የወልቃይት ጠገዴ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሸተ ደምለው ከትግራይ አቅጣጫ እየተነሳ ነው የሉትን የጦርነት አካሄድ አስመልክቶ ሁለት ስለት ያለው ሰይፍ ሲሉ የዘረዘሩትን አቋም ይፋ አድረገዋል። ጽሁፉ የተላከው ለአንዳፍታ ሚዲያ ሲሆን እንዳለ ወስደን አቅርበነዋል።
የወልቃይ ጠገዴ የዘመናት የአማራ ማንነትና ወሰን ጥያቄ የተለያዩ የትግል ምዕራፎችን አልፎ ዛሬ ወሳኝ የትግል ሜዳ ላይ ደርሷል፡፡
ዛሬ የደረስንበት የትግል ሜዳ የወትሮ ዝግጁነትን በማሳደግ በሁለት የትጥቅ አቅሞች ልቆ መገኘትን ይጠይቃል፡፡
አንደኛው በሀሳብ ትጥቅ ሲሆን፤ ሁለተኛ ደግሞ ከአባቶቻችን በወረስነው አርበኝነት መሰረት ራስን መከላከል ላይ መሰረት ያደረገ አቅምና ተነቃነቃዊ ዝግጁነትን ማሳደግ የሚጠይቅ ወሳኝ የትግል ጊዜ ላይ ነን፡፡ የሀሳብ ትጥቁም ሆነ ራስን ከወረራ የመከላከል ዝግጁነቱ መዳረሻ ግቡ የተከዜ አዳኝ ትውልድ ተልዕኮን ማሳካት ነው፡፡ ተልዕኳችን ደግሞ ‹ለመጭው ትውልድ ነጻነትን እንጂ ተሻጋሪ ዕዳን አናወርስም› የሚል ዘላቂ አሸናፊነትን ያለመ ነው፡፡ ዘላቂ አሸናፊነት ስንል በሁለት መልኩ ነው፡፡
በአንደኛው ገጽ ዘላቂ የሕግ አሸናፊነት ሲሆን፤ ሁለተኛው ገጽ ደግሞ የሕግ አሸናፊነታችንን አልቀበልም ብሎ ለዳግም ወረራ የሚነሳውን ኃይል የምንመክትበት ራስን የመሆን ክቡር ሰማዕትነትን ልንቀበልበት የተዘጋጀንለት የፀረ-ወረራ ተጋድሏችን ነው፡፡
እናም የተከዜ አዳኝ ትውልድ ሚና በሁለት ገጽ የተሳለ ሰይፍ ማለት ነው፡፡ በሀሳብ ትጥቅም ሆነ በራስ መከላከል ትጥቅ፤ ሁሌም ዝግጁ ሆኖ መገኘት!!
የሀሳብ ትጥቅ ስንል ምን ማለታችን ነው…?
የወልቃይት-ጠገዴን አማራነት ከታሪክ፤ ከመሬት ይዞታ፤ ከአስተዳደርና ከግብር ክፍያ፤ ከመልክዓ-ምድራዊ፤ ከሕዝብ ስርጭት፤ ከሥነ-ልቦናና ቱባ ባህላችን፣… ወዘተ ማመሳከሪያዎች አንጻር ወልቃይት-ጠገዴ አማራ እንጅ ትግሬ ሆኖ እንደማያውቅ በወያኔ የሐሰት ትርክት ለተደናገሩ ለሌሎች የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች በማስረዳት፤ ለዓለማቀፉ ማኀበረሰብ ማስገንዘብን ዋና ማዕከሉ ያደረገ የትግል ክፍል ነው፡፡ በዚህ የትግል ክፍል ውስጥ ታሪክ ትልቅ ቦታ ይሰጠዋል፡፡
ይህ የሚሆነው፡- ታሪኩን ጠንቅቆ የሚያውቅ ትውልድ ጉድለቱን ይሞላል፡፡ የትግል ስንቅ ባለቤት ይሆናል በሚል እሳቤ ነው፡፡ ራስን የመገንዘብ፣ አቅምን የማወቅ፣ ጸጋና በረከትን ለይቶ የመጠቀም፣ የሀሳብም የተግባርም ጉልበት ይኖረዋል፡፡
የሀሳብ ጉልበት ማለት የሀሳብ ትጥቅ ማለት ነው!! የሀገር ባለቤትነት ማረጋገጫ አንዱና ዋናው ጉዳይ ማንነትና ርስትን የማስከበር ጉዳይ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ታሪክን፣ መነሻን ከማወቅ ይጀምራል፡፡ ታሪክና መነሻን ማወቅ ማንነትንና ርስትን ለማስከበር ትልቅ አቅም ነው፡፡
የዚህ ትልቅ አቅም ባለቤት መሆን ደግሞ የሀገር ባለቤትነትን ያረጋግጣል!!
