶቹ ጋር ስብሰባውን ያደረገው የአፋር ነጻ አውጪ ፣ በመግለጫው ይፋ እንዳደርገው ሻዕቢያን ከሚቃወሙ ጋር ህብረት አድርጓል። በስብሰባውም ጋብዟቸዋል።
ከትናንት በስቲያ ” በትግራይ ላይ የሚታሰብና የሚደረግ የውክልና ግጭት (Proxy Conflict) ተቀባይነት የለውም ” ሲሉ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር መሪ ሌ/ጄነራል ታደሰ ወረደ ተናገሩ። “የውክልና ግጭት” ሲሉ ስም የሰጡት በአፋር ክልል ሰፍሯል ለተባለው የትግራይ ሰላማዊ ጦር ሲሆን፣ ጦሩ ሰሞኑን “ያለሁት ትግራይ ነጻ መሬት እንጂ አፋር አይደለም” ማለቱ አይዘነጋም።
እርስ በርሱ የሚጣረስ መግለጫና ሴራ እየናጣት ያለችው ትግራይ ለህጋዊውም፣ ለህገወጡም ጉዳይ ሕገመንግስት ይጠቀስባታል። ሕገመንግስት ጠቅሶ መጠየቅ፣ ቅሬታን ማቅረብ፣ የመብት ይከበር ግዴታን ማንሳት እንጂ ግዴታ የሚባል ነገር በትግራይ ፖለቲከኞች ዘንዳ የሚታሰብ እንዳልሆነ ታዛቢዎች መናገር ከጀመሩ ቆይቷል። ሻዕቢያ የጨፈጨፋቸውን ቀብረው ሳይጨርሱ በሻዕቢያ ፍቅር ተነድፈው ሕገመንግስቱን በመናድ በገሃድ ጥፋት እየሰሩ መልሰው “የሕገመንግስት ያለህ ሲሉ ያስደነግጣል። እንዴትስ ከነደነዚህ ዓይነት ኃይሎች ጋር በአመክንዮ መነጋገርና በግባባት ይቻላል?” በሚል እነዚሁ ታዛቢ ወገኖች ይናገራሉ። ሲያጠቃልሉም “በትግራይ ሕግ ፈሷል። መላ ካልተባለ አደጋ አለው፡፡ ጦርነት አያስፈልግም መመካከርና መፍትሄ መፈለጉ ከቀናዎች ይጠበቃል”
በመቐለ የሰማዕታት ሀውልት አዳራሽ በተካሄደው 36ኛው የሰማዕታት ቀን የማጠቃለያ ፕሮግራም ተገኝተው ንግግር ሲያደርጉ ” ነፃ (ሓራ) መሬት ተብሎ ትግራይ ላይ ለሚቃጣ ማንኛውም ዓይነት ጥቃት ተጠያቂዎቹ የፌደራል እና የዓፋር ክልል መንግስታት ናቸው ” በማለት ታደሰ ወረደ ሲናገሩ ተሰምቷል።
“ይህን የሰሙና በማህበራዊ ገጾች ጥያቄ ያነሱ ጄነራሉ ሻዕቢያ ከድርጅታቸው ጋር ሕብረት መፍጠሩን ያውቃሉ፡፡ በአገሪቱ ሕግ መሰረት ይህ አይቻልም፡፡ ከፌደራል መንግስት አገልግሎትና በጀት እየተጠቀሙ፣ በፌደራል መንግስት ተሹመው፣ ለፌደራል መንግስት ተጠሪ ሆነው ሳለ ሻዕቢያንና ትህነግን ወግነው ወይም አባሪ ሆነው በዚህ መልኩ በግልጽ መናገራቸው ወንጀል ነው” ባይ ናቸው፡፡ እነዚሁ ወገኖች የፌደራል መንግስትን ከህግ አንጻር መረዳት ቢፈለግ እንኳን እነሱን መርዳት እንደማይቻል በርካታ መረጃዎችን እያጣቀሱ ያናገራሉ።
