በጉጂ ዞን የምትገኘው ሻኪሶ የበለጸገች ናት። ከርሷ ወርቅ፣ታንታለምና ኤመራልድን ጨምሮ ሰላሳ ሰባት የሚጠጉ የማዕድን ዓይነቶችን ታቅፏል። ቀደም ሲል ሻኪሶ ሀብቷ ከከተማዋ እንዳይወጣ ኮሶን ትግት እንደነበር የሚነገረው በዚሁ የከርሷ ሃብት ሳቢያ ነው። እንቆቅልሹ ሻኪሶንም ሆነ አገርን ሊያስፈነጥር የሚችለውን ይህን ሃብት ለመጠቀም አለማቻሉና በዚህ ቁጭት የሚተጉ መሪዎች መታጣቱ ነው።
እርግጥ አሁን ላይ ጅምሮች ቢኖሩም ሁከትና ጦርነትን የዕለት ጉርስ ያደረጉና “በነጻ አውጪ ካባ” የተሸፈኑ አንጋቾች ጉጂን በማወክ ጅምሩን እየጎተቱ ቆይተዋል። የአካባቢው ነዋሪዎች እንደሚሉት አሁን ላይ የጸጥታው ሁኔታ ከፍተኛ መሻሻል ቢያሳይም ማዕድን ዘረፋ ላይ የተሰማሩ ታጣቂዎች እዛም እዚህም ይላሉ።
መነሻው ጉዳይ የድፍን ጉጂ ሳይሆን በዛው ዞን ስለምትገኘዋ የሻኪሶ ከተማ ነውና በከተማዋ መሬት ቢሮ፣ ገቢዎች ቢሮና ፋይናንስ ቢሮ ያለውን ዓይን ያወጣ ሌብነት፣ ስርዓት የለቀቀ የስራ ስነምግባር፣ በአካባቢ ተወላጅነት ስለሚፈጸም መድልዎ፣ ሕዝብ ስለሚያሰማው ሰሚ ያጣ ሮሮ ሰሚ ካለ በግርድፍ እንደሚከተለው ቀርቧል። በተለይም መሬት ቢሮና ገቢዎች ላይ እናተኩራለን። ለዚህ ጽሁፍ ምላሽ ያለው ማናቸውም የአስተዳደሩ ኃላፊ ወይም ይመለከተኛል የሚል ካለ ዝግጅት ክፍሉ ያስተናግዳል።
ሻኪሶ ኑ ወደ ልቅሶ ቤት እንሂድ፤ መሬት ቢሮ ገሃነብ የሆነባቸው ተገልጋዮች
በኦሮሚያ የተያዩ ዞኖችም ሆነ የክልሉ ቢሮዎች ሙስና “በአዋጅ የተፈቀደ ይመስላል” ይላሉ ቅሬታ አቅራቢዎች። ኦሮሚያ ብቻ ሳይሆን በአገሪቱ ሌብነት የስራ መመሪያ የመሰለበት ” የይዞ መገኘት ነው” እሳቤ ሰላባዎች እልፍ ናቸው። እነዚህ አካላት ለሞራላቸው ያደሩ በመካከላቸው ብቅ ካሉ የጠፏቸዋል። ሻኪሶ የተከሰተ ምሳሌ አለ።
የሪፖርቱ መነሻ ኦሮሚያ ስለሆነ እንጂ ሌብነት ሕዝብና መንግስት መካከል ሊፈርስ የማይችል የልዩነት ግንብ እየገነባ መሆኑ ተደጋግሞ የሚገልጽና ሰሚ ያጣ ጉዳይ ነው። ከጥበቃ ጀምሮ እስከ ኃላፊ ተቧድነው ሕዝብ የሚግጡ ተቋሞች አሉ። ሰሞኑን ገዢው ፓርቲ ባወጣው መግለጫ “እታገለዋለሁ፣ አጠራዋለሁ” ያለው ይህ የከፋ ችግር ይቀረፍ ይሆን የሚለው የበርካቶች ጥያቄ ነው።
በጎጂ ዞን የምትገኘው ሻኪሶ ወርቅ፣ታንታለም፣ ኤመራልድና ሌሎች ውድ ማዕድናት ትታወቃለች። በሌላ በኩል ደግሞ ከአቀማመጧ አንጻር የኮንትሮባንድ ኮሪዶር ናት። በሻኪሶ ከሚታወቁት ማዕድን ላይ ከተሰማሩ ኩባኒያዎች ውጪ ህገወጥ ማዕድን ቦጥቧጮች በቡድን የተቀራመቱት፣ መንግስትም ሆነ ሕዝብ ከቀረጥ ዱንቡሎ የማያገኙበት የማዕድን ማውጫዎችም እንዳሉ ምስክሮች ይናገራሉ።
በጉጂ ዞን ብረት አንስተው የሚንቀሳቀሱ የኦነግ ሸኔ ታጣቂ አመራሮችን ጨምሮ ህገወጥ የቁፋሮ የአካባቢው አስተዳደሮችና የጸጥታ ኃላፊዎች የሚሳተፉት ሌብነት እንደሚፈጸም እነዚሁ ምስክሮች ይጠቁማሉ። በዚህም ህገወጥ ዝርፊያ በሚገኝ ሃብት የተነሳ የሻኪሶ ከተማ ወስጥ በሰፊ የኑሮ ልዩነት የሚገለጹ ነዋሪዎች ይታያሉ። መኖር ግራ ያጋባቸውና ከልክ በላይ የሚኖሩ ዜጎች!