የሀገር ባለቤት ለመሆን የሀሳብ ትጥቅ ያስፈልጋል፡፡
ራስን የመከላከል አቅም መገንባት ስንል ምን ማለት ነው…?
ትግላችን ራስን የመሆን ክቡር የማንነት ትግል ነው፤ የራስን ዕድል በራስ የመወሰን ትግል ነው፡፡ ነገር ግን ይህን ለዘላቂ የሕግ አሸናፊነት የሚያበቃንን ሰላማዊ የትግል መንገድ አልቀበልም ብለው፤ ዳግም ለወረራ ተከዜን የሚሻገር ወራሪን የምናሳፍርበት፤ የፀረ-ወረራ ትግላችን መመከቻ ነው፡፡
ምክንያቱም ለወረራ እየተዘጋጀ ያለው ኃይል ትግሉ የእርሱ ያልሆነን ርስትና ማንነት የመውረር የማጥፋት ነው፡፡
በመሆኑም ይህ መምጫው ብዙ የሆነ ኃይል ሊመከት የሚችለው የትግል ዓላማ ጥራት ባለው በተደራጀ፤ የአመራር ተዋረድ ባለው፤ የታሪክና የትውልድን ጥያቄ በዘላቂነት ሊመልስ በሚችል ጠንካራ አደረጃጀት እንጂ እንዲሁ በተበተነና ባልተቀናጀ መልኩ በሚደረግ ትግል ማሸነፍ አይቻልም፡፡
ሕግና ሥርዓት ባለው መንግሥታዊ መዋቅር፣ ተዋረዳዊ ባለው አመራር ራስን የመሆን ክቡር ማንነታችን በዘላቂነት ይረጋገጣል ስንልም እውነት ሁሌም አሸናፊ እንደምታደርግ በመተማመን ነው።
የወልቃይት-ጠገዴ የአማራ ማንነትና ወሰን በዘላቂነት የማስከበር ትግል ከመቼውም ጊዜ በላይ ሕዝባዊ አንድነትና ስትራቴጂያዊ አመራር ይጠይቃል፡፡
እስካሁን በመጣንበት መንገድ፡- የወልቃይት-ጠገዴ የአማራ ማንነትና ወሰን ትግል ከከፋኝ የአርበኞች ተጋድሎ እስከ የማንነት አስመላሽ ኮሚቴው ሰላማዊ የትግል መንገድ፤ የሰሜን ዕዝ ከጀርባ መታረድን ተከትሎ በሕግ-ማስከበር ዘመቻው አገርን ከጥቃት፣ ራስን ደግሞ ከወራሪው ህወሓት የባርነት አገዛዝ ነፃ ለማውጣት ከተከፈለው መስዋዕትነት እስከ አሁን ድረስ ለዘለቀው የወልቃይት-ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ዞን ምስረታና በራስ ልጆች የመተዳደር ዕድል በጋራ መስዋዕትነታችን፣ በትግል ዓላማ ጽናታችን እዚህ ደረጃ ላይ ደርሰናል፡፡
ዛሬ የወልቃይት-ጠገዴ የአማራ ማንነት ጥያቄ ከኢትዮጵያ አልፎ በአፍሪካ ቀንድ ወሳኝ ከሚባሉ ጉዳዮች አንዱ ሆኗል፡፡
በትግላችን የአማራን ሕዝብና ፍትሕ ወዳድ የሆኑ ኢትዮጵያዊያንን ከጎናችን ማሰለፍ ችለናል፡፡ የማንነት ኮሚቴው ሰላማዊ የትግል መስመሩን ጠብቆ በመጓዝ ላይ ነው፡፡ የዞኑ አስተዳደር ህጋዊነትን ተላብሶ በሕግና በሥርዓት ሕዝብ እያስተዳደረ ይገኛል።
