ሰሞኑን የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት የመልቀቂያ ፈተና ውጤት ይፋ መሆኑን ተከትሎ በርካታ አስተያየቶች እየተደመጡ ነው። ከእነዚህ አስተያየቶች መካከል በአንዳንድ የመንግሥት ተቃዋሚ ማህበራዊ ሚዲያዎች ጎላ ብለው የተነሱት፣
፩. “ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ የጣላቸውን ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ያነሳዋል!”
፪. “ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ስልጣን ልቀቅ!”
፫. “ህውሓት/ኢህአዴግ ማረን!”
፬. “የሴክተር ሪቪው አብዮት እየመጣ ነው!”
፭. “ኤርትራናይዜሽን ኦፍ ኢትዮጵያ”…ወዘተ የሚሉት ይገኙበታል።
እንደ እውነቱ ከሆነ በእነዚህ ከላይ የተሰጡ አስተያየቶች ላይ ራሱን የቻለ ዘለግ ያለ መጣጥፍ የያዘ ምላሽ መስጠት ይቻላል። ለዛሬው ይህንን ለማድረግ የተሻለ ጊዜ አላገኘሁም። ነገር ግን እንደ አንድ የኢትዮጵያን የትምህርት ፍልስፍና ፣ ርዕዮት፣ ፍኖተ-ካርታ ፣ ፖሊሲ እና አፈጻጸም ላለፉት 23 ዓመታት በቅርበት (በአመራርነት ጭምር) እንደተከታተለ እና በመጽሐፍ ጭምር እንደከተበ ሰው ምንም አለማለት የጥፋተኝነት ስሜት እንዲሰማኝ አድርጓል። እንደዚህ አይነት በነሲብና እንደወረደ የሚወረወር አስተያየት እየተመለከቱ ዝም ማለት እርግጥም የሞራል ጥያቄ ያስነሳል።
እናም ይህን ድርጊታቸውን በማጤን በጣም ጥቂት ለማለት እገደዳለው። በተለይም ከትምህርት ስርዓቱ እና አመራር ጋር በተያያዘ “ህውሓት/ ኢህአዴግ ማረን” ለሚሉ ጫፍ የረገጡ ዘረኞች፣ ፈሪሳውያን፣ ፣ደናቁርት እንዲሁም በፍጹም ጥላቻና ቂም ቋጠሮ ለታወሩ አካላት ወደ ኋላ እና ወደፊት እየሄድኩ ትንሽ ለመናገር እፈልጋለሁ።
እዚህ ላይ በሰርጥ ማስገባት የምፈልገው አንድ ቁምነገር አለ። ይህም አሁን ያለው የትምህርት ስርዓት ሙሉ በሙሉ እኔ የምፈልገው አይነት ነው እያልኩ አይደለም። ከዚህ በተጨማሪም እንደ ድሮው በቅርበት እያንዳንዱን ቀዳዳ ስለማላውቃቸው ዝርዝር አፈጻጸሙን እና የማስፈጸም አቅሙን መናገር አልችልም። የማስፈጸም አቅም ሲባል አመለካከት እና እውቀት፣ ጥራት እና ዘመናዊ አሰራር እንዲሁም ውጤታማ አደረጃጀትን መፈተሽ የሚጠይቅ ስለሆነ በዚህ ዙሪያ የተሟላ መረጃ የለኝም። በአጭሩ በአደባባይ ከተገለጡት ውጭ አዳዲስ ጥናቶች አሉኝ ብዬ አልመጻደቅም። ነገር ግን በተቻለ መጠን ጉዳዩን መዋቅራዊ በሆነ መንገድ እንዲሁም በኢትዮጵያዊ ስሜት ለማየት እና ለማሰላሰል ሞክሬያለሁ። አገራዊ አቅጣጫ እና የብሔራዊ ራዕይ አመልካቾች መሆን እና አለመሆናቸውን ግራ እና ቀኝ ፣ ትላንት እና ዛሬን መሰረት በማድረግ ለመመርመር ሞክሬያለሁ።
እነሆ ምልከታዬ፣
፩ኛ) የትምህርት ስርዓቱ አመራርን በተመለከተ
የዘመነ ህውሓት/ኢህአዴግ የትምህርት አመራር ምደባን ለዘነጋችሁ ሰዎች ከአንደኛ ደረጃ ጀምሮ እስከ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ድረስ ምክትል ርዕሰ መምህር፣ ዋና ርዕስ መምህር፣ የዲፓርትሙንት ኃላፊዎች፣የቡድን መሪ ፣ የመምሪያ ኃላፊ፣ የጽህፈት ቤት ኃላፊ፣ አንዳንድ ኤክርፐርቶች፣ የኮሌጅ አመራሮች …ወዘተ የሚመደቡት በፓርቲ አባልነት ብቻ ሳይሆን በገዥው ፓርቲ ታማኝነት ጭምር ነበር። ለምሳሌ በአንድ ወቅት ብዙ ገንዘብ የተበላበት የአዲስ አበባ መስተዳድር የሁሉም ክፍለ ከተማ ትምህርት መምሪያ ኃላፊዎች 90 በመቶ የህውሓት ካድሬዎች ነበሩ (ባለቤት አልባ ከተማ መጽሐፍን ያንብቡ)።…አሁን ያለው የትምህርት አመራር እንደዛ ነው? እንደዛ ከሆነ ንገሩን እና እንቃወም! አብረናችሁ እናውግዝ!
