በአማራ ክልል ደቡብ ወሎ ዞን መካነ ሰላም ከተማ በስምና በድርጅት መለያቸው የሚታወቁ ታጣቂዎች መስጂድ ውስጥ በመግባት ጭፍጨፋ መፈጸማቸውን ነዋሪዎችና በስፍራው የነበሩ እማኞች አስታውቀዋል። ድርጊቱ የተፈጸመው በግልጽ ሆኖ ሳለ ለወትሮ መሰል ዜናዎችን የሚሰሩ የጀርመን ድምጽና ቢቢሲ አለመዘገባቸው ቅሬታን ፈጥሯል።
መስከረም 23፣2018 ዓ.ም በመስጂድ ኑር በኢሻ ሰላት ወቅት ወደ መስጂድ የታጠቁ ኃይሎች በመግባት ሃይማኖታዊ ግዴታቸውን ወይም የሶላት ስርዓት እየፈጸሙ ባሉ ንጹሃን ላይ ገድያ መፈጸሙን በርካታ ዜጎች በማህበራዊ ገጾቻቸው ይፋ አድርገዋል። ግድያው በተጠቀሰው ቀንና ስፍራ መፈጸሙን ያስተባበለ አካል ስለመኖሩ አልተደመጠም።
በአማራ ክልል በተለያዩ ጊዜያት ሙስሊም ዜጎች ላይ የተፈጸመውና እየተፈጸመ ያለው ግድያና በደል “በዛ” በሚል የአሁኑን ድርጊት በማውገዝ በርካታ የዕምነቱ ተከታዮችና ፍትህ ወዳድ ዜጎች ተቃውመዋል። ድርጊቱን ፈጸሙ የተባሉት ታጣቂዎች በምን ምክንያት በጅምላ እርምጃ እንደወሰዱ፣ የሶላት ሰዓትን እንደመረጡና የተጠቀስወን መስጂድ ዒላማ እንዳደረጉ ይህ እስከታተመ ድረስ የተባለ ነገር የለም።
በኢትዮጵያ እያደፈጡ የዕምነት አባቶችን፣ ምዕመኖችን፣ ቤተሰቦቻቸውንና በዙሪያቸው ያሉትን ማፈን፣ መግደል፣ ማገትና ገንዘብ መቀበል፣ ገዳማትን ማጥቃት ትርጉሙ በግልጽ ያልተቀመጠ ተደጋጋሚ ወንጀል ከሆነ ሰንብቷል። ከሁሉም በላይ ተመሳሳይ ወንጀል በተለያዩ ጊዜያት የሚፈጽሙትና ተበዳዮች በምስክርነት ማንነታቸው ጠቅሰው የሚወነጅሏቸው አደረጃጀቶች ስለሚፈጽሙት ወንጀል ኃላፊነት አይወዱም። በዚህም ሳቢያ የዜጎች እልቂት ተራ ጉዳይ እየሆነም ነው።
ሃማስ፣ ሂዝቦላ፣አልቃይዳ፣ ቦኮሃራም፣ የሃውቲ ተዋጊዎች፣ አይሲሲ ወዘተ ጥቃት ሲፈጽሙ ኃላፊነት በመውሰድ ድርጊቱን የፈጸሙበትን ዋና ምክንያት ይፋ እንደሚያደርጉት ሁሉ፣ በኢትዮጵያ የሚታወቁ ታጣቂዎች እገታ፣ ግድያ፣ አፈና፣ ወዘተ ሲፈጽሙ ምንም እንዳልተፈጠረ ዝምታን መምረጣቸው ስጋቱን ያገነዋል። ከምንም በላይ እነዚህን የሚታወቁ ታጣቂዎች የሚደግፉ፣ የሚመሩና በውጭና በአገር ውስጥ ሆነው የሚያደራጁ በድጋፍም ሆነ በውግዘት ምንም ሲሉ አለመደመጣቸው ሌላው ጉዳዩን ውስብስብ የሚያደርገው ቁልፍ ጉዳይ እንደሆነ በርካቶች በተደጋጋሚ አስተያየት የሚሰጡበትና መስልስ የማይገኝለት አሳሳቢ ጉዳይ ሆኗል።
እንደውም በተቃራኒ የሰለባዎች ቤተሰቦች፣ ከግድያና አፈና ያተረፉ ምስክሮች ስም ጠርተው በሲቃ ድምጽ ወንጀሉን የፈጸሙትን ሲያጋልጡ ማስተባበያ በመስራት ወንጀሉን ወደ ሌላ ወገን የማስተላለፍ ልምድ በዝቶ ይታያል። በዚህ አግባብ ቪኦኤ በዋናነት የሚጠቀስ ሲሆን ቢቢሲም ስላታዊ ሪፖርት በማቅረብ በተደጋጋሚ ቅሬታ ሲቀርበበት እንደነበር ይታወሳል።
ዛሬም ይህ እስከታተመ ድረስ ቢቢሲና ጀርመን ድምጽ ይህን ግፍ እያወቁ አለመዘገባቸው በስፍራው የነበሩትን፣ በጥቅል ሙስሊም ዜጎችን እንዲሁም ፍትህ ወዳዶችን አነጋግሯል። የኢትዮሪቪው የአዲስ አበባ ዘጋቢ በዚህ ጉዳይ ተገርመው ሲነጋገሩ የነበሩትን ጠይቆ “እስኪ አድረን እናያለን” በማለት ትዝብታቸውን አጋርተውታል።
