ኤርትራን በተመለከተ እስከማውቀው እና እስከገባኝ ድረስ፤ በኢትዮጵያ መንግስት በኩል ወደ ጦርነት የመግባት፤ በኢሳይያስ በኩል ከድንፋታ ያለፈ በቀጥታ የመላተምም ሆነ የመታኮስ ፍላጎት የለም። Proxy war ግን ሊኖር ይችላል። ስለዚህ የኢሳይያስን ድንፋታ ተማምኖ፣ ምንጩ እና አቅጣጫው በማይታወቅ የሶሻል ሚዲያ ምረጃ እና ሽቀጣ ተጀንጅኖ እንደ ህወሐታውያን ወደ መንግስት ለመተኮስ ያሰበ ኃይል ሁሉ ደጋግሞ ማሰብ ያለበት አንድ ነገር ራሱን “የጨዋታው ሜዳ” (ወይም chessboard) ከማድረግ ያለፈ ምንም ሚና እንደማይኖረው
Oluma M. Wodajo FB OPINION
ሰሞኑን የኤርትራው ገዢ ኢሳይያስ አፈወርቂ እንደተለመደው የራሱን ያረረ ድስት ትቶ፤ ለሁለት ሰአታት ያህል የሌሎችን የበሰለ ድስት ሲያማስል ተመልክተናል። ሰውዬው ሲያወራ የአንዲት ሚጢጢ gulag state ገዢ ሳይሆን የራሺያ፣ የአሜሪካ ወይም የቻይና ፕሬዚደንት ነበር የሚመስለው It was a virtual display of cognitive dissonance at a higher scale! ለዛሬ በአብዛኛው ስለዘበዘበው የኢትዮጵያ ጉዳይ–በተለይም በድህረ-2010ሩ የኢትዮ-ኤርትራ ግንኙነት ከፍታ እና ዝቅታ ላይ እናተኩር።
እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ እና የኤርትራ ግንኙነት ከሁለት አስርት አመታት “cold war” በኋላ መፍትሄ ያገኘው በ2010 ጠ/ሚ አብይ በተሾመበት ዕለት ያደረገውን ንግግር ተከትሎ ለወራት ከተደረገ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት በኋላ ነው። የዚህ ጥረት መቋጫውም በመስከረም 2011 በጂዳ (ሳዑዲ አረቢያ) የተፈረመው የሰላም ስምምነት ነው። ሁለቱ ሀገራት ያደረጉት ስምምነት በዋናነት ያተኮረውም ያለፈውን ትቶ በመጪው ዕጣ ፈንታቸው ላይ መተባበር የሚችሉባቸውን ጉዳዮች በቶሎ ለይተው ወደ ተግባር እንዲሸጋገሩ በማመቻቸት ላይ ነው። በዚህ መሰረትም ኢትዮጵያ እንደ ሀገር በተናጠል ተከታታይ የconfidence building measures ወስዳለች። ከእነዚህ ውስጥም፦
- ዋና ዋናዎቹ የድምበር አካባቢ መሸጋገሪያዎች እንዲከፈቱ ማድረግ፣
- የመከላከያ ሰራዊትን posturing መከለስ፣
- በኤርትራ ላይ የተጣሉ አለም አቀፍ ማዕቀቦች ተራ በተራ እንዲነሱ ማስደረግ፣ እና
- ኤርትራን ተገልላ እና ራሷን አግልላ ወደኖረችበት የቀጠናው የትብብር ማዕቀፎች እንድትመለስ ማድረግ ናቸው። በተጨማሪም በሁለቱ ሀገራት መሐከል ያለው ግንኙነት ቀጠናዊ ትርጉም እንዲኖረውም ሶማሊያን በማሳተፍ ከአስመራ በአዲስ አበባ እስከ ሞጋዲሹ ድረስ የትብብር መስመር ለመዘርጋት ብዙ ጥረት ተደርጓል።