፪ኛ). የትምህርት አደረጃጀት በተመለከተ
የዘመነ ህውሓት/ኢህአዴግ የትምህርት አደረጃጀት ማለትም አንደኛ ደረጃ እስከ ስምንት፣ ሁለተኛ ደረጃ ማጠናቀቂያ 10ኛ ክፍል፤ የመጀመሪያ ዲግሪ ማጠናቀቂያ ለብዙዎቹ የትምህርት ዘርፎች 3 ዓመት መደረጉ “ትውልድን ገዳይ” ተብሎ ህዝባዊ ተቃውሞ ተነስቶበታል። ተቃውሞ መነሳቱም ትክክል ነበር።… ዛሬ ይህ የትምህርት አደረጃጀት ነው ያለው? አይደለም። መዋዕለ ህጻናት አለ፣ አንደኛ ደረጃ (1-6) ሆኗል፣ መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ (7-8) ሆኗል፣ ሁለተኛ ደረጃ (9-12) ወደነበረበት ተመልሷል። የመጀመሪያ ዲግሪም ወደ አራት አመት ተመልሷል። ታዳያ የነበረን የህዝብ ቅሬታ ተመልክቶ ወደ ነበረበት መመለስ ነው የሴክተር ሪቪው አብዮት የሚያስነሳው? ትውልድ ገዳይ የሆነው?
፫ኛ) የዩንቨርስቲ ተማሪዎች የመማር ፍላጎት እና የትምህርት ጥራት በተመለከተ፣
በኢትዮጵያ ውስጥ ባሉ ዩንቨርስቲዎች በሙሉ የፓርቲ መዋቅር ተዘርግቶ እና የህውሓት፣ የብአዴን፣ የኦህዴድ ክትትል ኃላፊዎች ተመድበው ተማሪዎቹን ሲመለምሉ እና ሲያደራጁ ነበር። ተማሪዎች ትምህርታቸውን አጠናቀው ከተመረቁ በኋላ በቅድሚያ የመንግሥት ስራ የሚቀጠሩት የፓርቲ አባላት ነበሩ። ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና “ስራ ለመያዝ GPA 4 ነጥብ ከሚሆን በኢህአዴግ ፓርቲ ግምገማ 2 ነጥብ ማምጣት ይሻላል” የሚል አገላለጥ ነበራቸው። ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና ልክ ነበሩ። ሌላው ቀርቶ በአንድ ጊዜ ከ3ሺህ በላይ የዩንቨርስቲ መምህራን ሲቀጠሩ ምልመላውን የሰራው እና ያጸደቀው እኔ እሰራበት የነበረው አራት ኪሎ የሚገኘው የኢህአዴግ ቢሮ ነበር። (ባለቤት አልባ ከተማ መጽሐፍን ያንብቡ)… ዛሬ እንደዚህ ነው? ከሆነ ንጉሩን እና እናውግዝ!
