በሶማሌ ክልል ሰርጎ በመግባት ጥቃት ለመፈፀም በተንቀሳቀሱ 60 የአልሻባብ የሽብር ቡድን አባላት ላይ እስከ ዕድሜ ልክ የፍርድ ውሳኔ መተላለፉን የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ አስታወቀ
በሀገራችን ሶማሌ ክልል አፍዴር እና ሸበሌ ዞኖች በኩል ሰርጎ በመግባት ጥቃት ለመፈፀም ሲንቀሳቀሱ የነበሩ 60 የቡድኑ አባላት በቁጥጥር ሥር ውለው በ10 የምርመራ መዝገብ ተከሰው እስከ ዕድሜ ልክ እስራት የፍርድ ቤት ውሳኔ የተላለፈባቸው መሆኑን የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ አስታውቋል፡፡
ፖሊስ በ60 የሽብር ቡድኑ አባላት ላይ በቂ የቴክኒክና የታክቲክ ማስረጃ በማቅረብ በሽብር ወንጀል ምርመራ አጣርቶ ለፍትህ ሚኒስቴር በመላክ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ድሬዳዋ ምድብ ተዘዋዋሪ ችሎት ሁለት የሽብር ቡድኑ ከፍተኛ አመራሮች በዕድሜ ልክ እስራት፣ 56 ተከሳሾች እንደወንጀል ተሳትፎአቸው ከ6 ዓመት እስከ 18 ዓመት ፅኑ እስራት እና በአልሸባብ የሽብር ቡድን አባልነት የተከሰሱ ሁለት ተከሳሾች እያንዳንዳቸው 2 ዓመት ከ6 ወር እስራት እንዲፈረድባቸው ማድረጉን የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ገልጿል፡፡
በዚያን ወቅት በሀገራችን አንዳንድ አካባቢዎች የተፈጠሩ የፀጥታ ችግሮችን እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም የአልሸባብ የሽብር ቡድን ኢትዮጵያ ውስጥ ወታደራዊ ቤዝ ለመመስረት፤ ከአንዳንድ የሀገራችን አካባቢዎች ወጣቶችን በመመልመል፤ በሶማሊያ ሀገር ወታደራዊ ስልጠና ወስደው የጦር መሣሪያ ሳይታጠቁ ሰላማዊ ሰው መስለው ወደ ሀገራችን እንዲገቡ በማድረግ፣ ለሽብር ቡድኑ በመሰለል፣ ፈንጂ በማፈንዳት ድንገተኛ ጥቃት በመፈፀም አካባቢዎችን የሚቆጣጠር ኃይል ለማዘጋጀት ሲንቀሳቀስ እንደነበር የምርመራ ቡድኑ ባካሄደው ማጣራት ደርሶበታል፡፡
የሽብር ቡድኑ ሐምሌ 11 ቀን 2014 ዓ.ም ከሶማሊያ ሀገር በሰባት ተሸከርካሪና በአራት ሞተር ሳይክል በሌሊት ወደ ሀገራችን ሶማሌ ክልል አፍዴር ዞን ሁሉል አካባቢ ሲደርስ የሶማሌ ክልል ፖሊስ ከአካባቢው ነዋሪዎች ጋር በመተባበር ከአራት ቀን እልህ አስጨራሽ ውጊያ በኋላ በርካታ የሽብር ቡድኑን አባላት በመደምሰስ ሁለት ከፍተኛ አመራርን ጨምሮ 92 የሽብር ቡድኑ ታጣቂዎችን በመማረክ 406 ክላሽንኮቭ ጠመንጃ ከ67 ሳጥን መሰል ጥይቶች፣ 43 ላውንቸር እና 27 ብሬን ከአንድ ሳጥን መሰል ጥይት ጋር እንዲሁም በርካታ ተቀጣጣይ ፈንጂዎችን በኤግዚቢትነት መያዛቸውን የምርመራ መዝገቡ ያስረዳል፡፡
ከዚሁ ጋር በተያያዘ በስድስት የምርመራ መዝገብ 95 ተጠርጣሪዎች በሽብር ወንጀል ጉዳያቸው በፍርድ ቤት ክርክር ላይ እንደሚገኝ ከፌደራል ፖሊስ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