መሬት ቢሮ
በሻኪሶ መሬት ቢሮ በ”ሲዖል” ይመሰላል ። ጉዳይ ለማስፈጸም ወደ መሬት ቢሮ ለመሄድ የሚፈልጉ የሻኪሶ ነዋሪዎች “ለቅሶ ቤት ልሂድ/ እንሂድ” ነው የሚሉት። ባለፈው ሳምንት ሰኞና ማክሰኞ በተካሄደ ግምገማ ላይ “መሬት ቢሮ ለነዋሪው የሲዖል ቢሮ ሆኗል” በሚል በአስተዳደሩ ሰራተኞች ተገምግሟል። ነዋሪዎች እንደሚሉት በሻኪሶ የመሬት ቢሮ አገልግሎት ከሌብነት በዘለለ ህግና ስርዓት የከሸፈበት፣ እንደ ድራማ ድርሰት የሚመስል ወንጀል የሚፈጸምበት የስራ ክፍል ነው። ከልካይም ተቆጣጣሪ የለውም። እንደውም በተዋረድ ዝርፊያ የሚፈጸምበት ይመስላል።
ከቅርብ ምስክሮች እንደተሰማው ወር ባልሞላው ጊዜ ውስጥ ከንቲባው አቶ ፌርዶምሶ ኢደማ አንድ ባለሃብት ይዘው በመሄድ ቦታ ሊያስረክቡ በተዘጋጀው ሰነድ ላይ ወዳለው ስፍራ ያመራሉ። ሲደርሱ ኢንቨስተሩ የተመሩት መሬት የለም። የተሰጣቸውን የመሬቱ ማስረጃ እጃቸው ላይ ሲቀር መሬቱ አየር ላይ ተቸብችቧል።
ነገሩ እንዲህ ነው። አንድ ባለሃብት ለልማት መሬት ይወስዳሉ። መሬቱን ከመረከባቸው በፊት ለሚነሱት ሰዎች ምትክ መኖሪያ እንዲያሰሩ ይታዘዛሉ/ መመሪያ ነው/ አሰርተው ከጨረሱ በሁዋላ ሁሉንም አሟልተው በመጨረሳቸው ከንቲባው መሬታቸውን ሊያስረክቧቸው ወደ ስፍራው ይሄዳሉ።
ባለሃብቱ፣ ከንቲባውና የሚመለከታቸው ተሰባስበው የተባለው ቦታ ላይ ሲደርሱ መሬቱ የለም። መሬቱ ለሌላ ሰው ተሽጦ፣ ህጋዊ ሰነድ ተዘጋጅቶለት ስንብት ተደርጎለታል። በስፍራው ታዛቢ የነበሩ እንደሚሉት ይህ እስከተጻፈ ድረስ መሬቱን አየር በአየር የሸጠው ኃላፊም ሆነ ግብር አበሮቹ ምንም እርምጃ አልተወሰደባቸውም። መሬቱን ለተነጠቁት ባለሃብትም አልተመለሰም።
በሻኪሶ አስተዳደር የመሬት ቢሮ አይን ያወጣ፣ በፊት ለፊት ቢሮ ውስጥ “ገንዘብ አምጣ” የሚባልበት፤ ከሞራልም ሆነ ከስራ ዲሲፒሊን አንጻር ስም ሊሰጡት የሚያዳግት ሌብነት የነገሰበት ቤት ነው። ለዚህም ይመስላ አገልግሎት ፈላጊዎች ” ለቅሶ ቤት እንሂድ” ማለትን መርጠዋል። ራሱ አስተዳደሩ ባደረገው ግምጋማ ” ሰው የሚቃጠልበት ሲዖል ነው” በሚል ግምግሞታል።
