ስምምነቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ (ዶ/ር) በሩሲያ ሞስኮ ያደረጉትን ጉብኝት ተከትሎ ውይይት ካደረጉባቸው ሰፊ የትብብር መርሃ ግብር አካል ነው ተብሏል።
ስምምነቱ ትናንት ሐሙስ መስከረም 15 ቀን 2018 ዓ.ም በሩሲያ አቶሚክ ኢነርጂ ኮርፖሬሽን (ሮሳቶም) ዋና ዳይሬክተር አሌክሲ ሊካቼቭ እና በኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) መካከል ተፈርሟል።ይህም ሮሳቶም እና የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በኢትዮጵያ የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ጣቢያ ለመገንባት ለሚያደርጉት ትብብር ተግባራዊ እርምጃን የሚያስቀምጥ መሆኑ ተገልጿል።
ስምምነቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ (ዶ/ር) እና የሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን በተገኙበት በክሬምሊን የተደረገ ሲሆን ሁለቱ ሀገራት በኃይል፣ በግብርና፣ በጤና አጠባበቅ እና በመከላከያ ትብብር ላይም የሁለትዮሽ ውይይት ማድረጋቸውን የክሬምሊን መግለጫ አመላክቷል።
በዚሁ ወቅት የሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን “ኢትዮጵያ በአፍሪካ የቆየች አስተማማኝ አጋራችን ናት” ያሉ ሲሆን፣ በጎርጎሮሳውያኑ 1898 በሁለቱ ሀገራት መካከል ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ከተመሰረተበት ጊዜ አንስቶ በሁለትዮሽ ግንኙነቶች የተመዘገበውን ቀጣይነት ያለው እድገት አፅንኦት ሰጥተው ተናግረዋል።
በሩሲያ እየተካሄደ በሚገኘው የዓለም አቶሚክ ፎረም ላይ የተገኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አሕመድ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ፕሮጀክቱ ኢትዮጵያ ከሩሲያ ጋር ያላትን ትብብር የሚያጠናክር እና አዳዲስ የኃይል ልማት አማራጮችን የመከተልን ምኞት ያሳያል ብለዋል።
“ታሪካዊ ግንኙነታችን ወደፊትም የተሻለ ሆኖ እንዲቀጥል መስራት አስፈላጊ ነው” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ኢትዮጵያ በአስፈላጊ ዘርፎች ሁሉ ከሩሲያ ጋር ስትራቴጂካዊ ትብብር ለመፍጠር ያላትን ፍላጎት ገልፀዋል።
የኒውክሌር ኃይል ፕሮጀክት ስምምነቱ በኢትዮጵያ ንጹህ ኃይልና ማኅበራዊ አገልግሎቶችን ልማት ለመደገፍ የታለመ እንደሆነ ተጠቁሟል።
ቀደም ሲል ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ እና ፕሬዝዳንት ፑቲን ከሌሎች ሀገራት መሪዎች ጋር በመሆን በዓለም አቀፉ የአቶሚክ ፎረም ላይ ተገኝተዋል።
በቅርቡ በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚንስቴር የቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግር ክፍል ኃላፊና የኒውክሌር ፕሮግራም አስተባባሪ ተክለማርያም ተሰማ (ዶ/ር) ከሀገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን ጋር ባደረጉት ቆይታ፣ ኢትዮጵያ ለምርምር እና ኃይል ማመንጫ የሚውል የኒውክሌር ማብላያ ማዕከል የመገንባት እቅድ እንዳላት ገልጸዋል።
አክለውም የታቀደው ማዕከል የምርምር ላቦራቶሪን እና የትምህርት ሥልጠናን ጨምሮ ለተለያዩ አገልግሎቶች የሚውሉ ተቋማትን ያካተተ እንደሚሆን ገልፀው በተመሳሳይ ተቋማት ልምድ ባላቸው ሀገራት ተሞክሮ መሰረት፣ የማዕከሉ ግንባታ ከአምስት እስከ ሰባት ዓመት ሊወስድ እንደሚችል አመላክተዋል።
አያይዘውም ኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጨት የሚችል የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ ጣቢያ ለመገንባትም እቅድ እንዳላት ገልፀው ዓለም አቀፍ ተሞክሮን በመጥቀስ ጣቢያውን ለመገንባት ወደ አሥር ዓመት ገደማ ሊወስድ እንደሚችል ጠቁመዋል።
አሜሪካ፣ ኮሪያ፣ ቻይና እና ሩሲያን ጨምሮ በርካታ ሀገራት ይህን መሰል ቴክኖሎጂ ለሌሎች ሀገራት የመገንባት አቅም እንዳላቸው ገልፀው ኢትዮጵያ ለፕሮጀክቱ የሩሲያን የኒውክሌር ቴክኖሎጂ መምረጧን አስረድተዋል።
በተጨማሪም “የኒውክሌር ቴክኖሎጂ በተለያዩ ዘርፎች ላይ ሊተገበር ይችላል፤ እኛም ልንጠቀምበት ይገባል” ሲሉ ገልጸዋል። አስ

