የውድብ ዴሞክራሲያዊ ስምረት ትግራይ (ስምረት) ባወጣው ወቅታዊ መግለጫ፣ በክልሉ ውስጥ የሚንቀሳቀስ “የጥፋት ቡድን” ያለፈው የጦርነት ጠባሳ ሳይሽር አዲስ የጦርነት ቀስቃሽ ተግባር ውስጥ መግባቱን አስታውቋል።
ድርጅቱ “በወጣቶች ሕይወት መነገድ ይበቃል!” በሚል ባወጣው በዚህ መግለጫ፣ ቡድኑ የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት በግልጽ በመጣስ ቀጠናውን ወደማይቀር ትርምስ እየመራው መሆኑን በጽኑ ከስሷል።
ስምረት በመግለጫው እንዳመለከተው፣ ይህ የጥፋት ቡድን የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት ወደ ጎን በመተው ከኤርትራው የህግደፍ ሥርዓት ጋር በማበር የጦርነት ዝግጅት እያደረገ ይገኛል።
ቡድኑ የግዛት አንድነትን እና የተፈናቃዮችን ጉዳይ ለፖለቲካዊ መጠቀሚያነት ቢጠቀምበትም፣ በተግባር ግን የሕዝቡን ደህንነት ለአደጋ የሚያጋልጥ የጦርነት ወፍሪ መጀመሩን ድርጅቱ ገልጿል።
በተለይም ቡድኑ ቀደም ብሎ ቀብሮ የነበሩትን ከባድ መሣሪያዎች በማውጣት ወደ አማራ እና ዓፋር ክልሎች አቅጣጫ መጠነ ሰፊ ጥቃት ለመሰንዘር እየተንቀሳቀሰ መሆኑ በመግለጫው ተጠቁሟል።
በጠለምት አቅጣጫ የተጀመረው ትንኮሳ የድሃ ወጣቶችን “ለጥይት እራት” የሚያደርግ ታሪካዊ ስህተት ነው ሲል ስምረት ኩነኔውን ገልጿል።
ውድብ ዴሞክራሲያዊ ስምረት ትግራይ ለትግራይ ሰራዊት ባስተላለፈው ጥሪ፣ ሰራዊቱ የጥፋት ቡድኑን የግል ፍላጎት ለማርካት ከሚደረግ ጦርነት ራሱን እንዲያድን እና የሕዝቡን ሰላም እንዲያስቀድም አሳስቧል።
ወላጆችም ልጆቻቸው ለሌላ ጦርነት እንዳይማገዱ እንዲመክሩ ጥሪ የቀረበ ሲሆን፣ ድርጅቱ በትግራይ ሕገ-መንግስታዊ ወሰን መከበር እና የተፈናቃዮች ወደ ቀዬአቸው መመለስ ላይ ጽኑ አቋም እንዳለው ቢገልጽም፣ ይህ መሳካት ያለበት ግን በሰላማዊ እና በሕጋዊ መንገድ በፕሪቶሪያው ስምምነት መሰረት ብቻ መሆን እንዳለበት አፅንዖት ሰጥቷል።
ድርጅቱ በመጨረሻም ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የፕሪቶሪያው ስምምነት እንዲተገበር ጫና እንዲያደርግ የጠየቀ ሲሆን፣ ቡድኑ በሕገ-ወጥ መንገድ እየዘረፈ ያለው የሕዝብ ሀብት እና መሬት በዝርዝር እየተመዘገበ መሆኑንና ተጠያቂነት እንደማይቀር አስታውቋል።
በመሪዎቻችን ብዕር እና በጓዶቻችን ደም የተፈረመው የሰላም ስምምነት ሊፈርስ አይገባም ያለው ስምረት፣ መግለጫውን የደመደመው ጥሪ 21 ቀን 2018 ዓ.ም. መሆኑን ጠቅሶ በወጣቶች ሕይወት መነገድ እንዲቆም በድጋሚ በማሳሰብ ነው።

