” በዚህ ጦርነት ውስጥ ማን እየተጠቀመ እንዳለ ማወቅ አልቻልኩም ” ሲል የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ም/ቤት ተናገረ
” በአማራ እና በኦሮሚያ ክልሎች በመንግስት እና በታጣቂዎች መካከል እየተደረገ ያለው ግጭት ዓላማው ሊገባኝ አልቻለም ” አለ።
ም/ቤቱ ይህን ያለው ለሸገር ኤፍ ኤም 102.1 ሬድዮ በሰጠው ቃል ነው።
የም/ቤቱ ዋና ሰብሳቢ ደስታ ዲንቃ ፥ ” በሁለቱ ክልሎች ያለ መፍትሄ የቀጠለው ግጭት የጋራ ምክር ቤቱን በእጅጉ አሳስቦታል ” ብለዋል።
” ንጹሃንን እየገደለ፣ እያሰቃየ እና የሀገርን ሀብት እያወደመ ያለውን ግጭት ሁለቱም አካላት ቆም ብለው አስበው ምን እንዳመጣ እራሳቸውን ሊጠይቁ ” ይገባል ሲሉ ተናግረዋል።
” ንጹሃን፣ ባለስልጣናት እና የባለስልጣናት ልጆች እየተገደሉ እየታፈኑ ነው ” ያሉት ዋና ሰብሳቢው ” በዚህ ጦርነት ውስጥ ማን እየተጠቀመ እንዳለ ማወቅ አልቻልኩም ” ሲሉ አስረድተዋል፡፡
” በጦርነቱ እንደ ሀገር ሀገር እየተጎዳ ነው፣ እንደ ህዝብ ህዝብ እየተጎዳ ነው ፣እንደ ዜጋ ዜጎች እየተጎዱ ነው ፣እንደ ታሪክ ታሪክን እያበላሽን ነው ምን ዓይነት ስሌት አስልተን እንደምንረጋጋ አላውቅም ” ብለዋል፡፡
በሀገሪቱ በመንግስት እና በታጣቂዎች መካከል እየተደረገ ያለው ግጭት ውድመት እያስከተለ ቀጥሏል ያሉት አቶ ደስታ ችግሩን በንግግር ለመፍታት በሁለቱም ወገን ፍላጎት አይታይም ሲሉ ወቅሰዋል፡፡
” አንዱ በአንዱ ላይ የበላይ ለመሆን ከሚደረግ ሩጫ የዘለለ ግጭቱን በንግግር የመፍታት ፍላጎት እየተመለከትን አይደለም ” ሲሉ ገልጸዋል።
” ታጣቂዎች ሆኑ መንግስት ችግሩን በንግግር ከመፍታ ይልቅ ግጭቱን ስም ለማጠልሸት አንዱ ሌላውን ለመወንጀል እና የህዝብ ድጋፍ ለማግኝት እየተጠቀሙበት ነው ” ብለዋል።
ምክር ቤቱ በመንግስት እና በታጣዊዎች መካከል እየተካሄደ ያለው ግጭት ሁለቱም አካላት እቆምለታለሁ ፣ እቆረቆርለታለሁ የሚሉትን ህዝብ እና ሀገርን እያወደመ መሆኑን አውቀው በንግግር ችግራቸውን እንዲፈቱ ለሬድዮ ጣቢያው በሰጠው ቃል ጠይቋል፡፡