የባህር በር አጠቃቀምን በተመለከተ ኤርትራን፣ ኢትዮጵያን እና UAEን ያካተተ መሰረታዊ መግባባት ላይ ተደርሶ ነበር። በይፋ ከሚታወቁ ሂደቶች ባሻገርም የዱባዩ DP World አሰብን የኢትዮጵያን ትልልቅ የንግድ መርከቦች ማስተናገድ በሚያስችል ሁኔታ upgrade እንዲያደርግ የሶስትዮሽ ስምምነት ተደርጎ፤ የዲዛይን እና ተዛማጅ ስራዎች እንቅስቃሴ በDP World አማካይነት ተጀምሮ ነበር። በተጨማሪም UAE ከኤርትራ (አሰብ) ወደ ኢትዮጵያ የነዳጅ ማስተላለፊያ ቱቦ ለመገንባት ሀሳብ አቅርባ ዝርዝር ውይይት ለማድረግ ቀጠሮ ተይዞ ነበር። ከዚህ ባሻገርም በፈረንሳይ መንግስት ስልጠና እየተሰጣቸው የነበሩት የአዲሱ የኢትዮጵያ የባህር ኃይል አባላት ስልጠናቸውን ጨርሰው ሲመጡ በአሰብ ወደብ አካባቢ በሚዘጋጅ የባህር ኃይል ቤዝ/ካምፕ እንደሚሰፍሩ አጠቃላይ መግባባት ላይ ተደርሶም ነበር። ከላይ በተገለፁት ምክንያቶችም ነው ሁለቱ ሀገራት በየራሳቸው ግዛት ውስጥ ያሉትን ሀገር አቋራጭ መንገዶች ማደስ እና upgrade ማድረግ የጀመሩት።

በመሐል ግን የግንኙነቱን የመጀመሪያ ስንጥቃት ያስከተሉ ሁለት ችግሮች መፈጠር ጀመሩ። አንደኛው የተለመደው የኤርትራውያን የማይድን አመል ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ በወቅቱ እየተባባሰ የመጣው የህወሐታውያን sabotage ነው። ማለትም፦
- የኤርትራውያን የማይድን አመል፡ በኢህአዴግ ጊዜም ሆነ ዛሬ ከኤርትራ ጋር ሰላማዊ ግንኙነት መመስረትን ከባድ ካደረጉት ነገሮች አንዱ ኤርትራውያን በኢትዮጵያ ፖለቲካ እና ኢኮኖሚ ውስጥ እስከ አንገታቸው ድረስ ለመግባት የማያመነቱ ይሉኝታ-ቢሶች መሆናቸው ነው። ይህም በአጭሩ ሲገለፅ “ኢትዮጵያ የጋራችን፤ ኤርትራ የግላችን” በሚል አስተሳሰብ ላይ የተመሰረተው ጣልቃ-ገብነታቸው ነው። ከላይ ከተገለፁት በተጨማሪ ያሉት ማሳያዎችም ደህንነቶቻቸውን ኢትዮጵያ ውስጥ በስውር አስርገው በማስገባት ኤርትራውያን ስደተኞችን ከማፈን እስከ ደብዛ ማጥፋት፣ በአንዳንድ ወሳኝ ውስጣዊ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ጫና ለማድረግ መሞከር፣ ህገ-ወጥ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎችን መፈፀም፣ ወዘተ ግንኙነቱ በታደሰ በወራት ውስጥ የታዩ ችግሮች ናቸው።
- የህወሐታውያን sabotage: በህወሐት በኩል ደግሞ የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት ላይ “veto power” ሊኖረኝ ይገባል ከሚል የተሳሳተ ግንዛቤ የተነሳ ተከታታይ እና ተለዋዋጭ sabotage ይፈፀም ነበር። በተለይ ከላይ የተዘረዘሩት የ confidence building እርምጃዎችን ለማሰናከል ህወሐት ለአመታት ያካበተውን ልምድ፣ አለም አቀፍ ኔትወርክ እና ለኤርትራ ያለውን geographic proximity በስፋት ተጠቅሟል። የደህንነት እና ወታደሪዊ መረጃዎችን በመመዝበር ተጠግኖ ገና መሰረት ያልያዘውን ግንኙነት ሲገዘግዘው ከርሟል። በኋላም ጥቅምት 24/2013 ሰሜን ዕዝን በማጥቃት ቀጥሎም ወደ አስመራ ሮኬቶችን በመተኮስ የሁለቱ ሀገራት ትብብር ከኢኮኖሚያዊ ዘርፎች ይልቅ ወታደራዊ፣ የደህንነት አና ፖለቲካዊ ትብብሮች ላይ እንዲያተኩሩ አስገዳጅ ሁኔታዎችን ፈጥሯል።