፬ኛ) የከፍተኛ ትምህርት የቅበላ ነጥብ በተመለከተ፣
በዘመነ ኢህአዴግ ከጥራት ብዛት በሚል መርሆ ከ600 ከሚታረም የሁለተኛ ደረጃ መልቀቂያ ፈተና እስከ 200 ድረስ ያመጡ ተማሪዎች ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተመድበዋል። የከፍተኛ ትምህርት መምህራን መመዘኛ በሚያሳልፉት ተማሪ ይመዘናል ተብሎ ስማቸውን በአግባቡ የማይጽፉ በገፍ እንዲያልፉ ተደርጓል። የተመራቂ ተማሪዎች የመውጫ ፈተና የሚባል ነገር አልነበረም። … ዛሬ እንደዚህ ዓይነት የትምህርት ሁኔታ አለ?
፭ኛ) የተማሪዎች የሙሉ ቀን ትምህርት እና የምገባ ስርዓትን በተመለከተ፣
እኔ እስከማስታውሰው ድረስ በዘመነ ህውሓት/ ኢህአዴግ የተማሪ ምገባ የሚባል ስርዓት አልነበረም። በአሁን ሰዓት በአንዳንድ ክልሎች የትምህርት ቤት የምገባ ስርዓት መጀመሩን ሰምተናል። እኔ ባለኝ መረጃ በአዲስ አበባ ከ1ሚሊዮን በላይ ተማሪዎች ፤ በኦሮሚያ ክልል ከ9 ሚሊዮን በላይ ተማሪዎች የምገባ ስርዓት ውስጥ ገብተዋል። የሁለቱ ብቻ ከ10 ሚሊዮን በላይ ይሆናል። ይህም የፈረቃ ትምህርትን በማስቀረት ተማሪዎች ሙሉ ቀን ትምህርት ቤታቸው እንዲቆዩ ያደርጋቸዋል። ያለምንም መጠራጠር የእነዚህ ልጆች ቤተሰቦች በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ናቸው። ይሄ መሰረታዊ ለውጥ አይደለም? ማንስ ቢሆን ይህንን የማጣጣል ሞራል ይኖረዋል?
፮ኛ) አዳሪ ትምህርት ቤትን በተመለከተ
በዘመነ ህውሓት/ኢህአዴግ አይደለም የመንግሥት አዳሪ ትምህርት ቤት ፤ የሚኒስትሪ ውጤትን ማዕከል አድርገው የተቋቋሙ ስፔሻል ክፍሎች እንኳን እንዲፈርሱ ተደርጓል። በእርግጥ በአንዳንድ ክልሎች ኢፍትሐዊ እና በታቀደ መንገድ የተቋቋሙ መንግስት እና ገዥው ፓርቲና ኢንዶውመንቶቻቸው የሚደግፋቸው አዳሪ ትምህርት ቤቶች ነበሩ። የታየው የልዩነት ውጤትም ግልጽ እና የህዝብ ቅሬታ የፈጠረ ነበር። (በመለስ ልቃቂት መጽሐፍ ውስጥ “ቃላሚኖ” የሚለውን ምዕራፍ ያንብቡ)…በተቃራኒው ዛሬ ሁሉም ክልሎች ብቻ ሳይሆን በትምህርት ሚኒስቴር የሚተዳደሩ እና ከመላው ኢትዮጵያ የተውጣጡ ጎበዝ ተማሪዎች የሚማሩበት አዳሪ ትምህርት ቤቶች እየተቋቋሙ ነው። ይህንን ለውጥ በኢትዮጵያዊነት ስሜት ውስጥ ሆነን ብናየው፣ ብንዳስሰው፣ ብንቀምሰው ፣ ብናሸተው፣ ብናስተውለው ተስፋ የሚሰጥ አይደለም? እስቲ አስቡት በሁለተኛ ደረጃ አዳሪ ትምህርት ቤት ውስጥ ከትግራይ፣ አማራ፣ ኦሮሞ፣ ሶማሌ፣ አፋር፣ ወላይታ፣ ሲዳማ፣ ጋምቤላ፣ ጉምዝ፣ ጉራጌ፣ ስልጤ…ወዘተ መጥተው በአንድ ትምህርት ቤት ውስጥ ሲማሩ፣ አብረው ሲውሉ፣ ሲያጠኑ፣ በአንድ ዶርም ሲያድሩ እንደማየት የሚያስደስት ነገር አለ?
ኤርሚያስ ዋቅጅራ ፌስ ቡክ

