ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የመደመር እሳቤ በተግባር የተገለጠበት የአፍሪካውያን ስኬት መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡
ሁለተኛው የአፍሪካ ካሪቢያን ማህበረሰብ የመሪዎች ስብሰባ በአፍሪካ ሕብረት የመሰብሰቢያ አዳራሽ ተካሄዷል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት አሸናፊነት በሀይል ወይም በጀግንነት ሳይሆን በአንድነት በመቆም ነው።
የዓለም ነባራዊ ሁኔታ እየተለወጠ ባለበት ዘመን የተገለሉ ድምጾች መሰማት አለበት፤ በዚህ አዲስ ዘመን ከተናጠል ወጥተን በአንድ ድምጽ መናገር አለብን ብለዋል፡፡
የአፍሪካና ካሪቢያ ሀገራት ችግሮቻቸውን መፍታት የሚችሉት በመለያየት አይደለም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የአፍሪካ ከካረቢያን ሀገራት ማህበረሰብ ኢኮኖሚያዊ ትብብር መጠናከር እንዳለበት ገልጸዋል፡፡
ዓለም አቀፍ ፈተናዎች ቀጣናዊ ትብብርን የሚፈልጉበት ወቅት መሆኑን በመጥቀስ፤ እንደ እኛ ያሉ ደግሞ ግልጽ ትብብር እንጂ በተናጠል መንቀሳቀስ የለባቸውም ብለዋል፡፡
አፍሪካና የካሪቢያን ሀገራት ማህበረሰብ ያላቸውን እምቅ የተፈጥሮ ጸጋ፣ የቱሪዝም፣ ኢንቨስትመንት አቅም ተጠቅመው ትብብራቸውን ማላቅ እንዳለባቸውም ገልጸዋል፡፡
የመደመር እሳቤ የአላማ አንድነት መፍጠር መሆኑን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ የዓለም ነባራዊ ሁኔታ እየተቀየረ በመሆኑ በአንድ ድምፅ መናገር አለብን ብለዋል።
ኢትዮጵያ በመደመር እሳቤ ከትብብርም በላይ የጋራ ጥረትና የአላማ አንድነትን በማጎልበት ሀሳብ ወደ ተግባር፣ ተግባር ወደ ዘላቂ ለውጥ እየቀየረች መሆኑን ገልጸዋል።
በአፍሪካ ትልቁ የኢትዮጵያ አየር መንገድ አፍሪካን በማስተሳሰር ቀዳሚ የትራንስፖርት ዘርፍ መሆኑን በመጥቀስ፣ የህዝብ ለህዝብ፣ የሀሳብና የኢኮኖሚ ትብብር ፈጥሯል ብለዋል።
ኢትዮጵያ ባለፉት ሰባት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ 48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል ስርዓተ ምህዳሩን መመለስና የስራ ዕድል መፍጠር መቻሏን ገልጸዋል።
የአየር ንብረት ለውጥን ታሳቢ ያደረገው የኢትዮጵያ የስንዴ ምርት ከውጭ ከማስገባት ወደ ዓለም ገበያ የማቅረብ ሂደት ተሸጋግሯል ብለዋል።
ዲጂታል ኢትዮጵያ ለንግድና ፋይናንስ አዲስ መንገድ መክፈቱን ገልጸው፣ሀገር በቀል መፍትሔዎች ኢኮኖሚውን በማሳደግ ራሳችንን አስችሎናል ነው ያሉት።
ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በኢትዮጵያ ፋይናንስ ጉልበትና መስዋዕትነት የተገነባ መሆኑን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ስንተባበር ጠንካራ እንደምንሆን አሳይቷል ብለዋል።
እነዚህ ስኬቶች የመደመር ውጤቶች መሆናቸውን በመጥቀስ፣ ከካሪቢያን ሀገራት ማህበረሰብ ጋር ለጋራ ብልፅግና መተባበር አለብን ብለዋል።
አፍሪካና የካሪቢያን ሀገራት ማህበረሰብ በመልክዓ ምድር የተለየዩ መሆናቸውን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ታሪክ ግን በአንድ አስተሳስሮናል ብለዋል፡፡
በማደግና በማገገም ላይ ያሉ እየተባልን ከምንጠራበት የቋንቋ ጥገኝነት በመላቀቅ የራሳችንን አዲስ ነገር እንፍጠር ብለዋል፡፡
ግብርና፣ኢነርጂ፣ ዲጂታል ቴክኖሎጂ፣ እውቀት ለአፍሪካና የካሪቢያን ሃገራት ማህበረሰብ የብልፅግና ድልድይ መሆን እንዳለባቸው ገልጸዋል፡፡
በመርኃ ግብሩ የአንጎላ ፕሬዚዳንትና የወቅቱ የአፍሪካ ሕብረት ሊቀ መንበር ጃኦ ሎሬኔዞ፣ የኬንያ ፕሬዝዳንት ዊልያም ሩቶ፣ የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሀሙድ አሊ የሱፍ፣ የካሪቢያን ሀገራት ማህበረሰብ ዋና ጸሀፊ ካርላ ባርነት፣ የካሪቢያን ሀገራት መሪዎችና ሚኒስትሮች መገኘታቸውን የኢዜአ ዘገባ ያስረዳል።