ምስክሮች እንዳሉት ታጣቂዎቹ (በስም ይታወቃሉ) በመስጂዱ ቅጥር ግቢ ውስጥ ገብተው የፈጸሙት ግድያ እጅግ ሰብአዊነት የጎደለው ሲሆን፣ በአንድ አገር ዜጎች ላይ በራስ ወገን ይፈጸማል ተበሎ የሚታሰብ እንዳልሆነ አመልክተዋል። ለጥንቃቄ ሲባል ከመጻፍ ተቆጥበን እንጂ ድርጊቱ ዘግናኝ ነው። ለዚህ ነው ምክር ቤቱ ” …. የሃይማኖት ተቋማት እና መሪዎች ድርጊቱ አብሮ የመኖርን እሴት የሚሸረሽር በመሆኑ እንዲያወግዙና እንዲቃወሙ የሚመለከታቸው አካላትም ህጋዊ እርምጃ እንዲወስዱ አሳስባለሁ” ሲል ጥሪውን ያሰማው። ከስፍራው እንደተሰማው ከሆነ ድርጊቱ ከተፈጸመ በሁዋላ መከላከያ አካባቢው በመድረስ የማረጋጋትና የአሰሳ ስራ እየሰራ መሆኑ ታውቋል።
ከኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የተሰጠ ወቅታዊ መግለጫ!
በአማራ ክልል ደቡብ ወሎ ዞን መካነ ሰላም ከተማ መስከረም 23፣2018 ዓ.ል በመስጂድ ኑር በኢሻ ሰላት ወቅት ወደ መስጂድ የታጠቁ ኃይሎች በመግባት ሃይማኖታዊ ግዴታቸውን በመወጣት ላይ በነበሩ ፦

ፎቶ – ከተገደሉት መካከል በከፊል
1 የመስጂድ ዋና ኢማምና የወረዳው መጅሊስ ም/ሰብሳቢ
2 የመስጂድ አመራሮች
3 የመስጂድ ኻዲሞችን አሰቃቂ እና አረመኔያዊ በሆነ ሁኔታ መግደላቸውን የክልሉ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ም/ቤት አረጋግጦልናል።
እነሱም ሸሂድ ሆነዋል አላህ ጀነተል ፍርዶስ ይወፍቃቸው ።
ጠቅላይ ምክርቤቱ የእምነት ተቋማት የተከበሩ ቦታዎች በመሆናቸው ሊጠበቁ እንጅ እንዲህ አይነት አፀያፊ ተግባር የሚፈፀምባቸው መሆን የለባቸውምና ድርጊቱን በፅኑ ያወግዛል።
መላው የሃይማኖት ተቋማትም በእምነት ቦታዎች የሚደረጉ ትንኮሳዎች እና በእምነት ተከታዮች ላይ የተቃጣ መሰል የጅምላ ግድያ ሊያወግዙና ሊያስቆሙ ይገባል።
ህዝበ ሙስሊሙ ይህንን በሀይማኖት ተቋማት ላይ የተቃጣ አደጋ ለመከላከል መረጃ በመለዋወጥ የሃይማኖት ተቋማትንና አካባቢውን እንዲጠብቅ ጠቅላይ ምክርቤቱ ጥሪውን ያስተላልፋል።
ብዝሃ ሀይማኖት ባለባት ሀገራችን በተለያየ እምነት ውስጥ ያሉ ህዝቦች ለዘመናት ያቆዩተን ሰላማዊ እና መልካም መስተጋብር ሆን ተብሎ ለመናድና ማባሪያ ያጣ ቀውስ ውስጥ እንድንገባ የሚፈልጉ አካላት የፈፀሙት መሆኑን ጠቅላይ ምክር ቤቱ ይገነዘባል።
በመጨረሻም ሁሉም ሃይማኖት ተቋማትና መሪዎች ይህ ጉዳይ አብሮ የመኖር እሴት እንዳይሸረሽር ብሎም እንዳያጠፋ ድርጊቱን እንድታወግዙ እንዲሁም በፅኑ እንድትቃወሙ እየጠየቅን መንግስትም ይህንን ተግባር በእምነት ቦታዎችና አባቶች ላይ የፈፀሙት ላይ ህጋዊ እርምጃ እንዲወስድ እንጠይቃለን።
መስከረም 24 ቀን 2018 ዓ.ም
የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክርቤት

