በኤርትራ ወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት ሊካሄድ እንደሚችል የሚያሳዩ መረጃዎች እየወጡ ነው። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ “ከኢትዮጵያ ጋር ለመደራደር ፈቃደኛ ነን” በማለት ለአሜሪካ መናገራቸውን ተከትለው በቁም መታሰራቸውም ተሰምቷል።
በርካታ የሚከፈላቸው ሚዲያዎች በማሰማራት፣ ታጣቂዎችን በማደራጀት፣ በማስታጠቅና በተዋጊዎች ጭምር ድጋፍ በመስጠት ትህነግን ይዞ ኢትዮጵያን ለማተራመስ እየሰራ እንደሆነ የሚታወቀው የፕሬዚዳንት ኢሳያስ መንግስት የመፈንቅለ መንግስት ስጋት እንዳለበት ገምግሞ ስድስት ከፍተኛ መኮንኖችን በግዞት እንዳስቀመታቸው የዲያስፖራ ኤርትራዊ የተቃዋሚ አመራር ጠቁመዋል።
” ገዳም” የምትባለውና ያረጀ ዘመን ምሳሌ ያደረጓትን ኤርትራን የሚመሩት አቶ ኢሳያስ ኤርትራን ለምን በዚህ ደረጃ ጨለማ ለማድረግ እንደወሰኑ፣ ሕዝቡንም በማድቀቅ ከድህነት በታች ቀጥቅጠው ለምን ለመግዛት እንደወደዱ በግልጽ ተጠይቀው አያውቁም። አንዳንድ ደፋሮች ቢነሱም እስርና ሞት ተቀብለዋል። መፈንቅለ መንግስት አስበው የነበሩም ዘመናቸውን በእስር ጨርሰዋል መቸረሳቸው፣ መሞታቸውና የደረሱበት የማይታወቅ እንደሆነ በተለያዩ ጊዜያት የወጡ መረጃዎች ያስረዳሉ።
ዓለም አምባገነ የሚላቸው የኤርትራ የዕድሜ ልክ ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ከመኮንኖቹ በተጨማሪ የድሜ አቻቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ኦስማን ሳላህ አሊ በቁም ማሰራቸው ተሰምቷል። ከኤርትራ የሚወጡ መረጃዎች እንደሚያመልክቱት ኢሳያስ ኦሳማን ሳላህ ከአስመራ ንቅንቅ እንዳይሉ ጥብቅ ትዕዛዝ አስተላልፈዋል።
ኦስማን ሳላህ በቅርቡ ተከሂዶ በነበረው በተባበሩት መንግስታት ድርጅት 80ኛ ጉባኤ ጎን ለጎን ከአሜሪካ ስቴት ዲፓርትመንት መሥሪያ ቤት ከፍተኛ አማካሪ ከሆኑት ማሳድ ቡሎስን ጋር ተመካከረው ነበር። በዚሁ በይፋ ተገልጾ በነበረ ምክክር ‟ሃገራቸው ኤርትራ በቀይ ባህር ጉዳይ ከኢትዮጵያ ጋር ለመወያየት ዝግጁ ናት” ማለታቸው ተመልክቶ ነበር። ይህ መረጃ በስፋት ከተገለጸ በሁዋላ በአዲስ አበባ በኮንትሮባንድ ንግድና ወንጀል ተግባራት የሚታማው የኤርትራ ኤምባሲ “ምድር ከፍና ዝቅ ቢል በቀይ ባህር ድርድር የለም” ሲል የውች ጉዳይ ሚኒስትሩ ተናገሩት ተብሎ በዓለም ዓቀፍ ሚዲያዎች የተገለጸውን “የስህተት ዜና” በማለት ማስተባበሉ አይዘነጋም።
የድርድርና የውይይት አሳብን እንደሚቀበሉ በማስታወቃቸው ሳቢያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከስብሰባው መልስ የቁም እስር ላይ እንደሆኑ ነው መረጃዎች የሚያመልክቱት።
የዲያስፖራ የኢሳያስ ተቃዋሚዎች “ሻዕቢያ ይህንን ዜና ለማስተባበል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩን ወደ ሚዲያ ብቅ ለማድረግ ሞክሮ በግልጽ ባልታወቀ ምክንያት አልተሳካም” ብለዋል።
በመኮንኖቹ በታገድና ግዞት መቀመጥ፣ በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ የቁም እስርና ከዚህ ቀደም በተፈጸሙት በርካታ አስነዋሪ ተግባራት፣ ኤርትራ እንደ አገር እየወደቀች መምጣቷ እያንገበገባቸው ያሉ አካላት ወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት ሊያደርጉ እንደሚችሉ የብሶቱን መተን ያሰሉት ተቃዋሚዎች አመልክተዋል።
ኢሳያስ አሁን ላይ ታማኞቻቸው ሳይቀሩ እያጉረመረሙባቸው እንደሆነ መረጃ እንዳላቸው የሚገልጹት መረጃ ሰጪዎች፣ የኤርትራ ሕዝብ ለውጥ ከናፈቀው ዓመታት መቆጣሩ፣ በታም መሰላቸቱና ዓለም ከሚገኝበት ስላጣኔ ታቅቦ እንዲኖር መደረጉ በየዕለቱ ገሃድ አይውጣ እንጂ የኢሳያስን ስርዓት ቀፎ እንዳደረገው እነዚሁ ወገኖች ያስረዳሉ።