ሁለቱ ሃገራት የህወሐት ወታደራዊ እንቅስቃሴ የጋረጠባቸው የጋራ የብሄራዊ ደህንነት አደጋ ላይ በተቀናጀ ኃይል እርምጃ ወስደዋል። ይህ ትብብር በራሱ ግን በሁለቱ ሃገራት መሃከል ያሉትን ስትራቴጂክ እና ታክቲካል ልዩነቶች እጅግ ያጎላ ነበር። የኢሳያስ መንግስት ትግራይ ውስጥ የሚካሄደው ወታደራዊ ዘመቻ ህወሐት እና ህወሐታውያን ከምድረ-ገፅ እስኪጠፉ ድረስ መሆን አለበት የሚል አቋም ነበረው። በኢትዮጵያ መንግስት በኩል ደግሞ ከህወሐት ጋር የሚደረገው ትንቅንቅ ትግራይ ውስጥ ካስከተለው ሁለንተናዊ መዳቀቅ ባሻገር፤ የውጊያው geographic scope እየሰፋ ሰብአዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ዲፕሎማሲያዊ ኪሳራውን እያበዛው በመምጣቱ ውጊያውን ለኢትዮጵያ ሀገረ-መንግስት በሚጠቅም ወሳኝ የሃይል ሚዛን ላይ አድርሶ በጠረጴዛ ዙሪያ መፍታት የሚል አቋም ተይዞ ነበር። በዚህም መሰረት የሀይል ሚዛኑ ወደተፈለገበት አቅጣጫ ባዘነበለበት ወቅት ውይይቶች እና ድርድሮች በጂቡቲ እና በሲሼልስ፤ በመጨረሻም በፕሪቶሪያ ተደርጎ ህወሐት በስሙ “cessation of hostilities agreement” የተባለውን፤ በይዘቱ ግን “capitulation agreement” የሆነውን “የፕሪቶሪያ ስምምነት” ወድዶ ሳይሆን ታንቆ ፈርሟል!
የኤርትራ መንግስት ስምምነቱ premature (ያለ ጊዜው የተደረገ) ነው፤ የህወሐት ግብአተ መሬት ሳይፈፀም ውጊያው እንዲቆም መደረግ የለበትም ብሎ ሞግቷል። ይህን በሚልበት ወቅት የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ከመቐለ 55 ኪሎ ሜትር ርቀት ኲሐ ላይ ነበረ። መቐለ እና በዙሪያዋ ያሉትን ወረዳዎች ለመያዝ በከባድ መሳሪያ እየደበደበ መገስገስ የሚችልበት ሙሉ የሀይል ሚዛን ነበረው። ነገር ግን ይሄ የሚያስከትለው ሰብአዊ እና ቁሳዊ ኪሳራ አይደለም በራስ ሀገር፤ ለጠላትም የሚመኙት አልነበረም። ህወሐትም ቅድመ-ሁኔታዎቹን በሙሉ ትቶ ስምምነቱን የፈረመው ለዚሁ ነበር! በዚህም አራት ሃይሎች አኮረፉ፦ የኤርትራ መንግስት፣ አክራሪ የአማራ ብሄረተኞች (ዛሬ ራሳቸውን “ፋኖ” ከሚሉ አማፅያን ጋር የተቀላቀሉ)፣ ሃሳዊ pan-Ethiopianists እና አክራሪ ህወሐታውያን። የመጀመሪያዎቹ ሶስቱ “ህወሐት ሳትጠፋ ጦርነቱ መቆም የለበትም” ባዮች ሲሆኑ፤ አክራሪ ህወሐታውያኑ ደግሞ መሬት ላይ የደረሰባቸውን ሽንፈት ለመቀበል የከበዳቸው grieving losers ናቸው!