በወልቃይት ጠገዴ ጉዳይ በርካታ ዓለማቀፍ ኃይሎች ጫና ቢያሳድሩም ሕዝብን ይዞ የተሸነፈ የለምና ዛሬ በትግላችን ቀና ብለን መሄድ ጀምረናል፡፡
እንደሰው ተከብሮ ከመኖር፣ በባህል፣ ወግና ቋንቋችን ከመጠቀም አልፈን የሕዝባችንን የዘመናት የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች እንዲሟሉ በራስ ተነሳሽነት በአቅማችን እየታገልን እንገኛለን፡፡ የክልላችን መንግሥት አቅሙ የፈቀደውን ድጋፍ በማድረግ ላይ ነው። የፌዴራል መንግሥቱ አንደኛውን አንገብጋቢ ጥያቄ በኢትዮጵያ አየር መንገድ በኩል ምላሽ ሰጥቶናል። ለዚህም በመላው የወልቃይት ጠገዴ አማራ ሕዝብና አስተዳደር ሥም እናመሰግናለን።
ሌሎች የመሰረተ ልማት ድጋፎች እንደሚቀጥሉ እምነት አለን። በእኛ በኩል የትግል ቁርጠኝነታችን ጸንተን፣ የአገር ውስጥና የውጭ ዲያስፖራ ወገናችንን በማስተባበር በውስጥ አቅም ራስን ሆኖ መገኘት በሚለው መርሆችን የሕዝብ አቅምን ለሕዝብ ጥቅም አሟጠን ለመጠቀም እንተጋለን።
በጥቅሉ ዛሬ የወልቃይት-ጠገዴ ሲቲት ሁመራ ዞን አስተዳደርና ሕዝብ ‹በአንድ እጅ ነጻነት፣ በሌላው እጅ ልማትን ማረጋገጥ› እንደሚቻል በተግባር ማሳየት ችለናል፡፡
ቀን የእርሻ ቦታ ሌሊት ምሽግ እያደሩ ራስን ከመጠበቅ አልፎ ለኢትዮጵያ አገረ-መንግሥት ብሔራዊ ዘብ፤ ዳር ድንበር ጠባቂ መሆኑን የአባቶቹን ታሪክ በተግባር በመድገም ማስመስከሩን ቀጥሏል፡፡
ይሁን እንጂ በዚህ ሁሉ ድል መሀል ጠላት ዛሬም ዓይኑን ከእኛ ላይ አልነቀለም፡፡
ከሦስት አስርት ዓመታት በላይ ከአፓርታይድ በከፋ ሁኔታ ረግጦ ይገዛው የነበረውን ወልቃይት ጠገዴን ዳግም ተመልሶ ለመቆጣጠር የተለያዩ የፖለቲካ ሴራዎችን አለፍ ሲልም የኃይል አማራጭን ታሳቢ ያደረገ እንቅስቃሴን ያልማል።
ዛሬም ለዳግም ወረራ ታጣቂ ኃይሉን ተከዜን ለማሻገር የተጠና የፖለቲካ ስልት፤ የማደናገሪያ ፕሮፖጋንዳዎችን በመልቀቅ ላይ ነው፡፡
ይህ ኃይል ፍላጎቱ፣ ወልቃይት ጠገዴን መልሶ በመቆጣጠር ዛሬም እንደ ትናንቱ ከሰው በታች ሊያደርገን፤ ሊያዋርደን፤ ብቻ አይደለም፡፡ እንደሕዝብ ጨርሶ ሊያጠፋን ነው ፍላጎቱ፡፡
ይህ ደግሞ በወልቃት-ጠገዴ አማራ ሕዝብ መቃብር ላይ እንጅ የማይታሰብ ጉዳይ ነው!!
