ሁሉም የፓለቲካ ፓርቲዎች በእኩል የሚያሳትፍ በምክር ቤት የሚመራ ሲቪል ጊዚያዊ አስተዳደር እንዲቋቋም አራት የትግራይ ተፎካካሪ የፓለቲካ ፓርቲዎች ጠየቁ።
የጋራ መግለጫውን ያወጡት ፦
– ሳልሳይ ወያነ ትግራይ (ሳወት) ፣
– ባይቶና ዓባይ ትግራይ (ባይቶና) ፣
– ውድብ ናፅነት ትግራይ (ውናት)
– ዓረና ንሉኣላውነትን ዴሞክራስን (ዓረና) ናቸው።
ፓርቲዎቹ ባወጡት የጋራ መግለጫ ፤ ” በትግራይ ያጋጠመው ችግር መነሻው ፓለቲካዊ ውድቀት ስለሆነ ከውድቀቱ ለመውጣት አካታች ፓለቲካዊ መፍትሄ ያስፈልጋል ” ብለዋል።
” ችግሩ የሚፈታው አንድ የፓለቲካ ፓርቲ በሚያራምደው የበላይነት አመራር ሳይሆን ሁሉም አቀፍ በሆነ አካሄድ ነው ” ሲሉ ገልጸዋል።
ለዚህም ሁሉም የፓለቲካ ሃይሎች በእኩል የሚሳተፉበት በምክር ቤት የሚመራ ስቪል ጊዚያዊ አስተዳደር ማቋቋም እንደ አንድ የችግር መፍቻ አስቀምጠዋል።
ፓርቲዎቹ በአሁኑ ወቅት በሁለት የህወሓት ሃይሎች የተፈጠረው ፓለቲካዊ መሳሳብ ወደ ጎን በመተው ወጣቶች ፣ ሴቶች ፣ የዳያስፓራ ማህበረሰብ መላው የትግራይ ህዝብ ዓላማቸው ደግፎ ከጎናቸው ሆኖ እንዲታገል ጥሪ አቅርበዋል።
” የትግራይ የፀጥታ ሃይሎች ከማንኛውም የፓለቲካ ሃይል ውግንና ነፃ በመሆን የሲቪል መንግስትና ህግ በመመራት ለህዝብና አገር ጥቅም መቆም አለባቸው ” ሲሉ አሳስበዋል።
በቅርቡ የሚፈፀሙት ተጨማሪ ተፈናቃዮች ወደ ቄያቸው የመመለስ ፣ ግዛታዊ አንድነት የማስመለስ ፣ ታጣቃዎች ትጥቅ የማስፈታትና ወደ ህብረተሰቡ የመቀላቀልና ሌሎች በትግራይ በኩል የሚፈፀሙ ስምምነቶችና ውሎች ለህዝብና ጉዳዩ ለሚመለከታቸው አካላት ግልፅና ይፋ እንዲደረግም ጠይቀዋል።