“በበፊቱ ጦርነት ወቅት እስከ ደብረሲና ሲዘልቁ እነሱ ትክክል ነበሩ። መንግስት ኃይሉን አሰባስቦ ሲመታቸው ጄኖሳይድ ይላሉ። እነሱ ሲገድሉ ጽድቅ፣ ለኤላው በጦርነት ራሱን ሲከላከልም ሆነ ሲያጠቃ ጄኖሳይደር ብለው ይከሳሉ” የሚሉ ወገኖች ” አራት ኪሎ ገብተን መንግስት ገልብጠን፣ እንደቀድሞው መከላከያን አፍርሰን … ስናደርግ ዝም በሉን ነው እያሉ ያሉት ወይስ ምንድን ነው? እንኳን ለመከራከር እንዴት እንደሚያስቡ ለመረዳት ያዳግታል” ሲሉ መሰላቸታቸውን የሚገልጹ ጥቂት አይደሉም።
ቀደም ሲል በድርድር የሚያልቅ ጉዳይ እንደሆነ ገልጽው እዚህ ግባ የሚባል ኃይል እንዳልሆነ የጠቆሙትን የትግራይ ሰላም ኃይሎችን ጉልበት፣ ታደሰ ወረደ ከትናንት በስቲያ ባደረጉት ንግግር ደግሞ ” በዓፋር እንጂ በትግራይ ነፃ (ሓራ) መሬት ብሎ የለም ” ሲሉ አዲስ መረጃ ሰጥተዋል።
ራሳቸውን የትግራይ ሰላም ኃይሎች ብለው የሚጠሩትና አስር የሚጠጉ ጄነራሎች፣ እንዲሁም በርካታ ከፍተኛ መኮንኖችና 13 ክፈለጦር ያለው ኃይል ያደራጁት ወገኖች ” የምንገኘው በትግራይ ነጻ መሬት ውስጥ ነው” በሚል ካስታውቁ በሁዋላ፣ ትግራይን ወደ አልተገባ አቅጣጫ እየመራ ያለው ቡድን በሰላማዊ መንገድ ራሱን የማያስገዛ ከሆነ ከጌታው ጋር አንድ ላይ እናስወግደዋለን” ሲሉ ለቢቢሲ ትግርኛ መግልጻቸው ይታወሳል። ትግራይን እያስተዳደሩ ላሉት ሌ/ጄነራል ታደሰ በተደጋጋሚ መልዕክት መላካቸውንም አስታውቀዋል።
ለአፋር ሕዝብ ነጻነት ትግል ራሱን እያዘጋጀ ያለውን የአፋር ነጻ አውጪና የትግራይ ሰላም ኃይሎችን የውክልና ግጭት ለማድረግ እንደተዘጋጁ ጠቅሰው ማስጠንቀቂያ ያቀረቡት ታደሰ ወረደ፣ ” ነፃ (ሓራ) መሬት ተብሎ ትግራይ ላይ ለሚቃጣ ማንኛውም ዓይነት ጥቃት ተጠያቂዎቹ የፌደራል እና የዓፋር ክልል መንግስታት ናቸው ” ብለዋል።
ስምረት ፓርቲ በበኩሉ “ከአሁን በኋላ በትግራይ ላይ የሚፈፀሙ ጥፋቶች ብቸኛው ተጠያቂ ከዓለም አቀፍና አገራዊ ህጎች የተቃረነው ወመኔው ኋላ ቀር ቡድን እና መሰሎቹ መሆናቸው የኢትዮጵያ መንግስት መገንዘብ አለበት ” ሲል ይህ ቡድን እርምጃ እንዲወሰድበት ጠይቋል።
” የሃይማኖት አባቶች ፣ የአገር ሽማግሌዎች ፣ ወጣቶች በአገር ውስጥና በመላ ዓለም የሚገኙ ትግሬዎች ቡድኑ በስልጣን የሚቆይባቸው እያንዳንዱ ቀናት በህዝብ ላይ አስከፊ መከራና ስቃይ የሚያስከትሉ መሆናቸው በመረዳት ትግላችሁ አጠናክሩ ” የሚል ጥሪም አቅርቧል።
” ሌት ተቀን የጦርነት ነጋሪት ከሚጎስመው ኋላ ቀር ቡድን ራሳችሁን በማራቅ ከሰላም ፈላጊ ህዝብ ጎን ተሰለፉ ” ሲል አቶ ጌታቸው የሚመሩት ስምረት ፓርቲ ደጋግሞ አሳስቧል።
ጥሪውም ይሁን የሕዝብ ፍላጎት ከፊት ለፊት እንደሚታየው ሰላም ቢሆንም በትግራይ አሁን ላይ የኮማንዶ ምርቃት የሚያሳዩ መረጃዎች በስፋት በምስል እየወጡ ነው።