አንድ ባለ ጉዳይ የከተማዋ ነዋሪ የራሳቸውን መሬት አስመልክቶ ካርታ ለማሰራት ሄደው እዛው ቢሮ ውስጥ “ገንዘብ አምጪ” ተባሉ። እኚሁ እናት አልገባቸውምና ጥያቄ ሲያበዙ “ከሚያውቅ ሰው ጋር ኑ” በማለት ያሰናብቷቸዋል። ቤት ከሄዱ በሁዋላ የገጠማቸውን ሲናገሩ ” ጉቦ ነው” ተባሉ። እኚህ እናት ጉቦ ሰጥተው ሰላማያውቁ በመፍራት የተጠየቁትን በሌላ ሰው አማካይነት አደረጉ። ከዛም ካርታቸውን ወሰዱ።
ግምገማውን አስመልክቶ መረጃ የሰጡ እንደሚሉት ዞኑ ከሃያ ሶስት ዞኖች ውስጥ በሰራ አፈጻጸሙ ራሱን ገምግሞ ሃያ አንደኛ ደረጃ ይዟል። ሰራተኞችም አለቆችን ጨምሮ ዝቅተኛ የስራ አፈጻጸም አስመዝግበዋል። ይሁን እንጂ እስካሁን ያለ አንዳች ለውጥ “ሲዖል” ሲል ራሱን የገመገመው አስተዳደር እዛው “ሲዖል” ውስጥ ስራውን ቀጥሏል። ሕዝብም “ለቅሶ እንሂድ” እያለ ማንባቱን ቀጥሏል። አሁን ጥያቄው ” ውስጤን አጠራለሁ፣ አነጻለሁ” ያለው መንግስት የት ነው? ይቻለዋል ወይ? የሚለው ነው። ሕዝብ “መንግስት የት ነህ?” እያለ በቀን በቀን እያነባ ይማጸናል ሰሚ የለም። አማራጭም ስለሌለው እዛው ” ሲዖል” ይመላለሳል። እስከመቼ በዚህ መልኩ ይቀጥላል። እስከመቼ? ሻኪሶ ብቻ ሳይሆን በሁሉም ስፍራ!!
ሻኪሶን ከቀድሞዋ ቡራዩና አዲስ አበባ ዙሪያ ያሉ አስተዳደሮችን ጋር በማመሳሰል መረጃ የሰጡ እንዳሉት አንድ መሬት ከአንድ በላይ ለሆኑ ሰዎች ማደል፣ ፕላን እያሳቱ ሳይት ማጽደቅ፣ ሃብት ያላቸው ሰዎች ቅጥር እንዳይነካ መንገድ ማንጋደድ፣ በከተማቸው የመሬት ቢሮ የጠራራ ጸሃይ የ”ጽድቅ ስራዎቹ” ናቸው።
በዚሁ ፕላን የማሳትና የመደለዝ ስራ ከተማዋ መካከል የሚሳቅበት ቅርጸ ቢስ ፎቅ ምሳሌ እንደሆነ የሚናገሩ እንደሚሉት ፕላን እየተደረበ የሚሰጠው ገንዘብ ለመቀበል ነው። እጅግ የተማረሩ እንደሚሉት በመሬት ቢሮ ውስጥ ህጋዊ ነገር ቢሮው፣ የቢሮው ስም፣ በቢሮ ውስጥ ያሉት መጠቀሚያ ነገሮችና ሰዎች እንጂ ሌለው ሁሉ በቃል የሚገለጽ አይደለም።
ገቢዎች ቢሮ
የገቢዎች ቢሮም በተመሳሳይ ሌብነቱ መረን የወጣበት አንዱ የአስተዳደሩ መገለጫ ነው። ቢሮ ውስጥ ሆነው ግብር ላይ መደራደር፣ የተመደበ ግብርን በመቀነስ ገንዘብ መቀበል የተለመደ ተግባር ነው። ተገልጋዮች ባንክ ሄደው ገንዘብ እንዲከፍሉ የገንዘብ ማስገቢያው ደረሰኝ የሚቆርጡ በግልጽ የባንክ አካውንታቸውን በመስጠት ጉቦ ይወስዳሉ።
