ይህንን የብድር ዓይነት አስመልክቶ ትናንት የለጠፍኩት ማሳሰቢያ ላይ ባንኩ ውስጥ ከሚሠሩ ሠራተኞች ሀሳቤን አብራርቼ እንድገልጽ ተጠይቄያለሁ። በዚህ ጥያቄ መነሻ ሀሳቤን በመጠኑ እንደሚከተለው አብራራለሁ።
የኢትዮጵያ ልማት ባንክ #የሊዝ_ፋይናንሲንግ የብድር ዓይነት 20:80 የሚል የብድር ቀመር ይከተላል። ይህም ማለት የሚያስፈልገውን ለካፒታል ዕቃ መግዢያ የሚሆን ገንዘብ ሙሉ ለሙሉ ባንኩ የሚያቀርብ ሲሆን፣ የዚያን የካፒታል ዕቃ 20% የሚሆን ያህል ገንዘብ ለመንቀሳቀሻ ካፒታል (Working Capital) እንዲሆን ባለሀብቱ ያቀርባል ወይም ያስይዛል። ይህ የWorking Capital በባንኩ በኩል በሊዝ ፋይናንሲንግ የተገዛው ማሽን ሲተከል ለጥሬ-ዕቃ መግዢያ የሚለቀቅ ነው።
ነገር ግን በእኔ ምልከታ በዚህች የWorking Capital መጠን አናሳነት ምክንያት ተተክለው ሥራ መጀመር አቅቷቸው የቆሙ ወይም ሥራ ጀምረው ወደፊት መጓዝ ያቃታቸውና የከሰሩ ፋብሪካዎች በርካታ ናቸው። በዚህም ምክንያት ብድራቸውን መክፈል አቅቷቸው ከባንኩ ጋር የሐራጅ ውዝግብ ውስጥ የገቡ ተቋማት እንዳሉ አውቃለሁ።
የዱቄት ፋብሪካ፣ የመኖ ፋብሪካ፣ የወተት ፋብሪካ እና ሌሎችም የፋብሪካ ዓይነቶች በዚህ የWorking Capital ማነስ ችግር ምክንያት ፋብሪካዎቻቸውን ለኪሳራ ባለሀብቶቹንም በእድሜያቸው ያፈሩትን ጥሪት ሊበላ አሳሳቢ አደጋ እንደተጋረጠባቸው አስተውያለሁ። ይህ አካሄድ እርምትና ማስተካከያ ይፈልጋል። ችግሩን ከስሩ አጣርቶ ማረሚያ ማድረግ ያስፈልጋል።
በሊዝ ፋይናንሲንግ ብድር በማግኘቱ ብቻ ተደስቶ ፋብሪካ ተክሎ ለማምረት ጓጉቶ ነገር ግን ማምረት አቅቶት ባለሀብቱ ሲጨነቅ ማየት ያሳዝናል። የችግሩ ስር ያለው #የWorking_Capital_ማነስ ላይ ነው።
በዚህ ዘመን ማሽን መትከል ብቻውን በቂ አይደለም። እንዴት ፋብሪካውን ተወዳዳሪ አድርጎ እንደሚመራ ካልታወቀ ትርፉ ጭንቀትና ኪሳራ ነው።
በእኔ እይታ በአሁኑ ወቅት በአንዳንድ የኢንዱስትሪ ዘርፎች ሀገራችን #ከበቂ_በላይ_ፋብሪካ አላት። ፋብሪካዎቹ ግን በበቂ የማምረት ዓቅማቸው ስለማይሠሩ ከስረው እና ተዘግተው ቆመዋል። ይሄ ለሀገር ትልቅ ብክነት ነው። በዚህ ምክንያት በአንዳንድ የፋብሪካ መስኮች አዲስ ማሽን በውጭ ምንዛሪ ማስገባት አላስፈላጊና የውጭ ምንዛሪ ማባከን ነው። ያሉት መች ተሠራባቸውና?!
ለመሆኑ ለአንድ ፋብሪካ የሚያስፈልገው የWorking Capital መጠን ስንት ነው? የWorking Capital መጠን እንዴት ይተመናል? የሁሉም ፋብሪካ የWorking Capital መጠንስ ከካፒታሉ 20% ነው ወይ?
#Working_Capital የጥሬ-ዕቃ መግዢያን፣ የዱቤ ሽያጭ መጠንን፣ ለአቅራቢዎች የሚከፈል ቅድመ-ክፍያን፣ የደሞዝ ነዳጅ እና የኤሌክትሪክ ወጪዎችን ታሳቢ በማድረግ የሚሰላ ነው።
ለመሆኑ አንድ ፋብሪካ ምርት ሳያቋርጥ፣ ዋጋው ሳይዋዥቅና ገበያው ሳይረበሽ እንዲሠራ ምን ያህል የጥሬ-ዕቃ በክምችት መያዝ አለበት? ይህ ከኢንዱስትሪ ኢንዱስትሪ የሚለያይና እንደ ድርጅቱ የቢዝነስ ሞዴልና ዓቅም የሚለያይ ነው።
የኢትዮጵያ ልማት ባንክ የሊዝ ፋይናንስ ዋና ችግር የWorking Capital መጠንን ለሁሉም ፋብሪካ የካፒታሉን 20% ያህል ነው ብሎ ማሰቡ ነው። ይሄ ትልቅ ስህተት ነው። ይህ ታሳቢ ብዙ ፋብሪካዎችን ለችግር እና ኪሳራ ብሎም ለሐራጅ እየዳረገ ያለ ዋና ችግር ነው።
የWorking Capital ፍላጎት መጠን ከኢንዱስትሪ ኢንዱስትሪ ይለያያል። አንዳንድ ፋብሪካ ከማሽን ወጪ ይልቅ የመሥሪያ ካፒታል ፍላጎቱ ብዙ ነው።
ለምሳሌ :- የመኖ ፋብሪካ ማሽንን ከ20-30 ሚሊየን ብር በሚደርስ ወጪ መትከል ይቻላል። አዋጭ በሆነ መንገድ በቂ ጥሬ-ዕቃ ገዝቶ መኖን አትራፊ በሆነ መንገድ ለማምረት ግን 200 ሚሊየን ብርም አይበቃም። ካስፈለገ ዝርዝሩን ቀርቤ አስረዳለሁ።
ለዱቄት ፋብሪካም ተመሳሳይ ነው። የግብርና ግብዓት ለሚጠቀሙ ኢንዱስትሪዎች በቂ ጥሬ-ዕቃ በመኸር ጊዜ ዋጋው ዝቅ ሲል መያዝና መሥራት ይጠይቃል።
ለፕላስቲክ ኢንዱስትሪም የፔትሮሊየም ዋጋ ውጣ ውረድን ተከትሎ የጥሬ-ዕቃ ክምችት አያያዝን መመጠን አስፈላጊ ነው።
ታድያ ለዚህ በቂ Working Capital ያስፈልጋል።
የብዙዎቹ የሀገራችን ኢንዱስትሪዎች ችግር #የድሃ_አስቤዛ በሚመስል የWorking Capital መጠን ለመሥራት መሞከር ነው። ይህ #አክሳሪ መንገድ ነው።
ለእንደዚህ ዓይነቶቹ ኢንዱስትሪዎች 80% ለWorking Capital 20% ለማሽን እንጂ አሁን ያለው መንገድ አያሠራም።
የባንኩ ሰዎች ይህንን መሰል ችግሮች አቅርቤ እንዳስረዳ ከፈለጉ ቀርቤ ለማስረዳት ፈቃደኛ ነኝ።
(Via:- Get Toughe Zer)

