ስለ ቡትቶው ጥምረት (The Hodgepodge Alliance) ሳስብ፤ እጅ በብልት ሳይሆን እጅ በደረት ያደረጉት ሰውዬ የቀጠናው የ destabilization ደላላ ሆኖ መቅረት ያሳዝነኛል። ያዝናናኛል። አልፎ አልፎም ግርም ይለኛል። ስልጣን ላይ ከአንድ ጎልማሳ፤ ፖለቲካ ውስጥ ከአንድ አዛውንት ዕድሜ በላይ ቢቆዩም ሃገራቸውን የብጥብጥ መቀመሚያ lab ከማድረግ ያለፈ ርዕይ እንደሌላቸው ሳስብ ድንቅ ይለኛለኛል። ከሁሉም በላይ ሚጢጢ እና ተቸንክራ የቀረች ሃገር ይዘው፤ ራሳቸውን እንደ አንድ ልዕለ-ሃያል ሃገር philosopher king የሚያዩት ነገር ፈገግ ያሰኘኛል።
የሆነው ሆኖ ከስድስት አመታት በፊት ሐምሌ 2010 በኢትዮጵያ እና ኤርትራ መሀከል ለ20 አመታት የዘለቀው stalemate መቋጫ ያገኘ ሲመስል፤ “ኢሱ…ኢሱ…” ሲሉ ከነበሩት ወገን ባልሆንም፤ I was cautiously optimistic። በተለይ ደግሞ ኢትዮጵያን፣ ሶማሊያን እና ኤርትራን ያጣመረ የቀጠናዊ ትብብር ማዕቀፍ (regional cooperation framework) ለውይይት ቀርቦ በመርህ ደረጃ ስምምነት ላይ መደረሱ እሰየው የሚያስብል ነበር። ምክንያቱም በአፍሪካ ቀንድ ብቸኛው organic and legitimate ጥምረት በሶስቱ ሃገራት ትብብር ላይ የተመሰረተ ሊሆን ስለሚገባ።
በዚህ መሐል ያው የሰሜኑ ጦርነት ተነሳ። እብሪት ልቡን አሳብጦት ወደ ላይም ወደ ታችም መተኮስ የጀመረው ህወሐት በ2013 የሁለቱ የጋራ ጠላት ሆነ። በጋራ እና በተናጠል operations ተወቀጠ። በመጨረሻም እብሪተኛው ህወሐት በ”ፕሪቶሪያው ስምምነት” እጁን ሰጠ። ጦርነቱም ተቋረጠ። ብዙ ቀሪ ስራ አለ። ግን በቃ። ተኩስ ቆመ። እኒያ እጅ በደረት ያደረጉት ሰውዬ ደበራቸው። አኮረፉ። “ጦርነቱ ቀጥሎ ህወሐት እና ህወሐታውያን ከምድረ-ገፅ ካልጠፉ” አሉ። ከላይ ከላይ ሲታይ ቅሬታቸው ህወሐት ሳይጠፋ የጦርነቱ ነበልባል መጥፋት ነው። Deep inside ግን የመከፋታቸው መንስኤ ፀረ-ህወሐቱ ጥምረት ያመቻቸላቸው በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ ገብቶ የመፈትፈት ነገርም ከጦርነቱ ጋር አብሮ ማብቃቱ አይቀሬ እንደሆነ መረዳታቸው ነው። ለዚህም ነው በኢትዮጵያ ውስጥ የሚደረግ ወታደራዊ operation መቀጠል አለመቀጠል፤ የኢትዮጵያ መንግስት ውሳኔ ብቻ መሆኑን ለመቀበል የተቸገሩት። ለዚህም ነው ልክ “አብይ ካደን” ሲሉ እንደከረሙት ድኩማን፤ ደጋፊዎቻቸው በየመድረኩ “ኢትዮጵያ ካደችን” እያሉ የሚያላዝኑት።