ይህ አሰራር ያማረራቸው ተገልጋዮች ግብር እንዲቀነስላቸው እዛው ቢሮ ውስጥ በገሃድ የሚቀርብላቸውን ጥያቄ ከመመለስ ውጭ አማራጭ እንደሌላቸው ይናገራሉ። ተማረው የንግድ ፈቃድ የመለሱም አሉ። እነዚህ ወገኖች ድንጋጤያቸውና ተስፋ መቁረጣቸው የሚጨምረው ” ሰው በግል ባንኩ በኩል ጉቦ እንዲሰጠው፣ እዛው መንግስት በሾመው ወንበርላይ በመንግስት ቢሮ ውስጥ ተቀምጡ ይጠይቃል?” በሚል ሲያስቡ ነው።
ከዛሬ ሁለት ዓመት በፊት ካደጉ ከተሞች መካከል የተመደበችው ሻኪሶ ከዚያን ጊዜ አንስቶ የበጀት ድጎማ የላትም። እንደ አቻዎቿ ከተሞች “አድጋለች” ስለተባለ በበጀት ራሷን መቻል ግድ ነው። ዋና የመነግስት ተቋማት ገቢ ግብር እንደመሆኑ ሻኪሶም ግብር ትሰበስባለች። የግብር አሰባሰቡ ሌብነት የሰፈነበት በመሆኑ ከተማዋ ደሞዝ ለመክፈል ወር በተገባደደ ቁጥር ዘመቻ ለማድረግ ትገደዳላች።
“ደሞዝ የለም። ገኢ ሰብስቡ” የሚለው መፈክር በየወሩ የተለመደ መሆኑን የሚናገሩ የሌሎች ሴክተር ሰራተኞች “ሻኪሶ ገቢዋን ለከርሳሞች አስረክባ በየወሩ የደሞዝ ማሟያ ግብር ስብሰባ ዘመቻ ትጠራለች” ሲሉ የችግሩን ግዝፈት ያሳያሉ።
“ሃላ የሮ”
“ሃላ የሮ” ማለት የጊዜያዊ ሁኔታ በሚል ሰዎች ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ ለጊዜው የሚታሰሩበት አግባብ ወይም አሰራር ነው። አካባቢው የታጠቁ ኃይሎችንና የህቡዕ ተባባሪዎቻቸውን ለመቆጣጠር በሚል እንደወጣ የሚነገርለት ይህ አሰራር የሚያስራቸው ሰዎች፣ በጊዜ ገደብ ፍርድ ቤት አይቀርቡም። አቃቤ ሕግ ፈጥኖ ክስ እንዲመሰርትባቸው ግዳጅ አይጥልም፣ የተለመደው የዋስ መብት አይሰጥም። በጥቅሉ እንደማንኛውም ታሳሪ ህግ ተፈጻሚ አይደረግበትም።
አንድ የዞኑ የጸረ ሙስና መኮንን ሻኪሶ በገሃድ የሚፈጸመውን ሌብነት ለመግራት ላይ ታች ማለት ሲጁመሩ፣ የሌቦቹ መንደር ተንጫጫ። ወዲያው መላ ሲፈለግ “ሃላ የሮ” ተገኘ። የጸረ ሙስና መኮንኑ ሃላ የሮ ተቆለፈባቸው።
ምን ጥፋት እንደሰሩ ሳያውቁ ዋስትና ተከልክለው፣ ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ “ሃላ የሮ” ተብለው ታስረው ከረሙ። በመጨረሻም የደቡብ ኦሮሚያ የጸረ ሙስና ኮሚሽን ከሃገረማሪያም መቀመጫቸው በመምታት እስረኛውን አስፈቱዋችውው። ሻኪሶን ራሱ አስተዳደሩ ” ሕዝብ የሚቃጠልበት ሲዖል ነው” ያለው ትክክል የሚሆነው እዚህ ላይ ነው። “ስምን ማን ያወጣዋል” እንዲሉ!!
