በአሜሪካ የጥገኝነት ማመልከቻ ያስገቡት አቶ በቀለ ገርባ የስደት ፈቃድ ማመልከቻቸው ውድቅ ተደረገ። በድጋሚ እንዲታይላቸው ይግባኝ መጠየቃቸውም ታውቋል። ዳግም ወደ ፖለቲካ ተሳትፎ የተመለሱትም በዚህ ሳቢያ እንደሆነ ተመልክቷል።
ከእስር ከተፈቱ በሁዋላ ምስጋና ለማቅረብ ወደ አሜሪካ ከጃዋር ጋር ያመሩት አቶ በቀለ በምስጋና ጉዟቸው ወቅት ከአቶ ጃዋር ጋር ባለመግባባት መለያየታቸውና ይህ አለመግባባት አዲስ አበባ እያሉ የተጀመረ እንደነበር ጉዳዩን የሚያውቁ ማስታወቃቸው አይዘነጋም።
በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ በግል እና በፓርቲ ደረጃ ተሳታፊ የነበሩት አቶ በቀለ ገርባ ከፓርቲያቸው የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) በመልቀቅ በአሜሪካ ጥገኝነት መጠየቃቸውን ይፋ ያደረጉት ራሳቸው በቢቢሲ በኩል ነበር።
ወደ አሜሪካ ከመጡ አንድ ዓመት ከሦስት ወር እንደሞላቸው ገልጸው ለቢቢሲ ምክኛታቸውን ያስረዱት አቶ በቀለ ገርባ፣ “መጀመሪያ ስንመጣ የነበረኝ ዕቅድ በውጭ ከሚኖረው ሕዝባችን ጋር ተገናኝተን፣ አንደኛ ከእስር እንድንለቀቅ ላደረጉት ትግል ለማመስገን ሁለተኛ ደግሞ ወደፊት ምን ማድረግ አለብን የሚለው ላይ ለመወያየት ነበር” ካሉ በሁዋላ፣ አሜሪካ በቆዩባቸው 15 ወራት በኢትዮጵያ ያለው ሁኔታ በመቀየሩ “ወደዚያ አገር መመለሱ አስፈላጊ መስሎ አልታየኝም” ሲሉ አስታውቀው ነበር።
የስደት ማመልከቻቸውን ያየው ፍርድ ቤቱ ችግር መኖሩን ገልጾ እሳቸው ቢመለሱ ለሕይወታቸው አስጊ ጉዳይ እንደሌለ በመጥቀስ ማመልከቻቸውን ውድቅ ማድረጉን የፍርድ ሂደታቸውን የሚያውቁ ገልጸዋል።
አቶ በቀለ ትልቅ ሰው መሆናቸውንና በዚህ እድሜያቸው የተረጋጋ ሕየወት የሚኖሩበት ወቅት መሆኑን ያስታወቁት እነዚህ ወገኖች አቶ በቅለ በጠበቃቸው አማካይነት ይግባኝ መጠየቃቸውን ገልጸዋል። ውሳኔው ሊቀየር እንደሚችልም ገምተዋል።
በቅርቡ በጀርመን ድምጽ “ምነው ጠፉ? በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ «አዎ ትክክል ነዉ። ብዙም አልታይም። ተሳትፎዩ ላይ አንዳንድ ገደቦች አድርጌያለሁ። ገደብ ያደረኩባቸዉ ምክንያቶችም፤ አንደኛ፤ ቀድሞ የፓርቲ ሃላፊነቴ የሚጥልብኝ ግዴታ ነበረ። ስለዚህ በሃላፊነቴ ወጥቼ መናገር ይገባኝ ነበር። አሁን ግን ያ ሃላፊነት የለብኝም። ሁለተኛ፤ እኔ ማድረግ የምችለዉን ነገር ሌሎች አገር ዉስጥም ከአገር ዉጭም ያሉ ሰዎች አሉ። ስለዚህ አንዱ የሚናገረዉን መልሶ መናገር አስፈላጊነቱ ብዙም ስለማይታየኝ፤ ሌላዉ ሰዉ ከሰራዉ የሚል አስተያየት ስላለኝ ነዉ” የሚል መልስ ሰጥተው ነበር።
ከሁሉም በላይ እንደ ዋና ምክኛት ያቀረቡትና “ሦስተኛ” ያሉት ምክኛት ” … ዋንኛዉ ደግሞ በኢትዮጵያ የፖለቲካዉ አካሄድ፤ ቀድሞ ከማዉቀዉ እና ከማስበዉ አካሄድ ዉጭ እየተጓዘ በመሆኑ ነዉ። የፖለቲካ ባህሉ እጅግ ተቀይሯል። ድሮ በህዝብ ዘንድ ተቀባይነትን ለማግኘት አነሰም በዛ፤ በክርክር በሃሳብ የበላይነት በዉይይት፤ ባይስማሙም ተቀራርቦ በመነጋገር ጥረት ይደረግ ነበረ። አሁን ግን ያ ሁኔታ አይታይም። ሚዲያን ያለአግባብ ኢ-ሞራላዊ በሆነ መንገድ፤ በገፍ በመጠቀም አድማጭን በማደናገር እና የመጡብህ ፖለቲካ ፍርሃትን በማሰራጨት ፖለቲካዉ በጣም ቆሽሿል።» የሚል ነበር።
አቶ በቀለ ይህን ባሉ ሳምንታት ውስጥ በሲያትል ተደረገ በተባለ የኦሮሞ ልሂቃን ስብሰባና ህብረት፣ እንዲሁም “ከአብይ ውድቀት በሁዋላ’ በሚል ጃዋር ባዘጋጀው የዙም ውይይት ላይ ተናጋሪ ሆነው ታይተዋል።
ይህንኑ ተከትሎ የተሰጠው አስተያየት አቶ በቀለ ከተለዩት ፖለቲካና ” ቆሽሿል” ካሉት የሚዲያ አጠቃቀምና የፖለቲካ አውድ ዳግም የተመለሱት ምን አልባትም ለስደት ማመልከቻቸው ግብዓት እንዲሆናቸው በማሰብ ሊሆን እንደሚችል የሚያመላክቱ ሆነዋል።
ይህንኑ አስመልክቶ ያነጋገርናቸው የመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣን ” አቶ በቀለ ወደ አገራቸው ተመልሰው መስራትና በሙያቸው አገራቸውን ማገልገል ይቻላሉ። ምስንም ስጋት ሊገባቸው አይገባም። እንደውም ትብብር ይደረግላቸዋል” የሚል አስተያየት ሰጥተዋል።