Don’t get me wrong! በፀረ-ህወሐቱ ጦርነት ወቅት ኤርትራ ጥሩ አጋር (military ally) ነበረች። አጋርነቷም ጠቃሚ ነበር። ምክንያቱም ወታደሮቻችን ለ20 አመታት ከጥቃት በጠበቁት ወገን ሲጠቁ፤ ወደ ግዛቷ እንዲያፈገፍጉ ፈቅዳለች። ከሎጂስቲክ እና ከወታደራዊ ዘመቻ አንፃር ከኤርትራ ግዛት መንደርደር ሲኖርብን፤ አስፈላጊውን ትብብር አድርጋለች። ከዚህ ውጪ “ኤርትራ ወታሮቿን ልካ ኢትዮጵያን ከመፈራረስ አድናለች” እያሉ ኤርትራውያን በየመድረኩ የሚጠርቁት ተረት ያው “በሬ ወለደ ነው”።
የኤርትራን ወታደራዊ የተሳትፎ scope and justification በተመለከተ በጦርነቱ ወቅት እና ከጦርነቱ በኋላ ህወሐታውያን “እንዴት በኤርትራ ሠራዊት ታስጨፈጭፉናላችሁ?” ብለው ሲጠይ [በፊትም አሁንም] የምሰጠውን መልስ እዚህ ጋር ላስታውስ። ኤርትራ ወደ ትግራይ ሰራዊቷን ያዘመተችው ህወሐት ሚሳይሎችን ወደ አስመራ ከተኮሰ በኋላ ነው። በወቅቱ የኢትዮጵያ መንግስት ለኤርትራ መንግስት የደህንነት ዋስትና መስጠት አይችልም ነበር። ስለዚህ ኤርትራ ራሷን ከእብሪተኛው ህወሐት እንድትከላከል ተፈቅዷል። በዚህም ህወሐት የኢትዮጵያ እና የኤርትራ መንግስታት የጋራ ጠላት ሆኗልና፤ የጋራ/የተቀናጀ ዘመቻን ግድ ብሏል። በዚህ ሂደት አስፈላጊ የሆነውም ከአስፈላጊነት (necessity and proportionality) ያፈነገጠውም እርምጃ ተወስዷል። የጋራ ጠላትም ተሸንፏል። ህወሐትም አደብ እንዲገዛ ተደርጓል። ከዚህ ውጪ ማንም የማንንም ሃገር “ከመፍረስ” አልታደገም! ሁለቱም ለየራሳቸው እና ለሚጋሩት የጋራ የደህንነት ግብ ማድረግ ያለባቸውን አድርገዋል። Period!
ዛሬ እጅ በደረት ያደረጉት ሰውዬ ከኢትዮጵያ አንፃር ከ1990 እስከ 2010 ሲያደርጉ እንደነበረው፤ ወደ ቀድሞው የdestabilization ድለላ ስራቸው ተመልሰዋል። ቅሬታቸው ከኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ ጋር የተያያዘ ቢሆንም፤ እየዞሩ የሚሸቅሉት አጀንዳ ግን “የቀይ ባህር ጉዳይ” የሚል ነው። ያኔ የትግል አጋሮቻቸው ከነበሩት ከህወሐት/ኢህአዴጎች ጋር በ1980ዎቹ ሲጣሉም የሆነው ይኸው ነው። በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ ገብቶ የመፈትፈት ፍላጎታቸው አልሳካ ሲል “የድንበር ማካላል” ጦርነት መቀስቀስ። እኚህ እጅ በደረት ያደረጉ የsmall state, big ego complex ሰለባ የሆኑ ሰውዬ እና ደጋፊዎቻቸው፤ ለሉአላዊነታቸው ቀናኢ የሆኑትን ያህል፤ ለኢትዮጵያ ሉአላዊነት ክብር የላቸውም። በኢትዮጵያ ከመጣው መንግስት ጋር ሁሉ የሚያላትማቸውም ይኸው ነው። ከ2010 እስከ 2015 ካሉት አመታት ውጪ የስልጣን ዘመናቸውን ሁሉ አስመራን የኢትዮጵያ-ጠሎች መነሐሪያ አድርገው ያስቀሯትም ለዚህ ነው።
እናም “ኢሱን ምን አስቀየምናቸው?” ለሚለው ጥያቄ መልሱ፤ “ምንም!” የሚል ነው!