በመሆኑም ሁሌም ዝግጁ ሆኖ መገኘት በሚለው የትግላችን መርህ መሠረት፡- ለፍቅርም ሆነ ራስን ለመከላከል አንቦዝንም።
በህብረ ብሄራዊ አንድነት አብሮነትን የሚሹ እህት ወንድሞቻችንን እንቀበላለን፥ የኃይል አማራጭን አስበው ለወረራ የሚዘምቱ ካሉም አንታገስም።
በዞናችን የሚገኘውን ሁሉንም የትግል አቅም ወደአንድ የአመራር ቋት በማምጣት ለዘላቂ ድል የሚያበቃ የትግል ስትራቴጂ ለመከተል በምናደርገው ህጋዊና ሰላማዊ ትግል ውስጥ ሁሌም ከጎናችን የቆማችሁ መላው የአማራ ህዝብ፣ መላው የኢትዮጵያ ብሄር ብሄረሰቦችን እናመሰግናለን።
እንደ ዶክተር ዳኛቸው አሰፋ፣ እንደ ጋዜጠኛና ደራሲ ገነት አየለ ያሉ የሀሳብ ፊት አውራሪዎች የተከዜ አዳኝ ትውልድ በዕድሜ፣ በፆታ፣ በኃይማኖት፣ በጊዜ፣ በቦታ እንደማይወሰን፤ ብረት ብቻ ሳይሆን እውነትን ይዞ በሀሳብ መታገል እንደሚቻል ማሳያዎቻችን ናቸው።
እኒህን የመሰሉ ምሁራዊ ህዝባዊነትን የተላበሱ ወገኖቻችን፦ የትግል አበርክቷቸው በወልቃይት ጠገዴ የአማራ ማንነት ትግል ውስጥ መቼም፣ የትም በምንም ሁኔታ ከእውነት ጋር የመቆም የፍትሐዊ ትግል አካል የመሆን የሞራል ጉዳይ ስለመሆኑ ማሳያዎች ናቸው።
የትግሉ ዋና መርህ የወልቃይት ጠገዴ አማራ ማንነት የትግል መርህ፡- ሁሌም ዝግጁ ሆኖ መገኘት!
በምሽግ ውለው የሚያድሩ ታጋዮች በሚናቸው፤
በሀሳብ ፊት አውራሪነት ለእውነት የቆሙ ታጋዮችም በሚናቸው የተከዜ ዘብ ሆነው ይዘልቃሉ!!
ጠፍጣፋ ድንጋይ መሮ አይበሳው፣
የአባቱን ታሪክ ልጁ አይረሳውም” ብለን እንደ ብረት የጠነከረ አንድነትን ይዘን በጠላት አጀንዳና ፕሮፖጋንዳ አንደናገርም፣ ከትግላችን ዓላማም ንቅንቅ አንልም።
(ማስታወሻ፡- ይህ ሀሳብ የዋና አስተዳዳሪውን አቋም እንጂ የዝግጅት ክፍል አቋም እንዳልሆነ አስቀድመን ለማሳወቅ እንወዳለን፣ ተቃራኒ ወይም ተመሳሳይ አሳብ ካለ እናስተናግዳለን )