በአካባቢው የተወላጅነት እሳቤና ተወላጅነት ላይ የተመሰረተ ምደባ፣ ልዩ እንክብካቤ፣ ቡድን፣ ወዘተ እንዳለ የሚናገሩ እኚህ የጸረ ሙስና መኮንን ለምን በዚህ ደረጃ ሊጨከንባቸው እንደተፈለገ አይገባቸውም።
ከሌላ የኦሮሚያ አካባቢ የመጡ ” ምንም እንኳን ኦሮሞ ብንሆንም እንገፋለን” ሲሉ ቅሬታ ያሰማሉ። አክለውም እኚህ የጸረ ሙስና መኮንን በተወላጅነት የአካባቢው ሰው ቢሆንም በዚህ ደረጃ የተጠቁት ሌብነትን በመቃወማቸው መሆኑ በቡድን ዝርፊያ ስለመኖሩ ማሳያ ነው።
እንደ በረከት
በሻኪሶ ነዋሪዎች የሚያመሰግኑት ነገር ቢኖር ሰላምን ነው። “ምህረት የበዛባት ከተማ” ይሉዋታል። በጉጂ ዞን ታጣቂዎች በብዛት የተራመሱበት ስለነበር ዙሪያዋ የሚያስፈራው ሻኪሶ የስጋቱን ያህል ሳትናጥ መሽቶ ስለሚነጋላት ለነዋሪዎቿ ይህ እንደ በረከት ነው። ያው “ሳይደግስ አይጣልም” እንዲሉ።
በሻኪሶ አንድ የሚጠቀስ ችግር ቢኖር የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የፖለቲካ አጀንዳ መድፊያ መሆኑ ነው። አዲስ ጉዳይ ሲታሰብ ትምህርት ቤቱ ውስጥ ይደፋል። ከዛም ትምህርት ቤቱ ውስጥ ኦሮሞም ቢሆን ከሌሎች አካባቢ የመጡትን በመግፋት ረብሻ ይነሳል። በዚሁ ሁከት ሳቢያ ትምህርት ለአንድና ሁለት ወር ይዘጋል። ይህ ቢያንስ በዓመት አንዴ የተለመደ ነው። ከዚህ ውጭ ሕዝቡ ያለ ችግር የሚኖርበት መሆኑን ነዋሪዎች ይመስክራሉ።
እንደ መውጪያ
ሻኪሶን አስመልክቶ በስም፣ በኃላፊነትና የተፈጸሙ የሌብነት ወንጀሎችን በመዘርዘር ነው ቅሬታ አቅራቢዎቹ የተናገሩት። “ጫያ” በሚሰኘው የኦሮሚኛ ድንገት የሚቀረጽ ፕሮግራም ላይ በጥልቀት ባይሆንም ችግሩ መቀረቡን እነዚሁ ቅሬታ አቅራቢዎች ያስታውሳሉ። ኝ የተወሰደ ማሻሻያ የለም። ለምን? ቢባል የተለመደው በመላው አገሪቱ ” በተዋረድ ተቧድነህ ብላ” የሚባለው አሰራር እንጂ ሌላ ስም ሊሰጥ አይችልም። ራሱ አስተዳደሩ ከሳምንት በፊት ” ለነዋሪው ሲዖል ሆነንበታል” በሚል የገመገመውን ቢሮ “ሲዖል” ያደረጉትን ሌብች አቅፎ እየመራ ነው።
“የሚሰማ ካለ” በሚል ምሬታቸውን የገለጹት የከተማዋ ነዋሪዎች፣ በከተማዋ ሌብነት ግልጽ፣ ሃፍረት የማይታይበት፣ መመርመር ለሚፈልጉ ማናቸውም አካላት ሊሸሸግ የማይችል የአደባባይ ሃቅ እንደሆነ ያስረዳሉ።
ሕዝቡ የማይፈራ፣ ግልጽ የሚናገር በመሆኑ ፍትህን ለማስፈን ፍላጎት ያላቸው የመንግስት ተወካዮች ቢመጡ ሊያፍረጠርጡት ዝግጁ መሆናቸውን መረጃውን ያካፈሉን አስታውቀዋል። “መንግስት ሆይ ድረስ” ከማለት ውጪ ሌላ አማራጭ የሌላቸው ነዋሪዎቹ ” ምን አለበት ግን መንግስት አንድ ነገር ቢፈቅድ” ሲሉ ይጠይቃሉ። ” መንግስት ቢያንስ ከተሞች ራሳቸው ከንቲባዎቻቸውን ቢመርጡና ቢሰይሙ” ይህ ለሻኪሶ ነዋሪዎች ቅዠት ሳይሆን ትክክለኛ ጥያቄ ነው። በከተማቸው የሚከበሩ፣ የሚፈሩና ሞራል ያላቸውን መሪ ይሰይሙ ነበር።