“ጦርነት ባህልህ ነው” እየተባለ በመጀመሪያው ጦርነት ሲደረግ እንደነበረው፣ እናቶች ልጆቻቸውን እየመረቁ የሚሸልሉበት ዓይነት የስታዲየም ድግስ ባይሆንም ኮማንዶዎች ሲመረቁ የሚያሳዩ ቪዲዮ ማየት የተለመደ ሆኗል። ኤርትራም በተመሳሳይ እያስመረቀች ነው።
” ነፃ (ሓራ) መሬት ብሎ በትግራይ የለም ” በማለት ሌተናል ጄነራል ታደሰ በንግግራቸው አንስተው ” በዓፋር ክልል ያለው የትግራይ ታጣቂ በፌደራልና በዓፋር ክልል መንግስታት እውቅና እገዛ የሚንቀሳቀስ ነው ” ሲሉ የሾማቸውን መንግስት ዘልፈዋል።
” በዓፋር በኩል ያሉ ታጣቂዎች ትግራይ ላይ የሚቃጡት ማንኛውም ዓይነት ጫናና ግጭት ጊዚያዊ አስተዳደሩ የፌደራልና የዓፋር መንግስታት ፍላጎት እንጂ የነሱ አድርጎ አይመለከተውም ” ያሉት ሌተናል ጄነራል ታደሰ፣ ” እዚያ ካሉት ታጣቂዎች ያለው ማንኛውም ዓይነት ልዩነት ከውይይት ውጪ ሊፈታ አይችልም ” ብለዋል። አክለውም ” የፌደራልና የዓፋር መንግስታት ጉዳዩ ሰላማዊ ዕልባት እንዲኖረው ማገዝ አለባቸው ” የሚል ጥሪም አቅርበዋል። እሳቸው በሚመሩት ክልል የውጭ አገር ሰራዊት እንዳሻው ስለመቦረቁ ኝ ያነሱት አንዳችም የሕግ ጥያቄም አልተሰማም።
” የትግራይ ቁጥር አንድ ጥያቄ የፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት እንዲተገበር ነው ፤ ከዚህ ውጪ የውክልና ግጭት (proxy Conflict) እንዲካሄድ የሚደረገው ጥረት ተቀባይነት የለውም የሚሳካም አይደለም ” በሚል ንግግራቸው የደመደሙት ሌተናል ጄነራል ታደሰ፣ የሾማቸው የፌደራሉ መንግስት ምን ማልሽ እንደሚሰጣቸው ለጊዜው አልታወቀም።
በትግራይ ያለው ሕገወጥ እንቅስቃሴ ለመግታትና መስመር ለማስያዝ የሚያስችል ስራ እየሰራ እንደሆነ የሚገልጸው የትግራይ ሰላም ኃይሎች፣ በትግራይ በጉልበት መንግስት ገልብጦ ያለውን የእነ ደብረጽዮንን ቡድን ለማስወገድ ከጫፍ መድረሱን ማስታወቁ አይዘነጋም።
በሶስት ዙር በተካሄደው ጦርነት፣ መንግስት ነዳጅ፣ በጀት፣ ተሽከርካሪ፣ ቀለብ፣ መድሃኒት ወዘተ እንዲያቀረበ ይዋጋ እንደነበር የሚታወስ ነው።
በትግራይ ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ ሕዝቡ ጦርነትን አብዝቶ እንደሚቃወም መረጃዎች ያሳያሉ።
የተፈናቀሉ ወገኖች ወደ ቀዬያቸው ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ተመልሰው መግባባት ከተፈጠረ በሁዋላ ሕዝቡ ራሱ መክሮ በሚያቀርበው አሳብ መሰረት ዘላቂ መፍትሄ እንዲሰጠው የሚለውን የገለልተኛ ወገኖች ምክረ አሳብ በርካቶች በበጎ ቢያዩትም ከትግራይ ኃይሎች አንጻር “ቀድሞ ትህነግ ይዳን” በሚል ተቀባይነት ሊያገኝ አለመቻሉ በተደጋጋሚ የሚሰማ መሆኑ ያታወሳል።