ወደ ኤርትራ መንግስት (ወይም ወደ ኢትዮ-ኤርትራ ግንኙነት) ስንመለስ፤ ከፕሪቶሪያው ስምምነት በኋላ የተከተላቸው ሂደቶች ሁሉ ከአንድ ሃገር የሚጠበቅ ሳይሆን ዕቃ-ዕቃ ሲጫወቱ እንደነበሩ ህፃናት “ጨዋታው ፈረሰ ዳቦ ተቆረሰ” ይመስል ነበር። ማለትም ጦርነቱ በህወሐት ከምድረ-ገፅ መጥፋት የማይጠናቀቅ ከሆነ፤ ከጦርነቱ በፊት የተስማማንባቸው የትብብር ማዕቀፎች እና የተጀመሩ ስራዎች በሙሉ “ፈርሰዋል”። በDP Worldም ሆነ በUAE እና በፈረንሳይ ድጋፍ እንዲሰሩ የተስማማንባቸው ነገሮች ሁሉ ተሰርዘዋል። DP Worldም ጓዙን ጠቅልሎ ከአሰብ ይውጣ የሚል ነበር። ይህን ተከትሎ በአዲስ አበባ እና በአስመራ የተደረጉ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች በኢሳይያስ ግትርነት ሳቢያ አልተሳኩም። ብዙ የተለፋበት እና በ “Win-Win” እሳቤ የተጀመረው አስተማማኝ የባህር በር ተጠቃሚነት እና በቀይ ባህር አካባቢ ኢትዮጵያን በሰላማዊ ሂደት ለማንበር (“presence at the sea”) የተደረገው ጥረትም በዚሁ ተጨናግፏል።
ከላይ የተዘረዘረውን ተከትሎ እስከዚህ 2015 በምስጢር ተይዞ የነበረው እና ከኤርትራ መንግስት ጋር በሚደረግ “incremental cooperation framework” ለኢትዮጵያ “አስተማማኝ እና ደህንነቱ የተጠበቀ የባህር በር” በሰላማዊ መንገድ የማስገኘት ጥረት ይፋ ተደርጓል። ይህንም በ2015 እና 2016 በነበሩ የተለያዩ መድረኮች ጠቅላይ ሚኒሰትር አብይ በአደባባይ አስረድቷል። የኤርትራ መንግስትም አብሮ ያቀደውን ነገር ሁሉ ክዶ፤ ክፉ መርዶ እንደሰማ ለቀስተኛ ደረቱን ሲደቃ እነሆ ሁለተኛ አመቱን ይዟል። አልፎ-ተረፎም ለኩርፊያው ሰበብ የሆነውን እና ለምን ከምድረ-ገፅ አልጠፋም ሲለው የነበረውን የህወሐት ፍርስራሽ እንደ proxy ለመጠቀም እንቅስቃሴ ጀምሯል። ከስህተታቸው የማይማሩት አዕምሮ ስንኩላን ህወሐታውያንም ዳግመኛ በትግራይ ምድር ጦርነት እንዲደረግ ሰማይ መቧጠጥ ይዘዋል። የኤርትራን መንግስት ተማምነው፤ መንግስት በአማራ እና በኦሮሚያ ተወጥሯል ብለው አምነው ለኢትዮጵያ መንግስት ያለንን ድጋፍ እና ተቃውሞ ለጊዜው ወደ ጎን እንበለውና፤ ዛሬ በሀገሪቱ የተገነባው security architecture በማንኛውም objective መለኪያ ከ2013 እስከ 2015 ከነበረው የተሻለ መሆኑን መረዳት ለሁሉም ይጠቅማል። ይህ መንግስት ከመጣ ጀምሮ ፋታ በማጣቱ፤ በጦርነት “ጥርሱን ነቅሏል”። ካሁን በኋላ “እወጋሃለው” ብሎ ማስፈራራትም፤ “እንዋጋ በለው” ብሎ መጋበዝም ማንንም አይጠቅምም።
ለማጠቃለል፦ ኤርትራን በተመለከተ እስከማውቀው እና እስከገባኝ ድረስ፤ በኢትዮጵያ መንግስት በኩል ወደ ጦርነት የመግባት፤ በኢሳይያስ በኩል ከድንፋታ ያለፈ በቀጥታ የመላተምም ሆነ የመታኮስ ፍላጎት የለም። Proxy war ግን ሊኖር ይችላል። ስለዚህ የኢሳይያስን ድንፋታ ተማምኖ፣ ምንጩ እና አቅጣጫው በማይታወቅ የሶሻል ሚዲያ ምረጃ እና ሽቀጣ ተጀንጅኖ እንደ ህወሐታውያን ወደ መንግስት ለመተኮስ ያሰበ ኃይል ሁሉ ደጋግሞ ማሰብ ያለበት አንድ ነገር ራሱን “የጨዋታው ሜዳ” (ወይም chessboard) ከማድረግ ያለፈ ምንም ሚና እንደማይኖረው ማስታወስ ነው። በኢትዮጵያ እና በኤርትራ መሐል እየመጣ ያለው ሁለተኛው ቀዝቃዛ ጦርነት (the second “cold war”)፤ ከመጀመሪያው በአይነቱም በውጤቱም የተለየ ነው የሚሆነው! Let that sink in
By Oluma M. Wodajo FB


